Content-Language: am የቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ፎቶዎች የስላይድ ትዕይንት
header image


(ድረ ገጽ 5)

ግርማዊ ቀዳማዊ አፄ ኃይለ ሥላሴ



Emperor Haile Selassie at the time of crowning
Photo Courtesy of:   britannica.com




በወቅቱ የአሜሪካ መንግሥት፤ የኤርትራን በፌዴሬሽን የመተዳደር ሀሳብ በበጎ አይን መመልከቷ ለውሳኔው መጽደቅ እገዛ አድርጓል፡፡
Ethiopian Delegation Visiting the United States in 1919
ከግራ ወደ ቀኝ ሁለተኛው፤
ብላቴን ጌታ ኅሩይ ወልደ ሥላሴ፣
ሦስተኛው የልዑካን ቡድኑ ተጠሪ፤
ራስ ቢተወደድ ተሰማ ናደውና
አራተኛው፤ ከንቲባ ገብሩ ደስታ ይገኙበታል
Photo credit to: face2faceafrica

የኢትዮጵያና የአሜሪካ ኦፊሴላዊ ግንኙነት የጀመረው በዳግማዊ አፄ ምኒልክ ዘመነ መንግሥት በ1896 ዓ.ም. ሲሆን፤ ይህም አሜሪካ ኢትዮጵያን እንዲጎበኝ በላከችው የልዑካን ቡድን አማካኝነት ከዳግማዊ አፄ ምኒልክ ጋር በተፈራረሙት የወዳጅነትና የንግድ ውል አማካይነት ነው፡፡
አቶ ሊበን ኢብሳ ምስገና ይጋብውና በታዲያስ መጋዚን ላይ እንደአቀረበው ጽሁፍ ከሆነ፤
በአሜሪካው ፕሬዝደንት ቴዎዶር ሩዝቬልት ፕሬዝደንታዊ ዘመን፤ ዳግማዊ አፄ ምኒልክ፤ በ 1896 ዓ.ም ከአሜሪካ ጋር የተዋዋሉትን የወዳጅነትና የንግድ ውል መሠረት በማድረግ በንግሥተ ነገሥታት ዘውዲቱ ዘመነ መንግሥት በልዑል ራስ ተፈሪ የእንደራሴነት ሥልጣን፤ ሐምሌ 4 ቀን 1911 ዓ.ም. ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ አሜሪካ አንድ የአቢሲንያ የልዑካን ቡድን ተጉዞ ነበር፡፡
ከተጓዙትም አራት የልዑካን ቡድኑ አባላት መካከል፤
  1. ብላቴን ጌታ ኅሩይ ወልደ ሥላሴ
  2. ራስ ቢተወደድ ተሰማ ናደው የልዑካኑ ቡድኑ ተጠሪ እና
  3. ከንቲባ ገብሩ ደስታ
ይገኙበታል፡፡
የልዑካን ቡድኑ ኋይት ሀውስ ጥሪ ተደርጎለት በክብር በተገኙበት ወቅት፤ የአሜሪካ አምባሳደር ካፒቴን ሞሪስ፤
“ማወቅ ከምንፈልገው ዋናው ጉዳይ አንዱ፤ አቢሲንያ ከዓለም እጅግ ጥንታዊ የክርስቲያን ሐይማኖት ያላት ሀገር ናት፡፡”
በማለት ተናግረዋል፡፡

የልዑካን ቡድኑ ተጠሪ ቢተወደድ ተሰማ ናደውም በማከታተል፤
“ንጉሥ ሰለሞንን የጎበኘችው ንግሥት ሳባ የእኛ ንግሥት ነበረች፡፡ አሁን ያሉት መሪያችንም ከንግሥተ ሳባ ዘር ሲወርድ ሲዋረድ የተገኙ ናቸው፡፡”
በማለት ንግግር አሰምተዋል፡፡
ከኋይት ሀውስ ጉብኝት በኋላም የልዑካን ቡድኑ የኒውዮርክ፣ የዋሽንግተን ዲሲ፣ የችካጎንና ሳን ፍራንሲስኮን ከተሞች ጎብኝቷል፡፡ የእንግሊዝኛውን ጽሁፍ የበለጠ ለማንበብ፤ --->( ከምስጋና ጋር ለ፤ Tadias Magazine)
Emperor Haile-Selassie-I Signature
የቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ፊርማ
እስከ 1928 ዓ.ም. ድረስ የኢትዮጵያን የውጭ ግንኙነት ይቆጣጠሩ የነበሩት ሦስቱ አጎራባች የቅኝ ገዥ አገሮች ማለትም እንግሊዝ፣ ፈረንሳይና ጣሊያን ሲሆኑ፤ የአሜሪካ ሚና እየጎላ የመጣው ግን ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት ፍጻሜ በኋላ ነበር፡፡
በኢትዮጵያም የረዥም ዘመን ቅኝ ገዥነት ያደከማቸው እንግሊዞች ሳይወዱ በግድ ስፍራቸውን በትኩስ ኃይል ለምትንቀሳቀሰው አሜሪካ መተው ነበረባቸው፡፡
በሌላ በኩል እንግሊዞች ንጉሠ ነገሥቱን በስደታቸው ጊዜ መጠጊያ የሰጧቸውና ወደ አገራቸውም በክብር ለመመለስ ባለውለታቸው ቢሆኑም ቅሉ፤ የእንግሊዞች በአገሪቱ አስተዳደር ያለገደብ ጣልቃ እየገቡ ሥልጣን መሻማታቸውን ንጉሠ ነገሥቱ ዝም ብሎ መመልከት አላስቻላቸውም፡፡
እንግሊዞች፤ በኢትዮጵያ ላይ በገንዘብና በሐብት ረገድ ለሚያደርጉት ጥብቅ ቁጥጥር መፍትሔ ለማግኘት ይቻል ዘንድ አገሪቱ ፊቷን ወደ አሜሪካ በማዞር ከአሜሪካ ጋር የጠበቀ ግንኙነት እንዲኖራት ያልተቆጠበ ጥረት ማድረግ ጀመረች፡፡
ስለሆነም ከእንግሊዞች መዳፍ ለመላቀቅ የነበረው አማራጭ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነታቸውን ከአሜሪካ ጋር በአዲስ ምዕራፍ ማደስ ነበር፡፡

Ato Yilma Deressa
ክቡር አቶ ይልማ ደሬሳ
Photo credit to:  alchetron.com
በመጨረሻም አስር አመት ሙሉ ኢትዮጵያን ትቆጣጠር የነበረችው እንግሊዝ ዘወር እንድትል ተደርጋ፤ በምትኩ አሜሪካ ወደ መድረኩ ብቅ በማለት የኢትዮጵያ ዋና አጋዥ መሆን ጀመረች፡፡
በኢትዮጵያና በአሜሪካ መካከል የጠበቀ ግንኙነት ለመመስረት በመጀመሪያ የተጉት ከአሜሪካኖች ይልቅ ኢትዮጵያውያን ነበሩ፡፡
ኢትዮጵያና አሜሪካ ግንኙነታቸውን በአዲስ ምዕራፍ መጻፍ የጀመሩት በ1935 ዓ.ም. የኢትዮጵያ የገንዘብ ሚኒስትር ምክትል ሚኒስትር የነበሩት ክቡር አቶ ይልማ ደሬሳ አሜሪካንን በጎበኙበት ወቅት ነበር፡፡
ክቡር አቶ ይልማ ደሬሳ፤ እንግሊዝ አገር በሚገኘው በእውቁ የለንደን ስኩል ኦፍ ኢኮኖሚክስ ተምረው እንደጨረሱ ከ1949 ዓ.ም. ጀምሮ ለ13 ዓመታት ያህል በገንዘብ ምኒስትርነት እና በውጭ ጉዳይ ምኒስትርነት፣ የህግ መወሰኛ (ሴኔት) ምክር ቤት አባልነትና በአሜሪካ የኢትዮጵያ አምባሳደር በመሆን ያገለገሉ፣ ከፍተኛ የመንግሥት ሥልጣን የነበራቸውና እውቅናን ያተረፉ ምሁር ነበሩ፡፡
በጉብኝቱም ወቅት በኢትዮጵያ በኩል የቀረበው ጥያቄ፤ ወታደራዊ እርዳታ እንዲሰጣት፤ የገንዘብና የሕግ አማካሪዎች እንዲመደቡላት ነበር፡፡
አሜሪካም ወደ ኢትዮጵያ የቴክኒክ ቡድን በመላክ ሁኔታውን ካስጠናች በኋላ በ1936 ዓ.ም. ስምምነት በመፈረም የኢትዮጵያና የአሜሪካ ተራድኦ መሠረት ተጣለ፡፡
የአሜሪካ የቴክኒክ ኮሚቴ ጥናት ውጤትም በ1944 ዓ.ም. በሁለቱ አገሮች መካከል የ“ፖይንት ፎር” ስምምነት እንዲፈረም ተደረገ፡፡
የፖይንት ፎር ሰምምነት ካከናወናቸው ተግባራት ውስጥ፤
  • የእርሻና የጤና ጥበቃ ትምህርት ማስፋፋት
  • አንበጣ መከላከያን ማቋቋም
  • የሕዝብ አስተዳደር (ፐብሊክ አድምኒስትሬሽን) ሥልጠና መስጠትና
  • ኢትዮጵያውያንን ለትምህርት ወደ ውጭ አገር መላክ
የሚሉት ይገኙበታል፡፡
የፖይንት ፎር ስምምነት ለኢትዮጵያ የእድገት መሠረት የሚጥሉ መሆናቸው ግልጽ ቢሆንም፤ የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት መንግሥት ዋና ፍላጎት፤ ወታደራዊ እርዳታ ማግኘትና የእንግሊዞችን አምባገነንነት ለመቋቋም እንዲቻል አሜሪካ ዲፕሎማሲያዊ ድጋፍ እንድትሰጣት ነበር፡፡
Emperor Haile Selassie of Ethiopia Visiting Egypt
ግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ የካቲት 6
ቀን 1937 ዓ.ም. በግብፅ ጉብኝት
በማድረግ ከአሜሪካው ፕሬዚደንት ፍራንክሊን
ሩዝቬልት ጋር በአሜሪካ የጦር መርከብ
ላይ ተገናኝተዋል፡፡ ከንጉሠ ነገሥቱ ጀርባ
ይከተሉ የነበሩት ልዑል ራስ
ካሣ ኃይሉ ዳርጌ ናቸው
Photo link
የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሠት ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ፤ በ1937 ዓ.ም. ከአሜሪካው ፕሬዚዳንት ፍራንክሊን ሩዝቬልት ጋር በግብፅ ተገናኝተው ለኢትዮጵያ ወሳኝ በሆኑት፤ በኤርትራ፣ በኦጋዴንና በኢትዮ-ጅቡቲ የምድር ባቡር ጉዳዮች ላይ መነጋገር ቻሉ፡፡
በኦጋዴን ያለውን የእንግሊዞችን ጫና ለመቋቋም በሚል የፖለቲካ ስሌት መሠረት፤ ኢትዮጵያ ለአሜሪካው የፔትሮሊየም ኩባንያ ለሆነው ለሲንክለር በኦጋዴን የነዳጅ ፍለጋ ጥናት እንዲያካሂድ ፈቃድ ሰጠች፡፡
ከ 1943 ዓ.ም. በኋላ፤ ኤርትራ ከኢትዮጵያ ጋር በፌዴሬሽን ስትተሳሰር፤ አሜሪካም አሥመራ ባላት የመገናኛ ጣቢያ ምክንያት የምሥራቅ አፍሪካን እስትራተጅካዊ ጥቅሟን ለማስጠበቅ ስትል ከኢትዮጵያ ጋር ግንኙነቷን አጠናከረች፡፡
መስከረም 5 ቀን 1945 ዓ.ም. የእንግሊዝ ተራድኦ ቡድን ጓዙን ጠቅልሎ ከኢትዮጵያ ሲወጣ፤ ዘመናዊ ሥልጣኔን በማስተዋወቅ በአፍሪካ ታሪክ ውስጥ ከፍተኛ ተጽዕኖ ካሳደሩት መሪዎች አንዱ በሆኑት በቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዲፕሎማሲዊ ጥረት፤ ኢትዮጵያም የአሜሪካንን ወታደራዊ እርዳታ ለማግኘት ቻለች፡፡
በ1945 ዓ.ም. በኢትዮጵያና በአሜሪካ መካከል በተደረገው ስምምነት መሠረት፤ አሜሪካ በአዲስ ስያሜው “ቃኘው” የተባለውን በአሥመራ የሚገኘው የመገናኛ ጣቢያ ላይ የነበራትን ይዞታ አረጋገጠች፡፡
አሜሪካም በአጸፋው ለኢትዮጵያ ሰፊ የወታደራዊ እርዳታ ፕሮግራም ለመጀመር ተስማማች፡፡
“ማግ” በተባለው የአሜሪካ እርዳታ ፕሮግራም ቡድን አማካይነት፤ ኢትዮጵያ አምስት ሚሊዮን ዶላር ወጭ አድርጋ፤ 60 ሺህ ወታደሮች የያዘ ባለ ሦስት ክፍለ ጦር ሠራዊት ማቋቋም ቻለች፡፡
በዚህ የእርዳታ ፕሮግራም አማካይነት በተከታታዮቹ ዓመታት እየተሰጠ ቀጥሎ፤ አሜሪካ ለአፍሪካ አገራት ከምትሰጠው ወታደራዊ እርዳታ ውስጥ 60 በመቶው የሚመደበው ለኢትዮጵያ ነበር፡፡
ስለሆነም ከ1945 ዓ.ም. በኋላ በነበሩት ዓመታት ውስጥ፤ አሜሪካ በኢትዮጵያ የውጭ ግንኙነት መድረክ ዋና ተዋናይ በመሆን፤ በተለይ የጦር ሠራዊቱን ክፍል በማደራጀት ረገድ ወሳኝ ሚና ተጫውታለች፡፡
ዘመናዊ ሥልጣኔን በማስተዋወቅና በዲፕሎማሲው በአፍሪካ ታሪክ ውስጥ ከፍተኛ ተጽዕኖ ካሳደሩት መሪዎች አንዱ የሆኑት ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ፤ ቀደም ሲል የኢትዮጵያን አየር ኃይል ለማቋቋም ከፍተኛ ምኞት ስለነበራቸው፤ ንጉሠ ነገሥት ከመሆናቸው አንድ ዓመት በፊት በአፍሪካ ምድር ብቸኛ የሆነውን "ኢምፔሪያል ኢትዮጵያን አቪየሽን" የተሰኘ የአየር ኃይል በ1922 ዓ.ም. በነፃይቱ የኢትዮጵያ ምድር ማቋቋማቸው ይታወሳል፡፡ ( ---> የእንግሊዝኛውን ጽሁፍ የበለጠ ለማንበብ፤ ምስጋና ለ፤ adf-magazine.com)

Emperor Haile Selassie Showing up on Air Force plane
ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ በ1942 ዓ.ም. ወደ
አገራቸው ያሰገቡት የአየር ኃይል
የጦር አይሮፕላን ላይ ቆመው ይታያሉ

Photo credit to:  adf-magazine
ቀደም ሲል በስዊድን ቁጥጥር ሥር የነበረውን የኢትዮጵያ አየር ኃይል እና በኖርዌጅያኖች ይተዳደር የነበረው የኢትዮጵያ የባሕር ኃይልም ወደ አሜሪካኖች ተዛወረ፡፡
በዓለም እውቅና ባገኘው በእንግሊዙ የሳንድኸርስት የጦር አካዳሚ አምሳያ የተፈጠረውና የተደራጀው የቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ጦር አካደሚም፤ እንግሊዛውያኑ በብቃትና በጥራት ባሰለጠኗቸውና ባደራጇቸው የሕንድ አማካሪዎች አማካይነት ከተቋቋመ በኋላ በንጉሠ ነገሥቱ በግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ መስከረም 21 ቀን 1951 ዓ.ም. ተመርቆ ሥራወን በይፋ ሲጀምር የአሜሪካ የሰውና የማቴሪያል እርዳታ አልተለየውም ነበር፡፡
የኢትዮጵያ የፖሊስ ሠራዊትም የሠለጠነውና የተቋቋመው በጀርመንና በእስራኤል ሲሆን፤ የንጉሠ ነገሥቱ የክብር ዘበኛ ደግሞ የሠለጠነው በስዊድኖች ነበር፡፡
ከ1938 ዓ.ም. እስከ 1964 ዓ.ም. ድረስ አሜሪካ ለ26 ዓመታት ለኢትዮጵያ ያደረገችው ወታደራዊ እርዳታ፤ 180 ሚሊዮን ዶላር እንደሚደርስ ይገመታል፡፡
ከ1945 ዓ.ም. እስከ 1960 ዓ.ም. ድረስ ባለው ጊዜ ውስጥ፤ በአሜሪካ አገር 2,500 ኢትዮጵያውያን ወታደራዊ ሥልጠና ተሰጥቷቸዋል፡፡
የሚሊተሪ መሣሪያዎችንና ሎጂስቲክስን በተመለከተም ለምሳሌ፤
  • የጦር ጀቶች
  • ፀረ አውሮፕላን መቃወሚያዎች
  • ለባሕር ኃይል የሚያገለግሉ መርከቦችና ጀልባዎች
  • ለእግረኛው ጦር የነፍስ ወከፍ መሣሪያዎች እና
  • ወታደራዊ ዩኒፎርም
ሳይቀር የሚመጣው ከአሜሪካ ነበር፡፡
አሜሪካ ከምታበረክተው ወታደራዊ እርዳታ ውስጥ፤ በትጥቅም ሆነ በሥልጠና አቢይ ስፍራ የያዘው፤ በዘመናዊነቱና በቅልጥፍናው ዝናን ያተረፈው የኢትዮጵያ አየር ኃይል ነበር፡፡
በ 1938 ዓ.ም. የተባበሩት መንግሥታት ድርጅትን ለማቋቋም በተጠራው ጉባኤ ለመሳተፍ አሜሪካ ሄዶ የነበረው የኢትዮጵያ ልዑካን ቡድን፤ በኢትዮጵያ የአየር መንገድ ለማቋቋም የአሜሪካንን ዕርዳታ ጠየቁ፡፡
በዚህም መሠረት ኢትዮጵያ፤ Trans-contentental and Western Airline (TWA) ከተባለው የአሜሪካ አየር መንገድ ጋር፤ በአሜሪካ የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ አማካሪ በነበሩት በጆን ሰፔንሰር አማካይነት በተደረገው ስምምነት መሰረት ታህሳስ 12 ቀን 1938 ዓ.ም. የኢትዮጵያ አየር መንገድ ተቋቋመ፡፡
የኢትዮጵያ አየር መንገድ ሲቋቋም፤ በ 2.5 ሚሊዮን ብር የመነሻ ካፒታል በአክሲዮን መልክ በኢትዮጵያ መንግሥት ሙሉ ወጭ የተቋቋመ ሲሆን፤ አስተዳደሩ ግን ሙሉ በሙሉ በአሜሪካኖች ይመራ ነበር፡፡
የኢትዮጵያ አየር መንገድ ከተቋቋመ በኋላ፤ በስምምነቱ መሰረት ለ 30 ዓመታት ያህል አሜሪካ፤ ሥራ አስኪያጆችንና የቴክኒክ ተቆጣጣሪዎችን በመላክ ለአየር መንገዱ ሲመድቡ ቆይተዋል፡፡
Ethiopian Airlines first aircraft
በ1938 ዓ.ም. ይበር የነበረው
C-47 የተሰኘው የኢትዮጵያ
አየር መንገድ አይሮፕላን

Photo credit to:   selamtamagazine
የኢትዮጵያ አየር መንገድ ሥራውን የጀመረው የሁለተኛው ዓለም ጦርነት ቅርስ በሆኑትና ለወታደራዊ ትራንስፖርት አገልግሎት ይውሉ በነበሩት ቁጥራቸው አምስት በሚደርሱ C-47 በተሰኙ ዳኮታ አውሮፕላኖች ሲሆን፤ ሦስቱን አይሮፕላኖች፤ DC-3 የሚል ስያሜ በመስጠት ለመንገደኞች አመች እንዲሆን አሻሻሏቸው፡፡
ቆይቶም DC-6 የተሰኙ ባለ አራት ሞተር አውሮፕላኖችን በማስመጣት አገልግሎቱን ካሰፋ በኋላ፤ በ 1952 ዓ.ም. ወደ ጄት አውሮፕላኖች በመሸጋገር ሁለት ቦይንግ 720B በመግዛት ስራውን ጀመረ፡፡
በመጨረሻም በ 1964 ዓ.ም. የመጀመሪያው ኢትዮጵያዊ ዋና ሥራ አስኪያጅ ኮሎኔል ስምረት መድሃኔ ሲሾሙ፤ አየር መንገዱ ከአሜሪካኖች የአስተዳደር ቁጥጥር ወጥቶ ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ በኢትዮጵያውያን ቁጥጥር ሥር መሆኑ በውል ተረጋገጠ፡፡



በንጉሠ ነገሥቱ ላይ የተደረጉ አድማዎች መንስኤ ናቸው ተብለው በአብዛኛው ከሚገመቱት ወስጥ፤
  • አንደኛ፤ ንጉሠ ነገሥቱ በ1928 ሚያዝያ ወር ላይ አገር ጥለው ወደ ውጭ አገር መሄዳቸውና፣
  • ሁለተኛው፤ ንጉሠ ነገሥቱ ወደ አገር ከተመለሱም በኋላ አዲስ የአስተዳደር ሥርዓት ሲመሠርቱ፤ ጠላትን ያገለገሉ ባንዳዎች ሹመትና ማዕረግ ማግኘታቸው የሚሉት ይጠቀሳሉ፡፡
በዚህ የተነሳ በንጉሠ ነገሥቱ ላይ አመፁ የተባሉት ሦስት የቀድሞ አርበኞች የሚከተሉት ነበሩ::
  1. ደጃዝማች በላይ ዘለቀ
  2. ቢተወደድ ነጋሽ በዛብህ እና
  3. ብላታ ታከለ ወልደ ሐዋርያት

1ኛ:- ደጃዝማች በላይ ዘለቀ

Dejazmach Belay Zeleke
ደጃዝማች በላይ ዘለቀ
መሠረቱን በምሥረቅ ጎጃም በብቸና አውራጃ ያደረገው ደጃዝማች በላይ ዘለቀ፤ በአምስቱ ዓመታት የአርበኘነት ዘመን፤ በሕዝብ ዘንድ እጅግ ተወዳጅ፣ ጠላትን ያርበደበደና በተከታዮቹም ዘንድ ሞገስን ያገኘ፤ የተከታይ አርበኛውም ቁጥር ከሌሎች የአርበኞች መሪዎች ቁጥር የላቀና ቆራጥ የአርበኞች መሪ ነበር፡፡
ደጃዝማች በላይ ዘለቀ፤ በሕዝብ ዘንድ እጅግ ተወዳጅ መሆኑ፤ በንጉሠ ነገሥቱና በመኳንንቱ ዘንድ እምብዛም አልተወደደለትም ነበር፡፡
በዚህም ምክንያት በአርበኝነት ከኖረበትና ዝናን ካገኘበት አገር አንስተው፤ በራስነት ማዕረግ በደቡብ ኢትዮጵያ አገረ ገዥ እንዲሆን ሹመት አግኝቶ ነበር፡፡
ደጃዝማች በላይ ግን ሹመቱን ለመቀበል ደስተኛ አልነበረም፡፡
ለሌሎች የጎጃም የአርበኞች መሪዎች፤ በንጉሠ ነገሥቱ የተሰጣቸው ከፍተኛ ክብርና ማዕረግ፤ ደጃዝማች በላይ ዘለቀን ማስኮረፉ አልቀረም፡፡
ለምሳሌ፤ የጎጃም አርበኞች መሪና የበላይ ዘለቀ ጠበኛ ለነበሩት ለልጅ ኃይሉ በለው፤ የራስነት ማዕረግ፣ ለደጃዝማች መንገሻ ጀንበሬ ደግሞ የቢተዎደድነት ማዕረግ ተሰቷቸው የጎጃም ጠቅላይ ግዛትን እንዲያስተዳድሩ ተሾሙ፡፡
በላይ ዘለቀ ያዝባቸው የነበሩት በተለይ የሞጣና በከፊል የደብረ ማርቆስ አውራጃዎች ላይ ሹመት ማጣቱ የበለጠ ሳያሳዝነው አልቀረም፡፡
ቅሬታ እንዳደረበትም ለማሳየት፤ ከአዲስ አበባና ከድብረ ማርቆስ የሚላኩለትን ትእዛዞች አልቀበለም በማለት ገለፀ፡፡
በመጨረሻም በሚያዝያ ወር 1934 ዓ.ም. ከጎጃምና ከደብረ ማርቆስ የተውጣጣ ጦር የበላይ ዘለቀን ግዛት ወረረው፡፡
ደጃዝማች በላይ ዘለቀ ሦስት ወር ሙሉ ከተላከው ጦር ጋር ከተዋጋ በኋላ ስለተሸነፈ አዲስ አበባ ተወስዶ ታሰረ፡፡
ከጥቂት ወራት አስር በኋላም ከእስር ቤት አምልጦ ወደ ጎጃም በሚሄድበት ወቅት እንደገና ተይዞ ወደ አዲስ አበባ ከተመለሰ በኋላ የሞት ፍርድ ተፈርዶበት መርካቶ በሚገኘው አራተኛ ፖሊስ ጣቢያ አጠገብ ከወንድሙ እጅጉ ዘለቀ ጋር በስቅላት እንዲቀጣ ተደረገ፡፡

2ኛ:- ቢተወደድ ነጋሽ በዛብህ

የንጉሥ ተክለ ሐይማኖት የልጅ ልጅ የነበሩት ቢተወደድ ነጋሽ በዛብህም እንደ ደጃዝማች በላይ ዘለቀ በጎጃም የአርበኞች መሪ ነበሩ፡፡
ከነፃነት በኋላ በንጉሠ ነገሥቱ ዘመን፤ በምክትል ምኒስትርነትና በኋላም በሕግ መወሰኛ ምክር ቤት ፕሬዘዳንትነት ሠርተዋል፡፡
ቢተወደድ ነጋሽ በዛብህ፤ ከአንዳንድ ወታደራዊ መኮንኖች ጋር በመሆን ንጉሠ ነገሥቱን ገድዬ ወይም አስገድዬ ሬፐብሊክ እመሰርታለሁ በሚል እሳቤ አድማ መተው ነበር፡፡
ነገር ግን የአድማቸው ተሳተፊ እንዲሆን ጥሪ ያደረጉላቸው የአርበኞች መሪ ደጃዝማች ገረሱ ዱኪ አድማውን አጋለጡባቸው፡፡
በኋላም አድመኞችን በድብቅ አድብቶ እንዲያዙ ኃላፊነት የተሰጣቸው ኮሎኔል መንግሥቱ ንዋይ፤ አድመኞቹ ስብሰባ ላይ እንዳሉ በቁጥጥር ስር ካዋሏቸው በኋላ ፍርድ ቤት ቀርበው የተለያየ የእስር ቅጣት እንዲበየንባቸው ተደርጓል፡፡

3ኛ:- ደጃዝማች ታከለ ወልደ ሐዋርያት

እንደ ታሪክ ምሁሩ ፕሮፌሰር ባሕሩ ዘውዴ አገላለጽ፤ ብላታ ታከለ ወልደ ሐዋርያት፤ ንጉሠ ነገሥቱን ለ30 አመታት ያህል ባለመታከት መታገላቸውንና የግል ቂምና ምሬት እንደነበራቸው ገልፀዋል፡፡
Dejazmach Takele Woldehawariat
ደጃዝማች ታከለ ወልደሀዋሪያት
በ1928 ዓ.ም. ደጃዝማች ጠናጋሻው በሐብቴን ተክተው የአዲስ አበባ ተጠባባቂ ከንቲባ ሆነው ተመድበው የነበሩት ደጃዝማች ታከለ ወልደ ሐዋርያት፤ ንጉሠ ነገሥቱ ከመሰደዳቸው በፊት የንጉሡ ታማኝ አገልጋያቸው ነበሩ፡፡
ንጉሠ ነገሥቱ ከተሰደዱ በኋላ ግን መሰደዳቸውን አምርረው በመቃወማቸው፤ ንጉሠ ነገሥቱ ከስደት ተመልሰው እንደገና ሥልጣን ላይ እንዳይቀመጡ ማድረግ ዋነኛ ተልዕኳቸው ሆነ፡፡
የብላታ ታከለ ወልደ ሐዋርያትን አድማ የቆሰቆሰው ዋናው ምክንያት፤ የስደት ተመላሾችና የባንዳዎች ህብረት መፍጠር ነበር፡፡
በዚህም መሠረት የብላታ ታከለ ወልደ ሐዋርያት ዓላማ፤ ዘውዳዊውን ሥርዓት እንዳለ በማስቀጠል፤ በቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ምትክ ከልጅ እያሱ ልጆች አንዱ የሆነውን ዮሃንስ እያሱን ስልጣን ላይ ማስቀመጥ ነበር፡፡
ለዚህም የአድማ ተግባር የተወሰኑ የሠራዊቱን አባሎች ለማስተባበር ሞክረው ነበር፡፡
ሆኖም አድማ ማድረጋቸው ስለተነቃባቸው ተይዘው ጥቂት ጊዜያት ከታሰሩ በኋላ ተፈተው የምክትል አፈ ንጉሥነት ሹመት ተሰጣቸው፡፡
እርሳቸው ግን ለሁለተኛ ጊዜ አድማ ማድረጋቸው ስለታወቀ በድጋሚ ሰ7 ዓመት ከታሰሩ በኋላ እንደገና ተፈተው የአገር ግዛት ምኒስትር ሆነው ተሾሙ፡፡
በኋላም ጥቂት ዓመታት ቆይተው እንደገና ለሦስተኛ ጊዜ የአድማ ሙከራ አድርገው በሰበታ መንገድ ቦምብ አጥምደው ንጉሠ ነገሥቱን ለመግደል ያጠመዱት ወጥመድ ሲከሽፍባቸው መኖሪያ ቤታቸው መሽገው ኖሮ ከፖሊሶች ጋር ሲታኮሱ ተገደሉና የአድማቸው ፍጻሜ ሆነ፡፡

ንጉሠ ነገሥቱ ወደ ብራዚል ለጉብኝት ሄደው የነበረበትን ወቅት በመጠበቅ፤ ማክሰኞ ታህሳስ 4 ቀን 1953 ዓ.ም. ምሽት ላይ የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራ ተደረገ፡፡
General Mengistu Neway
መንግሥቱ ነዋይ

Photo link
Germame Neway
ግርማሜ ነዋይ

Photo link
የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራውን ያቀነባበሩት ሁለቱ ወንድማማቾች፤ መንግሥቱ ነዋይና ግርማሜ ነዋይ ነበሩ፡፡
የንጉሠ ነገሥቱ የክብር ዘበኛ አዛዥ የነበረው ብርጋዴር ጀነራል መንግሥቱ ነዋይ፤ ከ1928 ዓ.ም. በፊት በሆለታ የመኮንኖች ማሰልጠኛ የሰለጠነና ከፋሽስት ኢጣሊያ ወረራም በኋላ የጥቁር አንበሳ ድርጅቶችን አቋቁሞ ጠላትን ሲፋለም የነበር የወጣት አርበኞች አባል ነበር፡፡
የመፈንቅለ መንግሥቱ ዋና ጠንሳሽ ከመንግሥቱ ነዋይ ይልቅ ግርማሜ ነዋይ እንደነበረ ይነገራል፡፡
ግርማሜ ነዋይ በ1916 ዓ.ም. በአዲሰ አበባ ተወልዶ የ1ኛ እና 2ኛ ደረጃ ትምህርቱን በተዋቂው በተፈሪ መኮንን አጠናቆ በኋላም ለከፍተኛ ትምህርት አሜሪካ ከተላከ በኋላ የመጀመሪያ ዲግሪውንና ሁለተኛ ዲግሪውን በማሕበራዊ ሳይንስ በማጠናቀቅ ወደ ሀገሩ ከተመለሰ በኋላ የወላይታ አውራጃ ገዥ ሆኖ ተመደበ፡፡
በመንግሥት ሥራ ላይ ከተሰማራበት ጊዜ ጀምሮ ከፍተኛ የኃላፊነት ስሜት መሰማትና መቆርቆር አይነተኛ ባሕርይው ሆነ፡፡
መንግሥት ግን ይህን እዝማሚያውን አልወደደለትም፡፡
በዚህም ምክንያት ራቅ ያሉ ግዛቶች አስተዳዳሪ ሆኖ ቢሾምም ሀሳቡን ግን ሊገታው አልፈቀደም፡፡
በተመደበባቸው አገሮች ሁሉ ያለ መንግሥት እውቅና የተለያዩ ተራማጅ አርምጃዎችን መውሰድ ሲጀምር መንግሥትም ውሳኔውን እያሰናከለበት መሄድ ሲጀምር፤ ይህን ጊዜ ነው መንግሥትን መለወጥ አማራጭ የሌለው ተግባር መሆኑን አምኖ ወንድሙን መንግሥቱ ነዋይን በጎኑ እንዲቆም ማነሳሳት የጀመረው፡፡
የሁለቱ ወነድማማቾች የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራ፤ የዓላማ ግልጽነት የጎደለው፣ የአደረጃጀት ብቃት ያልነበረውና በርካታ ጉድለቶች የበዙበት ነበር፡፡
የመፈንቅለ መንግሥቱ መሪዎች ትልቁ ስሕተታቸው፤ የምድር ጦሩንና የአየር ኃይሉን ለማሳተፍ አለመቻላቸው ነበር፡፡
ያዋጣናል ብለው የተለሙት ዘዴ፤ የጦር ሠራዊት ከድቷል ብለው የመንግሥት ባለሥልጣኖችን ለማሳመን መሞከራቸው ነበር፡፡
ወዲያውኑ ሚኒስትሮችንና ሌሎች የሥርዓቱን ቁንጮ ባለሥልጣኖችን እየጠሩና እየለቀሙ አሰሩ፡፡
Leul Ras Asrate Kassa
ልዑል ራስ አስራተ ካሣ ኃይሉ

Photo credit to:   Antioco Lusci
Leutenant General Merid Mengesha
ሌፍትናንት ጀነራል
መርዕድ መንገሻ
የንጉሠ ነገሥቱንም ልጅ ልዑል አልጋወራሽ አስፋወሰንን በቁጥጥር ስር ካዋሏቸው በኋላ የአባታቸውን ዘውድ እርሳቸው እንደወረሱና ሥልጣኑንም እንደተረከቡ በሬድዮ ለኢትዮጵያ ሕዝብ መግለጫ እንዲሰጡ አስገድደው አናገሯቸው፡፡
ልዑል ራስ ካሣ ኃይሉ አራተኛ ልጅ የሆኑትና የንጉሠ ነገሥቱ የክብር ዘበኛ አዛዥ ልዑል ራስ አስራተ ካሣ፤ ከሜጀር ጀነራል መርዕድ መንገሻ ጋር በመሆን ከመፈንቅለ መንግሥቱ ማግሥት መደበኛ ሠራዊቱንና የአየር ኃይሉን በማስተባበርና በመምራት ፀረ መፈንቅለ መንግሥት እርምጃ መውሰድ ጀመሩ፡፡
በተጨማሪም በኤርትራ እንደራሴና የንጉሠ ነገሥቱን ልጅ ልዕልት ፀሐይ ኃይለ ሥላሴን በማግባት አማች የሆኑት ሌፍትናንት ጀነራል አቢይ አበበ በደቡብ አሜሪካ ጉብኝት ላይ ስለነበሩ፤ ከንጉሠ ነገሥቱ ታማኝ ጀነራሎች ጋር በማገናኘት መፈንቀለ መንግሥቱ እንዳይሳካ ቁልፍ ሚና ተጫውተዋል፡፡
የመጀመሪያው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ፓትሪያሪክ የነበሩት አቡነ ባስሊዮስ አማጽያኑን በማውገዝ ቤተክህነት ከንጉሠ ነገሥቱ ጎን መሆኗን አረጋገጠች፡፡
Colonel Wokneh Gebeyehu
ኮሎኔል ወርቅነህ ገበየሁ
Brigadier General Tsige Dibu
ብርጋዴር ጀነራል ጽጌ ዲቡ

Photo link
አሜሪካኖችም ጥቂት ጊዜ ካሰላሰሉ በኋላ ድጋፋቸውን ለንጉሠ ነገሥቱ ሰጡ፡፡
በመንግሥቱ ነዋይ የሚመራውና 9 ሺህ የሰለጠኑ ወታደሮች ያሉት የክብር ዘበኛ ሠራዊት፣ በብርጋዴር ጀነራል ጽጌ ዲቡ የሚመራው የፖሊስ ሠራዊት እና የደህንነት መሥሪያ ቤት አዛዡ ኮሎኔል ወርቅነህ ገበየሁ መፈንቅለ መንግሥቱን ለማሳካት ተቸግረው ነበር፡፡
ማክሰኞ ምሽት ታህሳስ 4 ቀን 1953 ዓ.ም. የአማጽያኑ መሪዎች የሆኑት ሁለቱ ወንድማማቾችና ግብረ አበሮቻቸው የጠነሰሱት ሴራ እንዳላዋጣቸው ሲረዱ፤ በገነተ ልዑል ቤተ መንግሥት (የአሁን የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ) አረንጓዴ ሳሎን ተብሎ በሚጠራው ውስጥ በቁጥጥር ሥር አድርገዋቸው የነበሩትን መሳፍንትና መኳንንት በሙሉ በጭካኔ ረሸኗቸው፡፡
ከተረሸኑትም መኳንንቶችና ባለሥልጣናት መካከል፤
  1. የሸዋ አርበኞች ማህበር መስራች፣ የአርበኞች ዋና መሪና አስተባባሪ፣ እንዲሁም የአገሪቱ የወቅቱ ጠቅላይ ምኒስትር የነበሩት ክቡር ራስ አበበ አረጋይ
  2. የአፄ ዮሃንስ የልጅ ልጅ የሆኑትና በማይጨው ጦርነት የሰሜን ጦር ግንባር የአርበኞች ጦር አዛዥ የነበሩት ልዑል ራስ ስዩም መንገሻ ዮሐንስ
  3. የንጉሠ ነገሥቱ የግል ንብረት አስተዳዳሪና የንስሐ አባት የሆኑት አባ ሃና ጅማ እና፣
  4. በማይጨው ጦርነት የጦር አዝማች የነበሩ፣ የንጉሠ ነገሥቱ የቅርብ ሰውና በጅሮንድ የነበሩት ደጃዝማች ለጥይበሉ ገብሬ ይገኙበታል፡፡
በኋላም በንጉሠ ነገሥቱ ታማኝ ጀነራሎችና ወታደሮች፣ መኳንንቶችና ባለሥልጣናት አጋዥነት የአማፂያኑ አድማ ከከሸፈ በኋላ የአማጽያኑ መሪዎች አዲስ አበባን ለቀው በመሸሽ ወደ መናገሻ ከተማ እንደገቡ የአማጽያኑ ግብረ አበሮችም እየታደኑ ተገደሉ፡፡
ብርጋዴር ጀነራል ጽጌ ዲቡም በተኩስ ልውውጡ መሀል ተገደለ፡፡
ከሁለቱ የመፈንቅለ መንግሥቱ መሪዎች ጋር በመሆን አመጹን በማስተባብር ከፍተኛ ድርሻ የነበረው የንጉሠ ነገሥቱ የፀጥታው ኃላፊ ሌፍትናንት ኮሎኔል ወርቅነህ ገበየሁም ራሱን ገደለ፡፡
የመፈንቅለ መንግሥቱ ዋና ጠንሳሽ የነበሩት መንግሥቱ ነዋይ እና ግርማሜ ንዋይ ሞጆ አካባቢ በጸጥታ ኃይሎች ተከበው ሳለ፤ ግርማሜ ንዋይ እጀን አልሰጥም ብሎ ራሱን አጠፋ፡፡
መንግሥቱ ነዋይ ግን ክፉኛ ቆስሎ ለጸጥታ ኃይሎች እጁን ሰጠ፡፡
ሆኖም የመፈንቅለ መንግሥቱ በተጀመረ በሦስተኛው ቀን፤ ማለትም ሐሙስ ታህሳስ 6 ቀን በአማጽያኑና በንጉሠ ነገሥቱ ታማኝ ሠራዊት መካከል የተኩስ ልውውጥ ተጀመረ፡፡
ብዙም ሳይቆዩ አማጽያኑ ተኩስ ለማቆም ዝግጁነታቸውን ቢገልጹም የንጉሠ ነገሥቱ ታማኝ ሠራዊት አማጽያኑን እንደሚያሸንፍ ስለተማመነ ከሁለት ቀን ውጊያ በኋላ ድል አደረገ፡፡
ከመፈንቅለ መንግሥቱ ማግሥት፣ ጃንሆይ የብራዚል ጉብኝታቸውን አቋርጠው በአስመራ በኩል ወደ አዲስ አበባ አመሩ፡፡
የንጉሳዊው ቤተሰብ፣ ከፍተኛ ባለስልጣኖችና ሌሎች የአዲስ አበባ ነዋሪዎች አየር ማረፊያውን ከበው፣ የጃንሆይን መምጣት በጉጉት ይጠባበቁ ነበር::
ንጉሠ ነገሥቱም ቅዳሜ ታህሳስ 8 ቀን 1953 ዓ.ም. አዲስ አበባ እንደገቡ፤ ንጉሠ ነገሥቱን የያዘቸው ዲሲ 6 አውሮፕላን እንዳረፈች፣ የመውረጃው ደረጃው ቀርቦ ቀይ ምንጣፍ አውሮፕላኑ ድረስ ተዘረጋ፡፡
ከአውሮፕላኑ ቀድመው የወረዱት የንጉሠ ነገሥቱ ልዩ ረዳት ጀነራል ደበበ ኃይለ ማርያም ነበሩ፡፡
ጃንሆይ ወታደራዊ ዩኒፎርማቸውን እንደለበሱ፣ ገና ከአውሮፕላኑ ብቅ እንዳሉ፣ ዙሪያውን ከቦ ይጠባበቃቸው የነበረው የአዲስ አበባ ነዋሪ ሕዝብ፣ እልልታውንና ጭብጨባውን አቀለጠው፡፡

ንጉሠ ነገሥቱ መሬቱን እንደረገጡ፣ አልጋ ወራሹ ልዑል አስፋ ወሠን፣ የጃንሆይ እግር ሥር ወደቁ፡፡
ልዑል አልጋ ወራሹ፤ አባታቸው እግር ሥር የወደቁበት ምክንያት፤ ከመፈንቅለ መንግሥቱ አድራጊዎች ጋር በመተባበራቸው ይቅርታ ለመጠየቅ አስበው ያደረጉት ይመስላል፡፡፡
ጃንሆይም፤ እግራቸው ሥር የተደፋውን ልጃቸውን ለማንሳት ምንም ሙከራ ሳያደርጉ በቁጣ ቃል፤
“ለእኛ ክብር የሚሆነው፣ አንተ ሞተህ ለቀብርህ ብንገኝ ነበር! ተነስ!” ማለታቸው ተዘግቧል፡፡ (...ምስጋና ለጽሁፍ አቅራቢ፤  ለባየህ ኃይሉ ተሰማ   ethioreference.com )

ጀነራል መንግሥቱ ታዳሚዎች በተገኘበት በገልጽ ፍርድ ቤት ቀርቦ፤
“ጃንሆይ! ከአይንዎ ሥር የነበረውን ቆሻሻ አሶገድኩልዎት እንጅ ወዳጆችዎን አልገደልኩም፡፡” በማለት መናገሩ ተዘግቧል፡፡
ፍርድ ቤቱ በስቅላት እንዲቀጣ ሲበይን፤ ንጉሠ ነገሥቱ ግን የሞት ፍርዱን ወደ ዕድሜ ልክ እስራት እንዲቀየርለት ፈልገው ነበር፡፡
በግሪን ሳሎን እልቂት የተገደሉት ከፍተኛ የመንግሥት ሹማምንቶች ቤተሰቦች ግን በንጉሠ ነገሥቱ የፍርድ ማሻሻያ ሀሳብ በመቆጣታቸው የተነሳ የሞት ቅጣት እንዲፈፀምበት ተወሰነ፡፡
ጀነራል መንግሥቱ ነዋይ በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች ታህሳስ 15 ቀን 1953 ዓ.ም. በቁጥጥር ሥር በዋለ ከሦስት ወራት በኋላ ሐሙስ መጋቢት 21 ቀን 1953 ዓ.ም. የስቅላት ቅጣት ተፈጽሞበታል፡፡


Prince Asrate Kassa with his wife Zuriashwork
ልዑል ራስ አሥራተ ካሣ ኃይሉና ባለቤታቸው
ወይዘሮ ዙሪያሽወርቅ ገብረ እግዚአብሔር

Photo credit to: ccjethio
በሐምሌ ወር 1964 ዓ.ም ንጉሠ ነገሥቱ፣ 80ኛ ዓመት የልደት በዓላቸውን ያከብሩ ስለነበር፣ ክረምቱ በልዩ ልዩ ዝግጅቶች ደምቆ ነበር፡፡
የልደታቸው ዕለት ጠዋት ልዑል ራስ አሥራተ ካሣና ባለቤታቸው፣ ጃንሆይን “እንኳን አደረሰዎ” ለማለት ወደ ቤተ መንግሥት አመሩ::
ልዑል ራስ አሥራተ ካሣ የልዑል ራስ ካሣ ኃይሉ የመጨረሻ ልጅ ናቸው፡፡
ጃንሆይ የተቀበሏቸው ከመኝታ ክፍላቸው ጋር በተያያዘው የእንግዳ መቀበያ ክፍል ነበር፡፡
ልዑል ራስ አስራተ ካሣ በተለይ ያዘጋጁትን ስጦታ ለጃንሆይ ካበረከቱላቸው በኋላ ጃንሆይ አልጋ ወራሻቸውን አሳውቀው፣ ሥልጣናቸውን ለመልቀቅ ከዚህ የተሻለ ጊዜ እንደሌለና “ይህንን ከፈጸሙም በታሪክ ውስጥ ስምዎ ለዘላለም ሲወሳ ይኖራል” ሲሉ በጃንሆይ እግር ስር በመውደቅ ተማጸኑ፡፡
ጃንሆይ፤ ልዑል ራስ አሥራተ ከእግራቸው ላይ እንዲነሱ ካደረጉ በኋላ፣
“እስኪ ንገረን እባክህ? ንጉሥ ዳዊት ሥልጣኑን በፈቃዱ ለቋል? ወይስ ሥልጣኑን በፈቃዱ የለቀቀ የኢትዮጵያ ንጉሥ በታሪክ ውስጥ ነበር? እግዚአብሔር እስከፈቀደልን ጊዜ ድረስ እንገዛለን፡፡ እኛ ከሄድን በኋላ ለኢትዮጵያ የሚጠቅማትን እርሱ ያውቃል”::
ብለው መናገራቸው ታውቋል፡፡
በየካቲት ወር 1966 ዓ.ም. ገንፍሎ የወጣው ሕዝባዊ አመፅ፤ የተለያዩ የህብረተሰብ ከፍሎች ማለትም፤ ወታደሩ፣ የመንግሥት ሠራተኞች፣ መምህራን፣ ተማሪዎችና ሥራ አጥ ወጣቶች፤ የነበረውን ዘውዳዊ ሥርዓት በመቃወም ተነሱ፡፡
በተለይ ውስጥ ወስጡን ሲብላላ የቆየውን የወታደሩን አመፅ ስንመለከት፤ የኑሯቸው ሁኔታ ይበልጥ እንግልት በዝቶበት የነበረው በአሥመራ የሚገኘው ሁለተኛ ክፍለ ጦር፤ ከኢኮኖሚያዊ ጥያቄ አልፎ የመንግሥት ለውጥ እንዲደረግ በመጠየቅ የከተማውን የሬድዮ ጣቢያ በቁጥጥር ሥር በማድረግ አመፁን አንድ እርምጃ ወደፊት ገፋው፡፡
ቀስ በቀስም የሲቪሉ ሕዝባዊ አመፅ እየበረታ መጥቶ፤ የካቲት 11 ቀን 1966 ዓ.ም. የሀገሪቱ መምሕራን ጠቅላላ የሥራ ማቆም አድማ መቱ፡፡
በዚሁም ዕለት ተመጣጣኝ የሆነ የታሪፍ ጭማሪ በመጠየቅ የታክሲ አሽከርካሪዎቸ ሥራ አቆሙ፡፡
ይህ ያልታሰበና ያልተቀናጀ ሕዝባዊ ማዕበል ግዙፍና ሁለንተናዊ በመሆኑ፤ የንጉሠ ነገሥቱ ሥርዓት ላይ ከፍተኛ ፍርሀትን ስለፈጠረ፤ የካቲት 21 ቀን 1966 ዓ.ም. በጠቅላይ ሚኒስትር አክሊሉ ሀብተ ወልድ የሚመራው የሚኒስትሮች ካቢኔ ከሥራ እንዲሰናበት ተደረገ፡፡
Prime Minister Aklilu Habtewold
ጠ/ ሚኒስትር አክሊሉ ኃብተወልድ
Leutenant General Abiye Abebe
ሌፍትናንት ጀነራል አቢይ አበበ
ንጉሠ ነገሥቱም ወዲያውኑ ሥራውን በለቀቀው ካቢኔ ምትክ፤ ሌፍትናንት ጀነራል አቢይ አበበ የጠቅላይ ሚኒስትርነቱን ቦታ እንዲረከቡ በንጉሠ ነገሥቱ ቢሾሙም፤ እርሳቸው ግን ሹመቱን የሚቀበሉት በሚኒስትሮች ካቢኔና በኢትዮጵያ ፓርላማ ተቀባይነት ካገኘ ብቻ እንደሆነ አሳወቁ፡፡
ንጉሠ ነገሥቱ ግን በሀሳቡ ሰላልተስማሙ፤ በጀነራል አቢይ ምትክ በወቅቱ የመገናኛ ሚኒስትር የነበሩትን ልጅ እንዳልካቸው መኮንንን ጠቅላይ ሚኒስትር አድረጎ በመሾም አዲስ ካቢኔ እንዲመሠረት ባዘዙት መሠረት አዲሱ ካቢኔ ተመሠረተ፡፡
ይሁን እንጅ ሕዝባዊ አመፁ ይበልጥ እየሰፋና እየተፋፋመ መጣ፡፡
የሕዝባዊ አመፁ ዋናና ልዩ ባሕርያት፤ ዝቅተኛው ሕብረተሰብ በኃያላን ላይ፤ ሠራተኛው በአሰሪ ላይ፤ የበታች መኮንኖች በበላይ መኮንኖች ላይ መነሳታቸው ነው፡፡
The Newly Appointed Prime Minister Endalkachew Mekonnen
ልጅ እንዳልካቸው መኮንን
በየምኒስቴር መሥሪያ ቤቶች፤ አንዳንድ ባለሥልጣናት በቢሯቸው ውስጥ መታሰር ጀመሩ፡፡
ይህን ሁሉ ሕዝባዊ አመፅ ለመቋቋም፤ አዲስ የተመሠረተው የጠቅላይ ሚኒስትር እንዳልካቸው ካቢኔ አንዳንድ እርምጃወችን በመውሰድ ጊዜ እንዲሰጠው ቢጠይቅም፤ ሊሳካለት አልቻለም፡፡
የተቃውሞውን ማዕበል መቋቋም ያቃተው አዲሱ ካቢኔ ሌላ ዘዴ መረጠ፡፡
ሠራዊቱን በጥቅልም ሆነ በከፊል አባብሎ ከጎኑ ለማሰለፍ ጥረት አድርጎ ነበር፡፡
ሠራዊቱ ትግሉን የሚያቀናጅለት ኮሚቴ አቋቁሞ በየካቲት ወር 1966 ዓ.ም. ንቅናቄውን ሲጀምር፤ የአየር ወለድ ብርጌድ አዛዥና የልጅ እንዳልካቸው መኮንን ዘመድ የሆነው ኮሎኔል የዓለም ዘውድ ተሰማ በተቋቋመው የሠራዊቱ ኮሚቴ ውስጥ የመሪነት ሥፍራ ይዞ ነበር፡፡
የኮሎኔል የዓለም ዘውድ በሠራዊቱ ኮሚቴ የመሪነት ሥፍራ መያዙ፤ ለጠቅላይ ሚኒስትር እንዳልካቸው ምቹ ሁኔታ ተፈጠረላቸው፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር እንዳልካቸው፤ የዓለም ዘውድን በመጠየቅና ንጉሠ ነገሠቱንም በማስፈቀድ የቀድሞ ካቢኔ ሚንስትሮችንና ሌሎችን ከፍተኛ የመንግሥት ሹማምንትን በቁጥጥር ስር እንዲውሉ አደረጉ፡፡



Bedroom of Emperor Haile Selassie
የቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ መኝታ ቤት

Photo link
አብዛኛወቹን የበታች መኮንኖችንና ባለ ሌላ ማዕረጎችን ያሰባሰበው ደርግ የተሰኘው ወታደራዊ ኮሚቴ ሥልጣኑን ቀስ በቀስ ከእንዳልካቸው ከወሰደ በኋላ አካሂዳለሁ ለሚለው ለውጥ እንቅፋት ይሆናሉ ብሎ ያሰባቸውን እርምጃዎች ሁሉ መውሰድ ጀመረ፡፡
በዚህም መሠረት የንጉሣዊው ሥልጣን ዋና አውታር የነበሩትን፤ እንደ ዙፋን ችሎት፣ የፍርድ አጣሪ ጉባኤ፣ ልዩ ካቢኔ፣ የግቢ ሚኒስቴርና የዘውድ ምክር ቤት የመሳሰሉትን የልዕለ መዋቅር ተቋማትን አፈረሰ፡፡
ይህ ሁሉ ሲሆን ግን፤ ንጉሠ ነገሥቱ ያፈዝ አደንግዝ እንደያዘው ሰው ሁኔታውን ለመቋቋም የሚያስችል ምንም ዓይነት የተለየ ትእዛዝ ሳይሰጡ በዝምታ ይመለከቱ ነበር፡፡
የወታደራዊው አማፂ ኃይሎች ንጉሠ ነገሥቱን ከሥልጣን አውርዶ ከቤተ መንግሥታቸው ለማሶጣት የማታለያ ዘዴዎችን ተጠቅመዋል፡፡
አማጺ ወታደሮች ለጃንሆይ ታማኝ እንደሆኑ፤ የሚቃወሙት ግን ባለሥልጣኖቻቸውን ብቻ እንደሆነ የማስመሰል ንግግር ይነግሯቸው ነበር፡፡

The Newly Appointed Prime Minister Endalkachew Mekonnen
ክቡር ዶክተር ልዑል አስፋወሰን አስራተ ካሣ
አዲስ አበባ ተወልደው፣ አዲስ አበባ ከተማ በሚገኘው የጀርመን ት/ቤት የተማሩትና ወደ ጀርመን ሀገርም በመሄድ ሕግና ኢክኖሚክስ አጥንተው በማዕረግ በመመረቅ በ1970 ዓ.ም. የዶክትሬት ዲግሪ የተቀበሉት እና ከ1975 ዓ.ም. ጀምሮ ለአፍሪካና ለመካከለኛው ምስራቅ የፖለቲካ አማካሪ ሆነው ከማገልገላቸውም በላይ በርካታ መጣጥፎችንና መጻሕፍትን ጽፈው ያቀረቡትና አልፎም ተርፎም “ኦርቢስ ኢትዮፒከስ” ተብሎ የሚጠራ የኢትዮጵያ ባህል ጥበቃና ማስፋፊያ ማህበር በማቋቋም የኢትዮጵያን ባሕልና ታሪክ ለአዲሱ ትውልድ ለማስተዋወቅ እውቅና የተሰጠው ሰፊ ሥራዎችን የሰሩት የክቡር ልዑል ራስ ካሣ ኃይሉ ዳርጌ የልጅ ልጅ የሆኑት ክቡር ዶክተር ልዑል አስፋወሰን አስራተ ካሣ ትውስታቸውን ሲናገሩ፤
“…አንድ ቀን ከምሳ በኋላ በአትክልቱ ስፍራ ስንዘዋወር አባቴ ያስጨነቀውን ጉዳይ ያካፍለኝ ጀመር፡፡
ለካስ ባለፈው ምሽት ጀነራል አቢይ አበበ ከቤታችን የመጡት አማጺ ወታደራዊ መኮንኖች ችግር ከመፍጠራቸው በፊት በቁጥጥር ሥር ለማዋል ጃንሆይ እንዲፈቅዱ ለመምከር ኖሯል፡፡
የዚያን እለት ጠዋት አባቴና የመከላከያ ሚኒስትሩ ጀነራል አቢይ ያቀረቡት ሃሳብ በጃንሆይ እምቢተኛነት ተቀባይነት ሳያገኝ ቀረ፡፡
በአትክልቱ ውስጥ የምናደርገው ሽርሽር ሊያበቃ ሲል፣ አባቴ ፍርሃቱን ፍርጥርጥ አድርጎ ሲገልጽልኝ፤

መጨረሻችን ተቃርቧል የሚል ሥጋት አለኝ፡፡
አማጺ ወታደሮች ለጃንሆይ ታማኝ እንደሆኑና የሚቃወሙትም ባለሥልጣኖቻቸውን ብቻ እንደሆነ አድርገው፣ ሀሰተኛ ተስፋ ለምስኪኑ ንጉሠ ነገሥት የሚመግቡ ኃይሎች፣ በቤተ መንግሥቱ ውስጥ አሉ፡፡
ነገር ግን የአማጺዎቹ ዋንኛ ዒላማ ራሳቸው ንጉሠ ነገሥቱ እንደሆኑ ጃንሆይ አሁን በቅርቡ ይረዱታል፡፡
በዝግታ ከምትሰምጠዋ መርከብ ላይ ምንም ሳያደርጉ ተቀምጦ ከማለቅ በስተቀር ሌላ አማራጭ ያለ አይመስለኝም፡፡'


ብሎኝ ነበር፡፡ አባቴ ከዚህ ቀደም በኢትዮጵያ ሁናቴ እንደዚህ ተስፋ ቆርጦ አይቼው አላውቅም፡፡”
በማለት በወቅቱ የነበረውን ሁኔታ ገልፀውታል፡፡

የደርግ ባለሥልጣናትም አስተማማኝ የሕዝብ ድጋፍ ለማግኘት ሲሉ የ1965ቱን የወሎ ረሀብ ምን እንደሚመስል ከንጉሠ ነገሥቱ የቅንጦትና የምቾት ኑሮ ጋር እያነፃፀሩ በእንግሊዛዊው ሪፖርተር ጆናታን ዲምቢልቢ ተዘጋጅቶ እንግሊዝ አገር በቴሌቪዥን የታየውን ዘጋቢ ፊልም፤ የመስከረም 1 ቀን 1967 ዓ.ም. አዲስ ዓመት ዋዜማ ምሽት ላይ ተቀናብሮ ለኢትዮጵያ እና በተለይ ለአዲስ አበባ ሕዝብ አቀረቡለት፡፡
Dergue Deposing the Emperor
ንጉሠ ነገሥቱን ከብሔራዊ
ቤተ መንግሥታቸው አውጥተው
በቢትልስ ቮልስዋገን ጭነው ሲወሰዷቸው

Photo credit to: face2faceafrica.comk
የዘጋቢ ፊልሙ የቀረበበት ዋና ዓላማ፤ በንጉሠ ነገሥቱ ሥርዓት ላይ ያነጣጠረ የመንግሥት ግልበጣ ሴራ ስለነበረ፤ ሕዝቡ ዘጋቢ ፊልሙን አይቶ በንጉሡ አገዛዝ ላይ ጥላቻ በማሳደር ቁጣው ገንፍሎ እነዲወጣና የደርግ የመፈንቅለ መንግሥት እንቅስቃሴ በሕዝቡ ዘንድ ተቀባይነት እንዲያገኝ ለማድረግ ነበር፡፡
ደርግ እንዳሰበውም ያቀነባበረው ፕሮፓጋንዳ ተሳክቶለት ንጉሠ ነገሥቱ ከዙፋናቸው እንዲወረዱ ሕዝቡ መጠየቅ ጀመረ፡፡
ሐሙስ መስከረም 2 ቀን 1967 ዓ.ም. ጧት ላይ የደርግ ተወካዮች ብሔራዊ ቤተ መንግሥት በመሄድ ንጉሠ ነገሥቱ ከሥልጣን እንዲወርዱ መወሰናቸውን ለንጉሡ የመርዶ ያህል ነግረው፤ ወደ ተዘጋጀላቸው ልዩ ሥፍራ እንዲሄዱ ጥያቄ አቀረቡላቸው፡፡
ንጉሠ ነገሥቱ ከቤተ መንግሥት ወጥተው የሄዱባት ቮልስ መኪና
ንጉሠ ነገሥቱ ከቤተ መንግሥት
ወጥተው የሄዱባት ቮልስ መኪና

ፎቶ በድህረ ገጽ አዘጋጁ
በንጉሠ ነገሥቱ ዘመነ መንግሥት፤ ለበርካታ ዓመታት በዘመናዊ መንገድ ተመልምሎ፣ ሰልጥኖና ተደራጅቶ፤ ለሕገመንግሥቱ፣ ለንጉሠ ነገሥቱና ለአገሩ ደኅንነት ታማኝ የነበረው ሠራዊት፤ የ82 ዓመት ዕድሜ ያላቸውን አዛውንቱን ንጉሥ ከቤተ መንግሥታቸው አውጥተው በቮልስ መኪና ላይ በማሳፈር፤ ደርግ ወደ ተጠነሰሰበትና አዲስ አበባ በሚገኘው አራተኛ ክፍለ ጦር ተብሎ ወደሚጠራው የጦር ሠፈር ያለምንም ኀፍረትና መሳቀቅ ወስደው በቁጥጥር ስር አደረጓቸው፡፡
ከ44 ዓመታት በኋላም 225ኛው የሰለሞናዊው የዘውድ አገዛዝ ሥርዓት ለመጨረሻ ጊዜ ፍፃሜውን አገኘ፡፡

ቆይቶም ንጉሠ ነገሥቱን ወደ ታላቁ ቤተ መንግሥት ወስደው የመጨረሻ የእስር ዓመታትን እዚያው እንዲያሳልፉ ተደረገ፡፡

ያለፍርድ የተገደሉት ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናት

ከንጉሡ እስር በኋላም፤ ኮሎኔል መንግሥቱ ኃይለማሪያም አብዛኛውን የንጉሣውያን ቤተሰቦች፣ ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናት፣ ከፍተኛ የጦር አዛዦችና መኮንኖች ከያሉበት ተለቅመው አዲስ አበባ በሚገኘው ከርቸሌ በተባለው ስፍራ ከአጎራቸው በኋላ ጥቅምት 11 ቀን 1967 ዓ.ም. በሰጠው ትእዛዝ መሠረት ወደ ታላቁ ቤተ መንግሥት እንዲዛወሩ አደረገ፡፡
በቤተ መንግሥቱና በሌላ ቦታም ታስረው በነበሩት 54 ከፍተኛ ባለሥልጣናት ላይ ግድያ እንዲፈጸምባቸው ለመወሰን፤ በታሰሩ በወሩ ህዳር 14 ቀን 1967 ዓ.ም. ቅዳሜ ቀን ማታ በኮሎኔል መንግሥቱ ኃይለማሪያም ሰብሳቢነት በደርግ ስብሰባ አዳራሽ ውስጥ 93 የደርግ አባለት ተሰብስበው፤ ማን ይገደል በሚለው ላይ እጅ በማውጣት ድምፅ መስጠት ተጀመረ፡፡
በዚህም መሠረት በቅደም ተከተል ከተጠሩት 7ቱ ከፍተኛ ባለሥልጣናት፤
  1. ፀሐፊ ትዕዛዝ አክሊሉ ኃብተ ወልድ
  2. ልዑል ራስ አስራተ ካሣ
  3. ጀነራል ከበደ ገብሬ
  4. ሌፍተናንት ጀነራል ድረሴ ዱባለ
  5. ሌፍተናንት ጀነራል አበበ ገመዳ
  6. ሪር አድሚራል እስክንድር ደስታ
  7. ራስ መስፍን ስለሽ
ተራ በተራ ስማቸው ከተጠራ በኋላ በጥይት ተረሽነው እንዲገደሉ በ 93ቱም የደርግ አባላት ሙሉ ድምፅ ተሰጠ፡፡

ቀጥሎ በተደረገውም ድምፅ አሰጣጥ፤ በቤተ መንግሥቱና በሌላ እስር ቤት ታስረው በነበሩት በቀሪዎቹ 47 ባለሥልጣናት ላይ ሙሉ ድምፅ ተሰጥቶ ከታሰሩበት ከምኒልክ ቤተ መንግሥት እና ከሌላም ስፍራ አውጥተው ከርቸሌ ወይም በተለምዶ ዓለም በቃኝ በተባለው እና ከ1915 ዓ.ም. ጀምሮ እስከ 1996 ዓ.ም. ድረስ በእስር ቤትነት ወደአገለገለው ማእከላዊ እስር ቤት በመውሰድ በጥይት እሩምታ ሁሉንም ተኩሰው ከገደሏቸው በኋላ የጅምላ መቃበር አዘጋጅተው በሬሣቸው ላይ ኖራ ነስንሰው አፈር በማልበስ ቀብረዋቸዋል፡፡
የተወሰደውም የግድያ እርምጃ በትክክል መፈፀሙን እንዲያረጋግጡ 9 የደርግ አባላት ተመርጠው ተልከው ነበር፡፡
የግድያ እርምጃው ሲወሰድ ኮሎኔል መንግሥቱ ኃይለማሪያም ከደርግ አባላት ጋር በመሆን ታላቁ ቤተ መንግሥት ውስጥ ስብሰባው ሳይበተን ቁጭ ብለው ግድያው በትክክል ስለመፈፀሙ የሚያረጋግጠውን ሪፖርት ይጠባበቁ ነበር፡፡

በሌፍትናንት ጀነራል አማን ሚካኤለ አንዶም ላይ እርምጃ ለመውሰድ የደርግ ወታደሮች ታንክና ከባድ የጦር መሣሪያዎችን በመያዝ ወደ ጀነራሉ ቤት በማምራት በተደረገው የተኩስ ልውውጥ በጀነራሉ መኖሪያ ቤት ውስጥ አብረው የነበሩና በተኩስ ልውውጡ ወቅት የተገደሉት 6ቱ፤
  1. ጀነራል አማን ሚካኤለ አንዶም
  2. መቶ አለቃ ደምሴ ሽፈራው
  3. ጁኒየር ኤርክራፍትስማን ዮሐንስ ፍቱይ
  4. አሥር አለቃ ተስፋየ ተክሌ
  5. አሥር አለቃ በቀለ ወ/ጊዮርጊስ
  6. አሥር አለቃ ተክሌ ኃይሌ
የተባሉት ይገኙበታል፡፡

ጀነራል አማን ሚካኤል አንዶም ለምን ተገደሉ?

Leutnant General Aman Michael Andom
ጀነራል አማን አንዶም በአሥመራ
ስታዲየም የተሰበሰበው ሕዝብ
የጋለ አቀባበል ሲያደርግላቸው
ሌፍትናንት ጀነራል አማን ሚካኤል አንዶም ፋሽስት ኢጣሊያ በ 1928 ዓ.ም. በኢትዮጵያ ላይ ወረራ በፈጸመችበት ወቀት ንጉሠ ነገሥቱን ደግፈው ከኢጣሊያ ጋር ከሚዋጉ የሱዳን ተዋጊ ኃይሎች ጋር በመቀላቀል ምክትል መቶ አለቃ ሆነው ተዋግተዋል፡፡
በ 1955 ዓ.ም. ደግሞ የሜጀር ጀነራልነት ማዕረግ አገኙ፡፡
በ 1956 ዓ.ም በኢትዮ ሶማሊያ ድንበር በተቀሰቀሰው ጦርነት የሶማሊያን ጦር በማሸነፍ አኩሪ ድል ያስመዘገቡና “የበረሃው አንበሣ” የሚል መጠሪያ በማግኘት በሠራዊቱ ዘንድ ከፍተኛ ተወዳጅነት የነበራቸው ነበሩ፡፡
ንጉሠ ነገሥቱ ከቤተ መንግሥታቸው ወተው ወደ እስር ቤት በተወሰዱ በሶስተኛው ቀን ጀነራል አማን ሚካኤል አንዶምን፤ በደርግ አባላት ጥያቄና ድጋፍ፤ በመጀመሪያ የጦር ኃይሎች ኤታ ማጆር ሹም፣(Chief of Army Staff) ቀጥሎ የመከላከያ ምኒስትር፣ በመጨረሻም የደረግ ጊዚያዊ አስተዳደር ደርግ ሊቀ መንበር አድርገው ሾሟቸው፡፡
ነገር ግን ጀነራል አማን በተወሰኑ ርዕሰ ጉዳዮችና ፖሊሲዎች ላይ ከደርግ ባለሥልጣናት ጋር ክፍተኛ ተቃርኖ ውስጥ ገቡ፡፡
ካልተስማሙባቸው ጉዳዮችም መካከል፤
  1. የደርግ አባላት ቁጥር መብዛት ለውሳኔ አመች ስላልሆነ መቀነስ እንዳለበት፣
  2. የኤርትራ ነፃ አውጭ ግንባርን በተመለከተ ደርግ ያለው ፖሊሲና እርሳቸው ያላቸው አቋም የተለየ መሆኑ እና እንዲሁም፤
  3. የንጉሣዊ ቤተሰብ አባላትና ቤተሰቦች፣ በሁለቱ ጠቅላይ ምኒስትሮች፤ በፀሐፊ ትዕዛዝ አክሊሉ ኃብተ ወልድ እና በልጅ እንዳልካቸው መኮንን፣ በቀድሞው ከፍተኛ የመንግሥት ባለስልጣናት እና በከፍተኛ ሹማምንቶች ላይ ሊፈፀም የታቀደውን የሞት የቅጣት እርምጃ መቃወማቸው፣
  4. አማን አንዶም የኤርትራ ተወላጅ መሆናቸው፣
የሚሉት ይገኙበታል፡፡
ጀነራል አማን ስለኤርትራ ጉዳይ የነበራቸው አቋም በድርድርና በስምምነት እነዲያልቅ በማሰብ ሁለት ጊዜ በግላቸው ወደ ኤርትራ በመጓዝ ለኤርትራ ሕዝብ ንግግር አድርገው ተመልሰዋል፡፡
ይህ የአማን አንዶም አቋም ከደርግ አባላት አቋም ጋር ፍፁም ተጻራሪ በመሆኑ ደርግም በበኩሉ በሚቃዎሙት የጦር ክፍሎች ላይ እርምጃ መውሰድ ጀመረ፡፡
በዚህም መሠረት ደርግ በቅድሚያ፤ በንጉሠ ነገሥቱ የክብር ዘብ፣ በአየር ኃይሉ እና በጦሩ የመሀንዲስ ክፍል ላይ እርምጃ መውሰድ ጀመረ፡፡
ህዳር 6 ቀን 1967 ዓ.ም. ጀነራል አማን አንዶም ለሁሉም የጦር ክፍሎች የደርግን አቋም የሚተች መልዕክት ላኩ፡፡
ከሁለት ቀናት በኋላ ኮሎኔል መንግሥቱ ኃይለማሪያም አጠቃላይ የደረግ ስብስባ እንዲጠራ በማድረግ ጀነራል አማን አንዶም በተገኙበት 5 ሺህ ሰዎች ወደ ኤርትራ እንዲላኩና ስድስት ንጉሣዊ ሹማምንቶች እንዲገደሉ ለደረግ አባለት ጥያቄ አቀረቡ፡፡
ጀነራል አማን አንዶም ጥያቄውን እንደማይቀበሉ ገልጸው በዚሁ ሳቢያ ስልጣናቸውን እንደሚለቁ አስታውቀው እቤታቸው መቀመጠን መረጡ፡፡
ህዳር 14 ቀን 1967 ዓ.ም. ጀነራል አማን አንዶምን በቁጥጥር ስር ለማድረግ የፀጥታ ኃይሎች ወደ መኖሪያ ቤታቸው ተላኩ፡፡
ጀነራሉ እጃቸውን እንዲሰጡ ቢጠየቁም እጃቸውን ለመስጠት ፈቃደኛ ስላልነበሩ በተደረገው የተኩስ ልውውጥ እርሳቸውና ከእርሳቸው ጋር የነበሩ ጠባቂዎች ተገደሉ፡፡
ደርግም የጀነራሉን የግድያ ምክንያት ባወጣው መግለጫ፤
አምባገነን ባሕርይ በማሳየቱ፣
ደርግንና ጦሩን የመከፋፈል ተገግባራት በመፈጸሙና
አኩርፎ ራሱን ከሥራ ገበታ በማግለሉ
የሚሉት ይገኙበታል፡፡
በዚሁ ዕለት ማታውኑ ቁጥራቸው 54 የሚሆኑ የቀድሞው የመንግሥት ከፍተኛ ባለሥልጣናትን ጨምሮ ከ6ቱ የነጀነራል አማን ወታደሮች ጋር በድምሩ 60 የቀድሞ ባለሥልጣናትን በጥይት እሩምታ ተኩሰው በመግደል የጅምላ መቃበር አዘጋጅተው ከቀበሯቸው በኋላ ህዳር 15 ቀን 1967 ዓ.ም. ለኢትዮጵያ ሕዝብ “የፖለቲካ ውሳኔ” እንደተወሰደባቸው በሚዲያ አስታወቁ፡፡
ከተገደሉት ውስጥ 54ቱ በሠላማዊ መንገድ እጃቸውን የሰጡና የሠሩት ወንጀል በፍርድ ቤት ያልተረጋገጠባቸው ንፁሃን ሰዎች ነበሩ፡፡
የፈፀሙት ወንጀል ቢኖር እንኳን በሕጋዊ መንገድ በምርመራ ተጣርቶ ውሳኔ እንዲያገኝ የመርማሪ ኮሚሽን አዋጅ በ1966 ዓ.ም. ተቋቁሞ ነበር፡፡
የተቋቋመውም የመርማሪ ኮሚሽን፤ በወሎ ተከስቶ በነበረው ድርቅና ረሃብ ሳቢያ ስለደረሰው እልቂት ባደረገው ምርመራ መሠረት ከዚህ በታች በተገለፁት የመንግሥት ባለሥልጣናት ላይ የወንጀል ክስ እንዲቀርብባቸው ለደርግ ጽሕፈት ቤት በጽሁፍ አስታውቆ ነበር፡፡
ፍርድ ቤት ይቀርባሉ ተብሎ ሲጠበቅ ፍርድ ቤት ሳይቀርቡ ያለፍርድ በግፍ ከተገደሉት መካከል፤
  1. ፀሐፊ ትዕዛዝ አክሊሉ ሀብተወልድ
  2. አቶ አካለወርቅ ሀብተወልድ (የአክሊሉ ሀብተወልድ ወንድም)
  3. ልጅ እንዳልካቸው መኮንን
  4. ጀነራል ከበደ ግብሬ
  5. ዶክተር ተስፋዬ ገብረእግዚ
  6. አቶ ሙላቱ ደበበ
  7. ደጃዝማች ካሣ ወልደማሪያም
  8. አቶ ሰይፉ ማህተመ ሥላሴ
ይገኙበታል፡፡

ከላይ የተጠቀሱት ባለሥልጣናት በ1949 ዓ.ም. በወጣው የወንጀለኛ መቅጫ ሕግ መሠረት ፍርድ ተሰቷቸው ቢሆን ኖሮ ቅጣታቸው ከ 3 ወር እስከ 10 ዓመት እስራት ያልበለጠ ይሆን ነበር፡፡
ይሁን እንጅ ህዳር 10 ቀን 1967 ዓ.ም. በደርጉ 2ኛ ምክትል ሊቀ መንበር በሆኑት በሌፍትናንት ኮሎኔል አጥናፉ አባተ ፊርማ በተላለፈ የጽሁፍ ትእዛዝ የመርማሪ ኮሚሽኑ ክስ እንዲቋረጥ ተደረገ፡፡
ከዚያም በኋላ በጥይት የተረሸኑና እጅ እንዲሰጡ ታዘው በኦፐሮሽን እርምጃ ተወስዶባቸው ከተገደሉት መካከል፤
⇨ 2 ጠቅላይ ምኒስትሮችን፣
⇨ 2 ልዑላንን፣
⇨ 17 ጀነራሎችን፣
⇨ 6 ደጃዝማቾችን፣
ጨምሮ በድምሩ 60 የሚደርሱ ንጉሣዊ ቤተሰቦችን፣ ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናትን፣ ሹማምንቶችን እና ከፍተኛ የጦር መኮንኖችን ያለምንም ፍርድ ህዳር 14 ቀን 1967 ዓ.ም. በዕለተ ቅዳሜ ደርግ የሞት ቅጣት እርምጃ ወስዶባቸዋል፡፡





ከዚህ በታች የተገለጸው ጽሁፍ፤ የደረግ ባለሥልጣናት ነሐሴ 17 ቀን 1967 ዓ.ም. ተሰብስበው በንጉሠ ነገሥቱ ላይ የግድያ እርምጃ እንዲወሰድ ትዛዝ ከሰጡበት ኦፊሽያል ማህተም ካረፈበት ደብዳቤ ላይ ቃል በቃል የተወሰደ የፎርማቱ ትክክለኛ ቅጅ ነው፡፡
Derg official letter written to assassinate the emperor

ከላይ በተነበበው የደርግ የግድያ ደብዳቤ መሰረት፤ የደረግ ባለሥልጣናት ሐሙስ ነሐሴ 22 ቀን 1967 ዓ.ም. በንጉሠ ነገሥቱ ላይ እርምጃ ከወሰዱ በኋላ ስለተወሰደው እርምጃ ኦፊሴላዊ መገለጫ ለሚዲያ ሲያስተላልፉ፤
ንጉሠ ነገሥቱ በትላንትናው ዕለት የመተንፈስ ችግር ስላጋጠማቸውና የፕሮስቴት ቀዶ ጥገና ሲደረግላቸው ህመማቸው በመወሳሰቡ ምክንያት ሕይወታቸው አልፏል፡፡
በማለት ለኢትዮጵያ ሕዝብ አስታወቁ፡፡
እውቁ የቀዶ ሕክምና ሐኪም የሆኑት ፕሮፌሰር አስራት ወልደየስ ግን በመንግሥት ሚዲያ የተነገረው የንጉሠ ነገሥቱ አሟሟት ፍፁም ሀሰትና የተዛባ መሆኑን በመግለጽ ንጉሠ ነገሥቱ የፕሮስቴት ቀዶ ጥገና ከተደረገላቸው ብዙ ወራት እንዳስቆጠሩና ከዚያ በኋላም በጥሩ ጤንነት ላይ እንደነበሩ በድፍረት አብራሩ፡፡
የደርግ መንግሥት ወድቆ ሌላ መንግሥት ከተተካ ከሦስት ዓመት በኋላ፤ በ 1994 ዓ.ም. በፍርድ ቤት በተወሰደው የማጣራት ሂደት፤
“ንጉሠ ነገሥቱ የሞቱት በሕመም ሳይሆን የተወሰኑ የደርግ መኮንኖች በአልጋቸው ላይ እንደተኙ አንገታቸውን አንቀው እንደገደሏቸው አረጋግጫለሁ፡፡”
በማለት መግለጫ ሰጠ፡፡
Patriots carying the coffin of Emperor Haile Selassie
የንጉሠ ነገሥቱን አስከሬን
አርበኞች ከመኪና ላይ ሲያወርዱ

Photo credit to: Peter Marlow
በኋላም ፍርድ ቤቱ በንጉሠ ነገሥቱ ግድያ እጃቸው አለበት ያላቸውን ተጠርጣሪዎች በሕይዎት ማጥፋትና በግድያ ወንጀል ክስ ከመሰረተባቸው በኋላ የግድያው ትዕዛዝ በቀጥታ የደርግ ምክትል ሊቀ መንበር በነበሩት በአጥናፉ አባተ እንደተሰጠና ይህንንም ድርጊት በተጨባጭ መፈፀሙን የሚያረጋግጡ ፊርማና ኦፊሺያል ማሕተም ያለባቸው ሰነዶች በመገኘታቸውና ሰነዶቹም በወቅቱ ይፋ መደረጋቸው ታውቋል፡፡
እነዚህም የደርግ ከፍተኛ ባለስልጣናት የግድያ ትእዛዙን የሰጡበት ሰነድ ላይ ንጉሠ ነገሥቱ የባላባታዊ ሥርዓት መሪ በመሆናቸው እንዲገደሉ የፈረሙባቸው ሰነዶች ሁሉም ሰው በገሃድ እንዲመለከተው በበይነ መረብ (internet) ሳይቀር ተለቋል፡፡

በ 1984 ዓ.ም. የንጉሠ ነገሥቱ አፅም በቤተ መንግሥቱ የምድር ቤት ውስጥ በኮንክሪት በተሞላ ወለል ውስጥ ተቀብሮ ተገኝቷል፡፡

Burial ceremony of Emperor Haile Selassie
Photo credit to: John Ryle
የተገኘውም የንጉሠ ነገሥቱ አስከሬን፤ በታዕካ ነገሥት በዓታ ለማርያም ገዳም ውስጥ በዳግማዊ አፄ ምኒልክ መቃብር አጠገብ ለ10 ዓመታት ያህል እንዲያርፍ ተደርጓል፡፡
በመጨረሻም እሁድ ጥቅምት 26 ቀን 1993 ዓ.ም. ሕይዎታቸው ካለፈ ከ25 ዓመታት በኋላ የኢትዮጵያ ኦርቶዶከስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ሥርዓተ ቀብራቸው በአግባቡ እንዲፈፀም ስታደርግ፤ በቀብር ሥነ ሥርዓቱ ላይ ከውጭ አገር የመጡት ጥቂት የአውሮፓ ጋዜጠኞች ብቻ ተገኝተዋል፡፡
የንጉሠ ነገሥቱ የቀብር ስነ ሥርዓት ሂደት የተጀመረው አስከሬኑ ካረፈበት ከታዕካ ነገሥት በዓታ ለማርያም ገዳም ተነስቶ ሲሆን፤ አስከሬኑ በኢትዮጵያ ሠንደቅ ዓላማ ተጠቅልሎና በአራት የጦር አርበኞች ታጅቦ ወደ መስቀል አደባባይ ከተጓዘ በኋላ ቀጥሎ ንጉሠ ነገሥቱ የንግሥ በዓላቸውን ወደ አከበሩበት ወደ መናገሻ ካቴድራል ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን አመራ፡፡

Tomb of Emperor Haile Selassie
Photo credit to: Stephany Evans Steggall
በመጨረሻም እራሳቸው ንጉሠ ነግሥቱ ወደ አሠሩት ወደ መንበረ ፀባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ቤተ ክርስቲያን ከደረሰ በኋላ አስከሬኑ በንጉሠ ነገሥቱ ባላቤት በእቴጌ መነን አስከሬን አጠገብ እንዲያርፍ ተደረገ፡፡
የቀብሩ አፈጻጸም ሥነ ሥርዓቱ፤ በመንግሥት በኩል በይፋ እውቅና ተሰጥቶት፤ ንጉሣዊ ክብርና ደረጃውን አግኝቶ የውጭ አገር መንግሥታት ተወካዮችም በተገኙበት እንዲከናዎን በንጉሠ ነገሥቱ ቤተሰቦች፣ በሥርዓቱ ደጋፊዎችና በንጉሠ ነገሥቱ አፍቃሪዎች ዘንድ ከፍተኛ ፍላጎት ቢኖርም፤ በጊዜው ሥልጣን ላይ የነበረው የኢሀዴግ መንግሥት ግን ይህ እንዲከናዎን ፈቃደኛ ባለመሆኑ ምክንያት እንደማኝኛውም ሰው በተለመደው መንገድ ቀብሩ ሊፈፀም ችሏል፡፡

የሰለሞናዊው የዘውድ ሥርዎ መንግሥት ፍጻሜ

የሰለሞናዊው የዘውድ ሥርዎ መንግሥት የዘር ሐረግ መነሻውን የተረከበው ከ13ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ጀምሮ ሲሆን፤ ከ1908 ዓ.ም. ጀምሮ እስከ 1922 ዓ.ም. ድረስ ባለው በንግሥተ ነገሥታት ዘውዲቱ ዘመነ መንግሥት፤ ልዑል ራስ ተፈሪ መኮንን አልጋ ወራሽና ባለሙሉ ሥልጣን እንደራሴ ተብለውና ንጉሥ ሆነው አገሪቱን ሲመሩ ቆዩ፡፡
በኋላም ልዑል ራስ ተፈሪ መኮንን በ39 ዓመት እድሜአቸው፤ ንጉሠ ነገሥት ወይም የንጉሦች ንጉሥ ተብለው ዘውድ ከጫኑበት ከ 1923 ዓ.ም. ጀምሮ ደርግ ባካሄደው የመፈንቅለ መንግሥት አመፅ ምክንያት 225ኛ የሆነው የንጉሠ ነገሥቱ የሰለሞናዊው የዘውድ ሥርዎ መንግሥት አገዛዝ የመጨረሻ ፍጻሜ እስካገኘበት እስከ መስከረም 2 ቀን 1967 ዓ.ም. ድረስ፤ “ሞኣ አንበሣ ዘእምነገደ ይሁዳ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ንጉሠ ነገሥት ዘኢትዮጵያ”
ተብለው ለ 44 ዓመታት ያህል፤ ዘውዳዊ ሥርዓተ መንግሥቱን ጠብቀው አቆይተዋል፡፡


ግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ፤ ሦስት ወንድ ልጆችንና አራት ሴት ልጆችን ወልደዋል፡፡

የግርማዊ ቀዳማዊ አፄ ኃይለ ሥላሴ ልጆች አጫጭር ታሪኮች


1. ልዕልት ሮማነወርቅ ኃይለ ሥላሴ


Prince Romanwork
ልዕልት ሮማነወርቅ
Dejazmach Beyene Merid
ክቡር ደጃዝማች በየነ መርዕድ
የግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ የበኩር ልጅ የሆኑት ልዕት ሮማንወርቅ፤ ለቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ የመጀመሪያ ባለቤታቸው ከሆኑት ከወይዘሮ ወይኒቱ አመዴ በነበራቸው ጋብቻ ጥር 3 ቀን 1902 ዓ.ም ተወለዱ፡፡
ልዕልቷ እድሜያቸው ለአቅመ ሔዋን ሲደርሱ ክቡር ደጃዝማች በየነ መርዕድን አግብተው፤
  1. ጌታቸው በየነ
  2. መርዕድ በየነ
  3. ሳምሶን በየነና
  4. ጌዲዮን በየነ

የተባሉ 4 ወንዶች ልጆችን የወለዱ ሲሆን ልጅ ሳምሶን በየነም የአንዳርጋቸው መሳይን ልጅ ወይዘሮ ኮረብቲት አንዳርጋቸውን በማግባት ሰባስትያኖስ በየነን ወልደዋል::
የፋሺስት ኢጣልያ ወረራም እንደተጀመረም፤ ባለቤታቸው ክቡር ደጃዝማች በየነ መርዕድ በደቡብ ኢትዮጵያ የጦር ግንባር ከነክቡር ራስ ደስታ ዳምጠው ጋር በመሰለፍ በውጊያ መስመር ሲፋለሙ ልዕልት ሮማን ወርቅ 3ቱን ልጆቻቸውን በመያዝ በደጀንነት አብረው ያልተለዩ ሲሆን በውጊያው ላይ ባለቤታቸው ደጃዝማች በየነመርዕድ ሲሞቱ ልዕልት ሮማነወርቅ ከ3ቱ ልጆች ጋር ተማርከው ግንቦት ወር 1929 ዓም ጣሊያን አገር "አዚናራ" በሚባል ስፍራ በግዞት መቀመጣቸው ይታወሳል::
በግዞት በነበሩበትም ወቅት ብዙ መጎሳቆል ስለደረሰባቸው ለሳምባ ምች ተዳርገዋል፡፡ በመጨረሻም ሕመሙ ስለጠናባቸውና አስፈላጊውን ሕክምና ባለማግኘታቸው ጥቅምት 4 ቀን 1933 ዓ.ም. ከመጀመሪያ ልጃቸው ከልጅ ጌታቸው በየነ ጋር ኢጣሊያ በሚገኘው በቱሪን መካነ መቃብር ቀብራቸው ተፈጽሟል፡፡
በሕይወት የተረፉት ልጆቻቸው ያደጉት በንጉሠ ነገሥት ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ሲሆን፤ የዘር ሐረጋቸውን አስቀጥለውት የነበሩት በእንግሊዝ የኖሩት ልጅ ሰባስትያኖስ በየነም ሐምሌ 18 2013 ዓ.ም. በተወለዱ በ 61 ዓመት እድሜያቸው ከዚህ ዓለም በሞት ተለይተዋል።
የልዕልት ሮማንወርቅ ባለቤት ራስ አንዳርጋቸው መሳይ የንጉሣዊው መንግሥት ከሥልጣን እንዲወገድ ሲደረግ ወደ ውጭ አገር ሄደው በነበረበት ወቅት ባደረባቸው ህመም ምክንያት ከዚህ አለም በሞት ተለይተዋል፡፡



2. ልዕልት ተናኘወርቅ ኃይለ ሥላሴ


Prince Tenagnework
ልዕልት ተናኘወርቅ
Ras Desta Damtew
ክቡር ራስ ደስታ ዳምጠው
የመጀመሪያ ልጅ የሆኑት ልዕልት ተናኘወርቅ ኃይለ ሥላሴ ከአባታቸው ከቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ እና ከእናታቸው ከእቴጌ መነን አስፋው ጥር 3 ቀን 1904 ዓ.ም. በሐረር ከተማ ተወለዱ፡፡
ልዕልት ተናኘወርቅ ከራስ ደስታ ዳምጠው ጋር ተጋብተው ሁለት ወንድ ልጆችን ማለትም፤ አምሃ ደስታንና እስክንድር ደስታን ሲወልዱ፤ እንዲሁም አራት ሴት ልጆችን ማለትም፤ አይዳ ደስታ፣ ሰብለ ደስታ፣ ሶፊያ ደስታንና ሂሩት ደስታን ወልደዋል፡፡
ልዕልት ተናኘወርቅ በፋሽስት ወረራ ወቅት ከቤተሰቦቻቸው ጋር እንግሊዝ አገር ተሰደው በነበረበት ወቅት እመቤት ጽጌ ማሪያምን ከአባቷ ከአቶ አበበ ረታ ወልደዋል፡፡
ራስ ደስታ ዳምጠው ከፋሽስት ኢጣሊያ ጋር ለአገራቸው ነፃነት ሲሉ በመዋደቅ ላይ ሳሉ በፋሽስት ወታደሮች ተይዘው ተረሽነዋል፡፡
ልዕልት ተናኘወርቅ ከቤተሰቦቻቸው ጋር ወደ አገራቸው ከተመለሱ በኋላ ከራስ አንዳርጋቸው መሳይ ጋር ተጋብተው ራስ አንዳርጋቸው የቤገምድርና የሰሜን ጠቅላይ ግዛቶች ገዥ ሆነው ሲሾሙ እና እንደገናም ወደ ኤርትራ በመጓዝ የኤርትራ እንደራሴ ሆነው ሲሾሙ አብረው ተጉዘዋል፡፡
የልዕልት ተናኘወርቅ ስብዕና ባብዛኛው ወግ አጥባቂ አመለካከቶች ያላቸውና የንጉሣዊው ሥርዓት ተቋም ጠባቂ ተደርገው በሰፊው የሚወሰዱ ጠንካራ ሴት ናቸው።
የደርግ መንግሥት ሥልጣኑን በኃይል እንደተረከበ ልዕልት ተናኘወርቅም ከንጉሣውያን ቤተሰቦች ጋር አብረው እንዲታሰሩ ተደረገ፡፡
ልዕልት ተናኘወርቅ ከ15 ዓመታት እስራት በኋላ በ1981 ዓ.ም. ከንጉሣውያን ቤተሰብ አባላትጋር ከእስር ቤት በነፃ ተለቀቁ፡፡ ከእስር ከተፈቱ በኋላም ልዕልት ተናኘወርቅ በመጀመሪያ ወደ ለንደን በመጓዝ፣ ከዚያም ወደ አሜሪካ ዲሲና ቨርጂኒያ ስቴት በመሄድ ወድማቸውን ልዑል አልጋወራሽ አስፋወሰንን ተቀላቀሉ፡፡ በዚያን ጊዜ አብዛኛው የንጉሣውያን ቤተሰቦች በለንደን እና በዋሽንግተን ዲሲ አካባቢ ይኖሩ ነበር፡፡
የልዕልት ተናኘወርቅ ወንድም ልዑል አልጋወራሽ አስፋወሰን ሲሞቱ በሀዘን በመጎዳታቸው ምክንያት ወደ ኢትዮጵያ ተመልሰው በቋሚነት ለመኖር ከወሰኑ በኋላ የግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ አፅም ከተቀበረበት ሥፍራ ወጥቶ ሁለተኛው የቀብር ሥነ ሥርዓት ሲፈፀም እርሳቸውም በቀብር ሥነ ሥርዓቱ ላይ ለመገኘት ችለዋል፡፡
በመጨረሻም ልዕልት ተናኘወርቅ በአዲስ አበባ እየኖሩ ሳለ መጋቢት 28 ቀን 1995 ዓ.ም. ሕይዎታቸው ሊያልፍ ችሏል፡፡
ሥርዓተ ቀብራቸውም ሚያዝያ 5 ቀን 1995 ዓ.ም. በፓትሪያሪክ አቡነ ጳውሎስ መሪነት የኢዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ሊቀ ጳጳሳትና ቀሳውስት፣ የቀድሞ መኳንንቶችና በርካታ የኅብረተሰብ ክፍሎች በተገኙበት በመንበረ ፀባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ተፈፅሟል፡፡



3.ልዑል አስፋው ወሰን ኃይለ ሥላሴ


Prince Asfawosen Haile Selassie
ልዑል አስፋው ወሰን ኃይለ ሥላሴ
Princess Wolete Israel Seyum
ልዕልት ወለተ እስራኤል ስዩም
ልዑል አስፋው ወሰን፤ ከአባታቸው ከራስ ተፈሪ መኮንን እና ከናታቸው ከወይዘሮ መነን አስፋው ሐምሌ 20 ቀን 1908 ዓ.ም. በሐረር ከተማ ተወለዱ፡፡
ልዑል አልጋወረሽ አስፋወሰን የመርዕድ አዝማችነት ማዕረግ በማግኘት የወሎን ጠቅላይ ግዛት እንዲያስተዳድሩ ሹመት ተሰጣቸው፡፡
ልዑል አልጋ ወራሽ አስፋወሰን፤ የምእራብ ትግራይ ገዥ የሆኑት የልዑል ራስ መንገሻ ስዩም ልጅና የአፄ ዮሐንስ 4ኛ የልጅ ልጅ የሆኑትን ልዕልት ወለተ እስራኤል ስዩምን አግብተው ልዕልት እጅጋየሁን ከወለዱ በኋላ ትዳራቸው ፈረሰ፡፡
በኋላም ሁለተኛ ሚስታቸው የሆኑትን እና የራስ ደስታ ዳምጠው ወንድም የራስ አበበ ዳምጠው ልጅ የሆኑትን ልዕልት መድፈሪያሽ ወርቅ አበበ ዳምጠውን አግብተው፤ ልዕልት ማሪያም ሰናን፣ ልዕልት ስህን አዜብን፤ ልዕልት ስፍራሽ ብዙን አና አልጋ ወራሽ ዘራ ያዕቆብ የተባሉትን 3 ሴት ልጆችንና አንድ ወንድ ልጅ ወልደዋል፡፡
Princess Medferiashwork Abebe
ልዕልት መድፈሪያሽ ወርቅ አበበ
የልዑል አልጋ ወራሽ አስፋወሰን ሁለተኛ ሚስት የሆኑት የልዕልት መድፈሪያሽ ወርቅ አበበ እናት፤ ወይዘሮ ወሰንየለሽ መንገሻ ይባላሉ፡፡ የወይዘሮ ወሰንየለሽ አባት ራስ ቢተወደድ መንገሻ አቲከም፤ የዳሞትና የአገውምድር ገዥና የጎጃም ተጠሪ ነበሩ፡፡
በ1953ቱ የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራ ወቅት እነ ጀነራል መንግሥቱ ነዋይ፤ ልጅ ልዑል አልጋወራሽ አስፋወሰንን ካሰሩ በኋላ የአባታቸውን ዘውድ እርሳቸው እንደወረሱና ሥልጣኑንም እንደተረከቡ በሬድዮ ለኢትዮጵያ ሕዝብ መግለጫ እንዲሰጡ አስገድደው አናግረዋቸዋል፡፡
ልዕልት መደፈሪያሽወርቅ በአፄ ኃይለ ሥላሴ ላይ የተሞከረውን የመፈንቅለ መንግሥት ለማክሸፍ መፈንቅለ መንግሥቱን የሚቃወሙትን በማደራጀት በኩል ቁልፍ ሚና እንደተጫወቱ ይነገራል።
ልዕልት መደፈሪያሽወርቅ፤ በመፈንቅለ መንግሥቱ አቀናባሪዎች በቁጥጥር ስር ካልዋሉት የንጉሠ ነገሥቱ ቤተሰቦች ጋር በአንድ ላይ ስለነበሩ፤ ያልታሰሩትን መሳፍንትን በማሰባሰብና ከጦር ሠራዊቱ አባላት ጋር በመሆን የክብር ዘበኞችን አመፅ ለመደምሰስ የሚያስችል ከፍተኛ የማስተባበር ስራ እንደሰሩ ይነገርላቸዋል፡፡
ልዑል አልጋ ወራሽ አስፋወሰን ከፍተኛ ስትሮክ (የደም መርጋት ሕመም) ታመው ጄኔቫ ለህክመና ሄደው ነበር፡፡
በዚህም ምክንያት ንጉሠ ነገሥቱ ዙፋናቸውን የሚወርስ ሌላ አልጋ ወራሻቸውን በይፋ ይሰይማሉ ተብሎ ተጠብቆ ነበር፡፡
Zera Yacob Amha Selassie
ዘርአ ያዕቆብ አምሃ ሥላሴ
ኅዳር 21 ቀን 1944 የተወለዱት ዘርአ ያዕቆብ አምሃ ሥላሴ፤ አባታቸው በታመሙበት ሰዓት በአባታቸው ምትክ የኢትዮዽያ ንጉሠ ነገሥት ዙፋን ወራሽ ለመሆን በግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ተጠባባቂ የአልጋ ወራሽነት ሹመት ተሰቷቸው ነበር፡፡ ነገር ግን አልጋ ወራሽነቱ የሚፀናው እርሳቸው ከሞቱ በኋላ እንደሆነ ተናገሩ፡፡
በመካከሉ ደርግ ሕዝባዊ አብዮት በማካሄድ በመፈንቅለ መንግሥት ንጉሠ ነገሥቱን ከሥልጣናቸው አውርዶ የመሪነቱን ሥልጣን ተረከበ፡፡
በዚህም ምክንያት አልጋ ወራሽነታቸው ፍጻሜ ሳያገኝ በዚያው ተደመደመ፡፡
በ1981 ዓ.ም. አልጋ ወራሽ አስፋወሰን በለንደን በስደት ላይ በነበሩበት ጊዜ ልጃቸውን ዘራያዕቆብ አምኃ ሥላሴን “ተጠባባቂ አልጋ ወራሽ” ብለው ሰይመዋቸው ነበር፡፡
ከየካቲት 10 ቀን 1989 ጀምሮ በኢትዮጵያ የዘውድ ምክር ቤት ዕውቅና ስለተሰጣቸው በስደት ላይ ለሚገኘው ለኢትዮጵያ የዘውዳዊው አገዛዝ ሥርዓት መሪ ሆነው አገልግለዋል።
ልዑል አልጋ ወራሽ አስፋወሰን ከቤተሰባቸው ጋር ወደ ለንደን ተሰደው ለ15 ዓመታት ያህል ኖረዋል፡፡
በ1981 ዓ.ም. ልዑል አስፋወሰን “ስደተኛው ንጉሠ ነገሥት” ተብለው “ቀዳማዊ አምሃ ሥላሴ” የሚለውን ማዕረግ ይዘው ባለቤታቸው ልዕልት መደፈሪያሽወርቅም “ዕቴጌ“ የሚለውን ስያሜ እንዲያገኙ ተደረገ፡፡
ልዑል አልጋ ወራሽ አስፋወሰንም ሕይዎታቸው አስከአለፈበት እስከ 1989 ዓ.ም. ድረስ ከባለቤታቸው ከልዕልት መደፈሪያሽወርቅ ጋር በቨርጂኒያ አሜሪካ ውስጥ ኖረዋል፡፡



4. ልዕልት ዘነበወርቅ ኃይለ ሥላሴ


Princess Sofia Desta
ልዕልት ዘነበወርቅ ኃይለ ሥላሴ
Dej. Haileselassie Gugsa
ደጃዝማች ኃይለ ሥላሴ ጉግሣ
2ኛ ልጅ የሆኑት ልዕልት ዘነበወርቅ ከአባታቸው ከቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ እና ከናታቸው ከወይዘሮ መነን አስፋው መጋቢት 15 ቀን 1926 ዓ.ም. በአዲስ አበባ ተወለዱ፡፡
ልዕልት ዘነበወርቅ በ15 ዓመት እድሜያቸው ሰኔ 8 ቀን 1924 ዓ.ም. ከምሥራቅ ትግራይ ገዥ ከሆኑት ከደጃዝማች ኃይለ ሥላሴ ጉግሣ ጋር በአዲስ አበባ ጋብቻቸውን ፈጸሙ፡፡
ደጃዝማች ኃይለ ሥላሴ ጉግሣ የአፄ ዮሐንስ 4ኛ ልጅ የሆኑት የራስ ጉግሣ አርአያ ሥላሴ ልጅ ናቸው፡፡
የልዕልት ዘነበወርቅ እና የደጃዝማች ኃይለ ሥላሴ ጉግሣ ጋብቻ እና የልዕልት ዘነበወርቅ ወንድም አልጋ ወራሽ አስፋው ወሰን ከልዑል ራስ ሥዩም መንገሻ ልጅ ከሆኑት ከልዕልት ወለተ እስራኤል ሥዩም ጋር በጋብቻ መተሳሰር፤ የሰለሞናዊ የዘውድ ሥርዎ መንግሥት የተጋብዎ ጥምረትን ያመለክታል።
በዚህም የጋብቻ ትስስር ሳቢያ የሸዋውን የሰለሞናዊ ስርዎ መንግሥትን እና የሥልጣን ተቀናቃኙን የትግራዩን የሰለሞናዊ ስርዎ መንግሥት ወገን ለማስተሳሰር የተደረገውን ጥረት ያሳያል፡፡
ሆኖም በልዕልት ዘነበወርቅ እና በደጃዝማች ኃይለ ሥላሴ ጉግሣ መካከል የነበረው ጋብቻ እንደተፈለገው ውጤት አላመጣም፡፡ ልዕልቷ የባለቤታቸው አያያዝ ደካማና ከሚጠበቀው የወረደ እንደሆነ ቅሬታ ያሰሙ እንደነበረ ይነገራል፡፡ በሌላ በኩል በሁለቱም የአፄ ዮሐንስ ቤተሰቦች መካከል ከፍተኛ የሥልጣን ፉክክር ስልነበረ፤ ደጃዝማች ኃይለ ሥላሴ ጉግሣ የተሰጣቸው ማዕረግ የሥልጣን ተቀናቃኛቸው ከሆኑት ከአጎታቸው ከልዑል ራስ ሥዩም መንገሻ ጋር ሲነፃፀር የእርሳቸው ዝቅተኛ ነው በሚል ሰበብ ለምን የራስነት ማዕረግ አልተሰጠኝም በማለት ይበሳጩ እንደነበረ ይነገራል፡፡
ልዕልት ዘነበወርቅም በ1926 ዓ.ም በድንገት ከዚህ ዓለም በሞት ሲለዩ፤ መሞታቸውን የተረዱት ንጉሠ ነገሥቱ በልጃቸው መሞት ከፍተኛ ሐዘንና ብስጭት ስለተሰማቸው የልዕልቷ አስከን በፍጥነት ከመቀሌ ወደ አዲስ አበባ መጥቶ እንዲቀበር አዘዙ።
የልዕልት ዘነበወርቅም አስከሬን ከትግራይ ተልኮ የንጉሣውያን ቤተሰብ መቃብር ካለበት ከመንበረ ፀባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል በክብር አርፏል፡፡
ንጉሠ ነገሥቱ ለልዕልት ዘነበወርቅ መታሰቢያ የሚሆን በሰማቸው አንድ ሆስፒታል እንዲታነጽ አድርገዋል፡፡
የልዕልት ዘነበወርቅ ባለቤት የነበረው ኃይለ ሥላሴ ጉግሳ፤ በ1928ቱ የፋሽስት ኢጣሊያ ወረራ ወቅት ያለምንም ማወላወል አገሩን ከድቶ ከኢጣልያ ጋር በመቀላቀል ቀዳሚውን ስፍራ በመያዝ ንጉሳዊ ቤተሰቡን፤ መኳንንቱንና አገር ወዳድ የኢትዮጵያ ተዋጊ አርበኛውን ሁሉ ያስደነገጠ ተግባር ፈጽሟል።
ጣሊያኖችም ግለሰቡ ይመኝ የነበረውን የራስነት ማዕረግ ሰጥተው የትግራይ ቀዳሚ ገዥ ነህ ብለው ሰይመውት ነበር፡፡
ፋሽስት ኢጣሊያ በ1933 ዓ.ም. ኢትዮጵያን ለቆ ከወጣ በኋላ ኃይለ ሥላሴ ጉግሳ በአገር ክህደት ወንጀል በቁጥጥር ስር እንዲውል ተፈርዶበት በጣሊኖች የተሰጠውም የራስነት ሹመት ተገፎ ወደቀድሞው የደጃዝማችነት ማዕረግ እንዲመለስ ተደርጓል፡፡
ኃይለ ሥላሴ ጉግሳ የዘውዳዊው አገዛዝ በደርግ መንግሥት እስከተገረሰሰበት አስከ 1966 ዓ.ም. ድረስ ለ33 ዓመታት በቁም እስር ከቆየ በኋላ ብዙም ሳይቆይ ሕይወቱ አልፏል፡፡



5. ልዕልት ፀሐይ ኃይለ ሥላሴ


Princess Tsehay Haile Selassie
ልዕልት ፀሐይ ኃይለ ሥላሴ
General Abiye Abebe
ሌፍትናነት ጀነራል ዐቢይ አበበ
ልዕልት ፀሐይ ኃይለ ሥላሴ ከአባታቸው ከቀዳማዊ አፄ ኃይለ ሥላሴ እና ከናታቸው ከወይዘሮ መነን አስፋው ጥቅምት 2 ቀን 1912 ዓ.ም. በአዲስ አበባ የተወለዱ 4ኛ ሴት ልጅ ናቸው፡፡
ከአባታቸው ጋር በስደት እንግሊዝ አገር በነበሩበት ጊዜ በለንደን ግሬት ኦርመንድ ስትሪት ሆስፒታል ውስጥ ለታመሙ ሕፃናት ህክምና ለመስጠት በነርስነት ሠልጥነዋል፡፡ በኋላም በነርስነት ሙያ በመንግሥት ተመዝግቦ እውቅና ባገኘ የነርስነት ሙያ ተመርቀዋል፡፡
ፋሽስት ኢጣሊያ ከኢትዮጵያ ለቆ ንጉሠ ነገሥቱ ወደ ሀገራቸው ከተመለሱ በኋላ ንግሥቲቱ ሌፍትናነት ጀነራል ዐቢይ አበበን ካገቡ በኋላ ጀነራል ዐቢይ የወለጋ ጠቅላይ ግዛት አስተዳዳሪ ሆነው ሲሾሙ ከባለቤታቸው ጋር አብረው ሄደዋል፡፡ በኋላም በደሴ ሆስፒታል በነርስነት አገልግለዋል፡፡
ልዕልት ፀሐይ በወሊድ ምክንያት በተፈጠረባቸው የመወሳሰብ ችግር መንሥዔ ነሐሴ 11 ቀን 1934 ዓ.ም. ሕይዎታቸው ሲያልፍ ሕጻኑም በሕይወት ሊተርፍ አልቻለም፡፡
አስከሬናቸውም በታዕካ ነገሥት በዓታ ለማሪያም ገዳም በሚገኘው የነገሥታት መካነ መቃብር ውስጥ በክብር አርፏል፡፡
የልዕልቷ አባት ግርማዊ ቀዳማዊ አፄ ኃይለ ሥላሴ ለልዕልቲቱ መታሰቢያ “ልዕልት ፀሐይ ሆሰፒታል” ተብሎ የተሰየመ ሆሰፒታል አሰርተውላቸዋል፡፡ ሆኖም ደረግ ስልጣን ከያዘ በኋላ የሆሰፒታሉን ስም የጦር ኃይሎች ሆስፒታል በማለት ስያሜውን ቀይሮታል፡፡



6. ልዑል መኮንን ኃይለ ሥላሴ


Prince Mekonnen Haile Selassie
ልዑል መኮንን ኃይለ ሥላሴ
Princess Sara Gizaw
ልዕልት ሣራ ግዛው
ሁለተኛው ወንድ ልጅ የሆኑት ልዑል መኮንን ኃይለ ሥላሴ ከአባታቸው ከቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ እና ከናታቸው ከወይዘሮ መነን አስፋው ጥቅምት 6 ቀን 1917 ዓ.ም. ተወለዱ፡፡
ልዑል መኮንን ኃይለ ሥላሴ፤ የአክሱም ንቡረዕድ እና የራያና አዘቦ አውራጃ ገዥ የነበሩት የደጃዝማች ግዛው አበራ ልጅን ሣራ ግዛው አበራን አገቡ፡፡
ልዕልት ሣራ ግዛው ታህሳስ 23 ቀን 1921 ዓ.ም. ተወለዱ፡፡
ልዑል መኮንን ኃይለ ሥላሴና ልዕልት ሣራ ግዛው አበራ ስድስት ወንድ ልጆችን አፍርተዋል፡፡ ስማቸውም፤
1ኛ፡- ልዑል መኮንን መኮንን
2ኛ፡- ልዑል ጴጥሮስ ወሰን መኮንን
3ኛ፡- ልዑል ሚካኤል መኮንን
4ኛ፡- ልዑል ዳዊት መኮንን
5ኛ፡- ልዑል ፍሊጶስ ተፈሪ መኮንን እና
6ኛ፡- ልዑል በዕደ ማሪያም መኮንን
ይባላሉ፡፡
Dergue Deposing the Emperor
ልዑል መኮንን ከባለቤታቸው
ከልዕልት ሣራ ግዛው ጋር

Photo Link
ልዑል መኮንን ከጋብቻ በፊት የወለዷት ወይዘሮ ምሕረት መኮንን የተባለች ሴት ልጅ ነበራቸው፡፡
ግርማዊ ቀዳማዊ አፄ ኃይለ ሥላሴ ልዑል መኮንንን ከሌሎች ልጆቻቸው ሁሉ አብልጠው ይወዱት እንደነበረ ተዘግቧል፡፡
ልዑል መኮንን ኃይለ ሥላሴ በመኪና ሲጓዙ በነበረበት ወቅት በደረሰባቸው ድንገተኛ አደጋ ገና በለጋ እድሜያቸው በተወለዱ በ32 ዓመታቸው ግንቦት 24 ቀን 1949 ዓ.ም. ሕይዎታቸው ሊያልፍ ችሏል፡፡
ግርማዊነታቸው ለጉብኝት ግንቦት 23 ቀን 1949 ዓ.ም ወደ ሻሸመኔ ሄደው በነበረበት ወቅት ልዑል መኰንንም በማግስቱ ወደ ሻሸመኔ ለመሄድ አስበው ስለነበረ ከራስ መስፍን ጋር በኩንቢ ቮልስ ዋገን መኪና ተሳፍረው ሲጓዙ ደብረ ዘይትን አልፈው የሞጆን ወንዝ ሳይሻገሩ መኪናውን ያሽከረክር የነበረው ሾፌር የማሽከርከር በቂ ልምድ ስላልነበረው የመኪና አደጋ ሊያደርስ ችሏል፡፡ ሌሎች ተሳፋሪዎች ላይ ግን ከጭረት በስተቀር የከፋ ጉዳት አልደረሰባቸውም፡፡
ከናዝሬት ወደ አዲስ አበባ ሰው ጭኖ ሲመጣ የነበረው ኩንቢ ቮልስ ዋገን፤ የመኪና አደጋው ቦታ ደርሶ የጫናቸውን ሰዎች ከአራገፈ በኋላ፤ በመኪና አደጋው ጉዳት የደረሰባቸውን ልዑል መኮንን ኃይለ ሥላሴን ይዞ ወዲያውኑ በዕለቱ ደብረ ዘይት ከተማ አየር ኃይል ሆስፒታል ቢያደርሳቸውም ሕይዎታቸው ሊተርፍ አልቻለም፡፡
በስፍራው የነበሩ ሰዎች እንደተናገሩት ከሆነ ከተቀመጡበት ስፍራ በስተኋላ የነበረው ልዩ ልዩ ዕቃ የያዘ ሳጥን ከማጅራታቸው ላይ ሲወድቅ የአንገታቸው አከርካሪ ስለተመታ ለሞት እንደአበቃቸው ገልጸዋል፡፡( ...የበለጠ ለማንበብ  Getish Ras Teferi)
የቀብራቸውም ሥነ ሥርዓት፤ አባታቸው ግርማዊ ቀዳማዊ አፄ ኃይለ ሥላሴ እና እናታቸው እቴጌ መነን አስፋው፣ የልዑል መኮንን ባለቤት ልዕልት ሣራ ግዛው ከመላው ልዑላን ቤተሰቦች ጋር በተገኙበትና እንዲሁም የሐዘኑ ተካፋዮች፤ መሳፍንቶችና መኳንንቶች፣ ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናት፣ የኢትዮጵያ የመከላከያ ሠራዊት ከፍተኛ የጦር የበላይ አዛዦች እና ከፍተኛ የሀገር ሽማግሌዎችና ወዳጆቻቸው በተገኙበት፤ በመንበረ ፀባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል በንጉሣውያን መካነ መቃብር በክብር ተፈጽሟል፡፡

ልዕልት ሣራ ግዛው፤ እቴጌ መነን ከሞቱ በኋላ ንጉሠ ነገሥቱ በውጭ አገር ጉብኝት በሚያደርጉበት ወቅት ብዙውን ጊዜ አብረዋቸው ይጓዙ ነበር፡፡

ልዕልት ሣራ ግዛው ከንጉሣዊያን ቤተሰቦች መካከል እጅግ ያማሩ፤ ውብና የሚማርክ ደም ግባት እንደነበራቸው እርሳቸውን የተመለከቱ የውጭ ሀገር ሰዎች ሳይቀሩ ስለቁንጅናቸው መስክረውላቸዋል፡፡
የተማሪወች ንቅናቄ መሪ የነበረው ጥላሁን ግዛውም በልዕልቷ አባት በኩል ወንድማቸው ነው።
ደርግ ስልጣን ከተቆጣጠረ በኋላ ልዕልት ሣራም ከሌሎች ንጉሣዊ ቤተሰቦች ጋር በወህኒ ቤት ታስረው ነበር፡፡ በ 1980 ዓ.ም. ከእስር ከተለቀቁ በኋላም በአዲስ አበባ መኖር ጀመሩ፡፡

ልዕልት ሣራ ግዛው ባደረባቸው ሕመም ምክንያት በተወለዱ በ90 ዓመት እድሜያቸው የካቲት 10 ቀን 2011 ዓ.ም. ከዚህ ዓለም በሞት ተለይተዋል፡፡ አስከሬናቸውም በመንበረ ፀባዖት ቅደስ ሥላሴ ካቴድራል በንጉሣውያን መካነ መቃብር ተፈጽሟል፡፡



7. ልዑል ሣህለ ሥላሴ ኃይለ ሥላሴ


Prince Mekonnen Haile Selassie
ልዑል ሣህለ ሥላሴ ኃይለ ሥላሴ
Princess Mahitsente Habte Mariam
ልዕልት ማኅፅንተ ሐብተ ማሪያም
የመጨረሻ ወንድ ልጅ የሆኑት ልዑል ሣህለ ሥላሴ ኃይለ ሥላሴ ከአባታቸው ከቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ እና ከናታቸው ከወይዘሮ መነን አስፋው የካቲት 19 ቀን 1924 ዓ.ም. ተወለዱ፡፡
ልዑል ሣህለ ሥላሴ፤ አባታቸው ንጉሠ ነገሥት ተብለው፣ እናታቸውም ንግሥተ ነገሥታት ተብለው ዘውድ ከደፉ በኋላ የልዑልነት ማዕረግ አግኝተው የተወለዱ ብቸኛ ልጅ ያደርጋቸዋል፡፡
የልዑል ሣህለ ሥላሴ ወንድሞች ግን ልዑል አስፋወሰን እና ልዑል መኮንን የተወለዱት ወላጆቻቸው ከመንገሣቸው ከ1923 ዓ.ም. በፊት ነበር፡፡
ልዑል ሣህለ ሥላሴ፤ የወለጋ ገዥ የነበሩት የደጃዝማች ሐብተ ማሪያም ገብረ እግዚአብሔር (ወይም በሌላ መጠሪያቸው ኩምሳ ሞረዳ) ልጅ የሆኑትን ልዕልት ማኅፅንተ ሐብተ ማሪያምን አግብተው ብቸኛ ወንድ ልጃቸውን ልዑል ኤርምያስ ሣህለ ሥላሴ ኃይለ ሥላሴን ወልደዋል፡፡
Prince Ermias Sahle Selassie
ልዑል ኤርምያስ ሣህለ ሥላሴ
ልዑል ኤርምያስ ሣህለ ሥላሴ ከአማርኛ ሌላ እንግሊዝኛና ጀርመንኛ ቋንቋዎችን አቀላጥፈው ይናገራሉ፡፡
ልዑል ኤርሚያስ፤ የአፈ-ንጉሥ ፍሥሐ ገብረ ሥላሴ ልጅ ከሆኑት ከመጀመሪያ በላቤታቸው ከወይዘሮ ገሊላ ፍሥሐ ጋር ሰኔ 2 ቀን 1981 ጋብቻ ፈጽመው ሁለት መንታ ወንድ ልጆችን ወልደዋል።
በኋላም የመጀመሪያ ሚስታቸውን ፈተው ሁለተኛ ሚስታቸው የሆኑትን ልዕልት ሳባ ከበደን አግብተው በዋሽንግተን ሜትሮፖሊታን አካባቢ ይኖራሉ፡፡
ልዑል ኤርሚያስ ሣህለ ሥላሴ፤ በአሁኑ ጊዜ በስደት ላይ ለሚገኘው ለኢትዮጵያ የዘውድ ምክር ቤት ፕሬዝዳንት ሆነው በማገልገል ላይ ይገኛሉ።
የኢትዮጵያ የዘውድ ምክር ቤት፤ የባህል እና የሰብአዊነት ሚናን በማስፋፋት ላይ ያተኮረ ተልእኮ አለው።
ልዑል ኤርሚያስ፤ በኃይለ ሥላሴ ፈንድ እና በላሊበላ ቅዱስ ጊዮርጊስ ፋውንዴሽን አማካኝነት ለተቸገሩ ህፃናት የተማሪዎች ስኮላርሺፕ በመስጠት እገዛ በማድረግ ላይ ይገኛሉ።











1 / 30
visit
ንግሥት ኤልሳቤጥ እና ልዑል ፊሊፕ በ1957 ዓ.ም. ኢትዮጵያን በጎበኙበት ወቀት በቤተ መንግሥት ውስጥ ቀርበው ንጉሠ ነገሥቱንና እቴጌይቱን ጎንበስ ብለው እጅ ሲነሱ
2 / 30
visit
በ 1957 ዓ.ም. ንግሥት ኤልሣቤጥና ባለቤታቸው
ልዑል ፊሊፕ ኢትዮጵያን በጎበኙበት ወቅት
3 / 30
visit
ንግሥት ኤልሣቤጥና ልዑል ፊሊፕ በቤተ መንግሥት ውስጥ
4 / 30
visit
ንግሥት ኤልሣቤጥና ልዑል ፊሊፕ በቤተ መንግሥት ውስጥ
5 / 30
visit
ንግሥት ኤልሣቤጥ ለአንድ ኢትዮጵያዊ አርበኛ ሽልማት ሲሰጡ
6 / 30
visit
ንግሥት ኤልሣቤጥ በጉብኝት ወቅት
7 / 30
visit
ንግሥት ኤልሣቤጥ በቤተ መንግሥት አቀባበል ሲደረግላቸው
8 / 30
visit
ንግሥት ኤልሣቤጥና ባለቤታቸው ልዑል ፊሊፕ
በቤተ መንግሥት በራት ግብዣ ላይ
9 / 30
visit
ንግሥት ኤልሣቤጥ በራት ግብዣው ላይ ንግግር ሲያደርጉ
10 / 30
visit
በ 1955 ዓ.ም. ንጉሠ ነገሥቱ አሜሪካንን ሲጎበኙ ፕሬዘዳንት ጆን ኦፍ ኬኔዲ አቀባብል ሲያደርጉላቸው
11 / 30
visit
ንጉሠ ነገሥቱ አቀባበል ላደረገላቸው የአሜሪካን ሕዝብ ሠላምታ እየሰጡ ሲያልፉ
12 / 30
visit
ንጉሠ ነገሥቱን በሠንደቅ ዓላማ ያዦች በክብር ታጅበው ደረጃ ሲወርዱ
13 / 30
visit
ንጉሠ ነገሥቱ ከፕሬዘዳንት ጆን ኦፍ ኬኔዲ ጋር በጉብኝት ላይ
14 / 30
visit
ንጉሠ ነገሥቱ ከፕሬዘዳንት ጆን ኦፍ ኬኔዲ ጋር በጉብኝት ላይ
15 / 30
visit
ንጉሠ ነገሥቱ በኋይት ሀውስ የክብር ራት ግብዣ ሲደረግላቸው፤ ከንጉሠ ነገሥቱ በስተቀኝ፤ የአሜሪካ የመከላከያ ሚኒስትሩ ባለቤት፣ ከንጉሠ ነገሥቱ በስተግራ፤ የፕሬዘዳንት ጆን ኦፍ ኬኔዲ ባለቤት፣ ከጆን ኦፍ ኬኔዲ ባለቤት በስተግራ፤ ልዑል ራስ መስፍን ስለሽ
16 / 30
visit
በኋይት ሀውስ የክብር ራት ግብዣ ላይ
17 / 30
visit
ንጉሠ ነገሥቱ የካቲት 6 ቀን 1937 ዓ.ም. ወደ ግብጽ ተጉዘው
በአሜሪካ የጦር መርከብ ላይ ጉብኝት ሲያደርጉ
18 / 30
visit
ንጉሠ ነገሥቱ በ 1946 ዓ.ም. ስዊድንን ሲገበኙ የስዊድኑ ንጉሥ ጉስታፍ ሲቀበሏቸው
19 / 30
visit
ጥቅምት 29 ቀን 1947 ዓ.ም. ንጉሠ ነገሥቱ በጀርመን ኦፊሴላዊ ጉብኝት ሲያደርጉ
20 / 30
visit
የንጉሠ ነገሥቱ በጀርመን ጉብኝት
21 / 30
visit
የንጉሠ ነገሥቱ በጀርመን ጉብኝት
22 / 30
visit
የንጉሠ ነገሥቱ በጀርመን ጉብኝት
23 / 30
visit
የንጉሠ ነገሥቱ በጀርመን ጉብኝት
24 / 30
visit
ንጉሠ ነገሥቱ ከልዕልት ሣራ ግዛው ጋር በጀርምን ጉብኝት
ምስጋና ለ፤ dw.com
25 / 30
visit
ንጉሠ ነገሥቱ ስዊድንን ሲጎበኙ ከስዊድን ንጉስ ጉስታፍ ጋር በመሆን
የስዊድንን የባቡር ድርጅት ዳይሬክተር ጀነራል ሲተዋወቁ
26 / 30
visit
ንጉሠ ነገሥቱ በጀርመን ጉብኝት ባደረጉበት ወቅት
የቦን ዩኒቨርሲቲ የክብር ዶክትሬት ዲግሪ ሲያበረክትላቸው
ምስጋና ለ፤ dw.com
27 / 30
visit
ንጉሠ ነገሥቱ ከውጭ የመጡ እንግዶችን ሲቀበሉ
28 / 30
visit
ንጉሠ ነገሥቱ በ 1947 ዓ.ም. ከልዕልት ሣራ ግዛው ጋር ሆነው ኔዘርላንድን ሲጎበኙ
29 / 30
ንጉሠ ነገሥቱ የአሜሪካ የሚሊተሪ ዴሊጌሽን ኢትዮጵያ በመጣበት ወቅት ከዴሊጌሽኑ ጋር ሲፈራረሙ
30 / 30
ግንቦት 17 ቀን 1955 ዓ.ም. የአፍሪካ አነድነት ድርጅት
በተመሠረተበት ዕለት ከግብፁ ገማል አብደል ናስር ጋር ሲወያዩ




ምንጭ፤
  1. "የኢትዮጵያ ታሪክ - ከአፄ ልብነ ድንግል እስከ አፄ ቴዎድሮስ"  ደራሲ፡- ተክለ ጻድቅ መኩሪያ 1961 ዓ.ም.
  2. "የኢትዮጵያ ታሪክ ከ 1847 እሰከ 1983"  ደራሲ፡- ፕሮፌሰር ባሕሩ ዘውዴ
  3. "የታሪክ ማስታወሻ"  ደራሲ፡- ደጃዝማች ከበደ ተሰማ 1962 ዓ.ም.
  4. "ሕይወቴና የኢትዮጵያ እርምጃ - ፩ኛ መጽሐፍ"  ደራሲ፡- ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ንጉሠ ነገሥት 1928 ዓ.ም.
  5.   ethioreference
  6. ከዊኪፒዲያ የተተረጎመ