Content-Language: am ዳግማዊ አፄ ቴዎድሮስ ገጽ አንድ
header image



Minilk
The image is digitally edited by the webmaster

(ገጽ 1)

ዳግማዊ አፄ ቴዎድሮስ



የዳግማዊ አፄ ቴዎድሮስ የአስተዳደር፣ የአመራር ጥበብና
የሕይዎት ዘመን ትረካ

በእያንዳንዱ አርዕስት ሥር የሚገኘውን የድምጽ
ማጫወቻ በመጠቀም ትረካውን ማዳመጥ ይችላሉ

ትውልድና ዕድገት፣ ሽፍትነት በቋራ በረሃ፣ ጋብቻ፣
ድጋሚ ስለመሸፈትና የንግሥ ሥርዓት ክንውን
በአስተዳደር ዘመናቸው የሥልጣኔ ፈር ቀዳጅ
ስለመሆናቸውና ስላሰሩት የሴባስቶፖል መድፍ
የግል ባሕርያትና ልዩ ችሎታወች፣
የግብፆችና የአውሮፓውያን ሤራ
ከእንግሊዞች ጋር የገጠሙት ጦርነትና
የአገዛዝ ዘመናቸው የመጨረሻ ፍጻሜ


አፄ ቴዎድሮስ ከመንገሣቸው አስቀድሞ ካሣ ኃይሉ ተብለው ይጠሩ ነበር፡፡
አፄ ቴዎድሮስ ጥር 6 ቀን 1811 ዓ.ም. የሱዳን አዋሳኝ በሆነው በቋራ ወረዳ ውስጥ ከጎንደር ከተማ 12 ኪሎ ሜትር ያህል ርቃ በምትገኝ ዳዋ ተብላ በምትጠራ መንደር ተወለዱ፡፡
እናታቸው ወይዘሮ አትጠገብ ወንድወሰን ይባላሉ፡፡
አባታቸው አቶ ኃይሉ ወልደ ጊዮርጊስ የቋራ አውራጃ ገዥ ነበሩ፡፡
የአባታቸው አባት ደጃዝማች ወልደ ጊዮርጊስ ይባላሉ፡፡
የካሣ ኃይሉ የእናታቸው አባት ራስ ወዳጆ ይባላሉ፡፡
ካሣ ኃይሉ ከተወለዱ ከአንድ ዓመት በኋላ አባታቸው አቶ ኃይሉ ወልደ ጊዮርጊስ በሞት ተለዩአቸው፡፡
በአካባቢው ማኅበረሰብ ዘንድ ተወዳጅ የነበሩት አጎቶቻቸው ደጃዝማች ማሩና ደጃዝማች ክንፉ ካሣ ኃይሉን ወስደው እያስተማሩ አሳደጓቸው፡፡
ደጃዝማች ክንፉ ሲሞቱ፤ የአፄ ዮሐንስ 3ኛ ባለቤትና የቤገምድሩ ገዥ የራስ ዓሊ ትንሹ እናት የሆኑት እቴጌ መነን ሊበን አመዴ፤ ልጅ ካሣን የቋራ አገረ ገዥ አድረገው ሾሟቸው፡፡
ይሁን እንጅ ታላቅ ሕልም የነበራቸው ካሣ፤ በተሰጣቸው ሹመት ተወስነው መቅረቱ ሰላላረካቸው፤ ወደ በረሃ ገብተው ከሸፈቱ በኋላ በውጊያ አሸንፈው ደንቢያ የተባለውን አገር ተቆጣጠሩ፡፡


Thewodros going for battle
የአፄ ቴዎድሮስን ወደ
ዘመቻ ጉዞ የሚያሳይ ስዕል
ካሣ ኃይሉ በጀግንነታቸው ምክንያት ሁሉም ሰው ይፈራቸዋል፣ ይጠላቸዋል፡፡ መሄጃ አጡ፡፡ የሚያስጠጋቸው ሰው በማጣታቸው ለመኖር ሲሉ ሽፍትነት ጀመሩ፡፡
የካሣ ኃይሉ ገዥዎች ማለትም፤ የሰሎሞናዊው ሥርዎ መንግሥት ተወላጅ የሆኑት አፄ ዮሃንስ 3ኛ፣ ባለቤታቸው እቴጌ መነን ሊበን አመዴ እና ልጃቻው የቤገምድሩ ገዥ የሆኑት መስፍኑ ራስ ዓሊ 2ኛ ምንም ሳይፈይዱ ቁጭ ብለው፤ ካሣ ኃይሉ ግን በሽፍትነታቸው ዘመን በሱዳን በኩል ድንበር እያለፉ ወደ ኢትዮጵያ ግዛት ውስጥ በመግባት በተደጋጋሚ ቤት በማቃጠል፣ በመዝረፍና በመግደል የሚያስቸግረውን የአረቦች ማለትም የግብፅን ሠራዊት እየደጋገሙ በመምታት በርካታ ድሎችን አስመዝግበዋል፡፡
በጊዜው ዘመናዊ የተባለውን የጦር መሣሪያ ከታጠቀው የግብፅ ጦር ጋር የካሣ ሠራዊት ተጋጥሞ በጦር እየወጋ፣ በጎራዴ እየመታ ከፍተኛ ውጊያ ከማካሄዳቸውም ሌላ ወሰን አልፈው በመሄድ ግብጾችን ድል አድርገው ምሽጋቸውንም በማፈራረስ በርካታ የጦር መሣሪያዎችን ማርከዋል፡፡
የካሣን ዝና በኢትዮጵያም ሆነ በሱዳን በኩል እጅግ ከፍ እንዲል ያደረገው ይሄው በሱዳን በኩል ያስገኙት ተደጋጋሚ የጀግንነት ድል ነው፡፡
በዚህ ረገድ በቆራጡ የጦር መሪ በካሣ ኃይሉ ጥበብና ጀግንነት የተሞላው አመራር ደፋሮቹና ጀግኖቹ የካሣ ኃይሉ የጦር ወታደሮች የሀገራቸውን ዳር ድንበር ለማስከበር አጥንታቸውንና ደማቸውን በመገበር ብዙ መስዋዕትነት ከፍለዋል፡፡


ካሣ ኃይሉ ሽፍታ ቢሆኑም ቅሉ ያለማንም ሌላ ረዳት ራሳቸው ያደራጁትን ሠራዊት እየመሩ፣ እያወጉና እየተዋጉ፤ በሱዳን በኩል ባስገኙት ተደጋጋሚ የጀግንነት ድል ምክንያት የእርሳቸው ገዥዎች (አፄ ዮሐንስ 3ኛ ፣ እቴጌ መነንና መስፍኑ ራስ ዓሊ) ይፈሯቸውና ይጠሏቸው ስለነበር እሰከጭራሹ ለማስገደልም ይፈልጓቸው ነበር፡፡
እቴጌ መነን (የአፄ ዮሐንስ 3ኛ ባለቤት) ግን እነደዚህ አይነቱን ጀግና በጦርነት ሳይሆን በወዳጅነት መያዝ ስላሰቡ “የዕንግዳወርቅን ልጅ ፈተህ የእኔን ልጅ አግባ” ብለው መልዕክት ላኩባቸው፡፡
ካሣ ኃይሉም ከገዥዎቻቸው ጋር ሠላም ለመፍጠር ስለወደዱ በእቴጌ መነን ሀሳብ ተደስተው የቀድሞ ሚስታቸውን ፈተው በ 29 አመታቸው የእቴጌ መነንን የልጅ ልጅ፣ ማለትም የራስ ዓሊ አሉላን ልጅ ወይዘሮ ተዋበች ዓሊን በሕግ አገቡ፡፡
ራስ ካሣ ኃይሉና ወይዘሮ ተዋበች በጋብቻቸው የቆይታ ጊዜ አንድም ልጅ አልወለዱም፡፡


Thewodros going barefooted working on raod
አፄ ቴወድሮስ በባዶ እግራቸው
በመንገድ ሥራ ላይ

ከዚህ በፊት በተደጋጋሚ እንዳደረጉት ሁሉ ፣ ካሣ ኃይሉ በጊዜው ዘመናዊ የተባለውን የጦር መሣሪያ ከታጠቀው የግብፅ ጦር ጋር ውጊያ ገጥመው ድል ካደረጉ በኋላ ቆስለው ነበር፡፡
ቁስላቸው የበረታ ስለነበር ማገገም እንዲችሉ አፄ ዮሃንስ ሳልሳዊ አንድ ሰንጋ ልከውላቸው ነበር፡፡
እቴጌ መነን ግን ሰንጋ ሳይሆን የላኩላቸው፣ አንድ ብልት ሥጋ ብቻ ነበር፡፡
የካሣ ኃይሉ ባለቤት ወይዘሮ ተዋበች አንድ ብልት ሥጋ ብቻ በመላኩ ይህን ድርጊት የንቀት ያህል ስለቆጠሩትና በአያታቸው ድርጊት ስለተበሳጩ የተላከው ብልት ሥጋ ሳይበላ በአገልግል ውስጥ እንዲቀመጥ ከአዘዙ በኋላ፤
እንዴት ብንናቅ ነው አንድ ብልት ሥጋ ብቻ የተላከልን?
ጀግና ሰው እወዳለሁ፡፡ ፈሪ ወንድ ግን እንቃለሁ፡፡
ከፈሪ ሰው ጋርም አብሬ መኖር አልፈቅድም፡፡
ብለው ለአፄ ቴዎድሮስ ነገሯቸው::
ይህን የሚስታቸውን የቁጣ ንግግር የሰሙት ካሣም ቁጭት ስለተሰማቸው እንደገና ለመሸፈት ተገደዱ፡፡

ሲቨን ሮቢንሰን የተባለው ፀሐፊ ፤
እቴጌ መነን ኢትዮጵያን እየከፋፈሉ ሊሸጡ ካስማሙ ባላባቶች አንደኛይቱ ናቸው፡፡
በአሌክሳንድርያ የቤልጅዬም መንግሥት ቆንስላ (ካውንስለር) የነበረው ኤድዋርድ ብሎንዲል ከእቴጌ መነን ጋር በመነጋገር አጋሜንና እንጣሎን በ 15 ሺህ ማርትሬዛና በ 3 ሺህ ጠመንጃ ለመግዛት ተስማምቶ ነበር፡፡
ለዚህም ጉዳይ ኢትዮጵያዊው አባ ገብረ ማሪያም ለኢትዮጵያ መንግሥት ኃላፊ ሆነው ለሽያጭ ተግባር ዋና ደላላና ተዋዋይ ነበሩ፡፡
በማለት ጽፏል፡፡
አባ ገብረ ማርያም ካይሮ ውስጥ ከቤልጅጉ (Belgium) ቆንስል (Counselor) ከብሎንዲል ጋር የተዋዋሉት ውል እነደሚከተለው ይነበባል፡፡
በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም፡፡ እኔ ገብረ ማርያም የኢትዮጵያ እጨጌ፣ በኢትዮጵያ ገዥ በራስ ዓሊ ስም የሚከተለውን ተስማምቻለሁ፡፡
ለቤልጅግ ንጉሥ ግርማዊ ቀዳማዊ ሊዎፖልድና ለእርሳቸው ወራሾች ሁሉ እንዲሆን የአጋሜን አውራጃ በሙሉ ከአዲግራት እስከ ባሕሩ ድረስ ሰተናል፡፡

አባ ገብረ ማርያም በመስፍኑ በራስ ዓሊ ስም ከላይ የተጠቀሰውን ውል ይዋዋሉ እንጅ ጉዳዩን የፈጸሙት የራስ ዓሊ እናት እቴጌ መነን ነበሩ ተብሏል፡፡
ይሁን እንጅ የእቴጌ መነንንም ሆነ የአባ ገብረማሪያምን የሀገርን መሬት ቆርሶ ለውጭ ኃይል የመሸጭን ሀሳብ የአፄ ቴዎድሮስ መነሳት አጨናግፎታል፡፡
Weapons Used by Emperor Thewodros
አዲስ አበባ ብሔራዊ ሙዚየም የሚገኘው
የአፄ ቴዎድሮስ የጦር መሣሪያ

ምስግና ...ለ፤ አዲስ አበባ ብሔራዊ ሙዚየም
ካሣ ኃይሉ ያስመዘገቧቸው የመጀመሪያዎቹ የውጊያ ድሎች፤ በዘመነ መሳፍንት አውራዎች ላይ የተቀዳጇቸው ተከታታይ ድሎችን የሚያበስሩ ነበሩ፡፡
የካሣን የውጊያ ችሎታና ጥበብ አጉልተው ባሳዩት በነዚህ ድሎች አማካኝነትም የዘመኑ የመሳፍንት መሪ ተዋንያን በሚያስገርም ፍጥነት አንድ ባንድ ድል ሆኑ፡፡
በዚሀም መሰረት በውጊያ ድል ካደረጓቸው ወይም ካንበረከኳቸው መሳፍንቶች ውስጥ ከብዙ በጥቂቱ የሚከተሉት ይገኙበታል፡፡
  1. የጎጃሙ ገዥ ደጃዝማች ጎሹ ዘውዴ
  2. የጎጃሙ ገዥ ብሩ ጎሹ (የደጃዝማች ጎሹ ዘውዴ ልጅ)
  3. እቴጌ መነን (የአፄ ዮሐንስ 3ኛ ባለቤት)
  4. ትንሹ ራስ ዓሊ አሉላ
    (የእቴጌ መነን ልጅ ወይም የአፄ ቴዎድሮስ ባለቤት የወ/ሮ ምንትዋብ አባት)
  5. የሰሜን ኢትዮጵያና የትግራይ ገዥ ደጃዝማች ውቤ ኃይለማሪያም፤
    (የእቴጌ ጣይቱ የአባታቸው ወንድም)
  6. የሸዋዉ ገዥ ንጉሥ ኃይለ መለኮት

የትንሹ ራስ ዓሊ አሉላ የጦር መሪዎች የነበሩ

  1. ደጃዝማች ብሩ አሊጋዝ
  2. ደጃዝማች በለው
  3. ደጃዝማች አቤ
  4. ደጃዝማች ያዘው



Crow of Emperor Tewodros
በእንግሊዝ ወራሪ ጦር የተዘረፈውና
በእንግሊዝ ሀገር በቪክቶሪያ አልበርት
ሙዚየም የሚገኘው ሙሉ በሙሉ
ከወርቅ የተሠራው የአፄ ቴዎድሮስ ዘውድ
ካሣ ኃይሉ የዘመነ መሳፍንት አውራዎችን አንድ ባንድ ድል ካደረጉ በኋላ ወደ ጎንደር ወዲያውኑ ተመልሰው የንግሥ ሥርዓቱን ልፈጽም አላሉም፡፡
ይልቁንም “ደረስጌ” በተባለው ስፍራ፤ የትግራይና የሐማሴን ገዥ የሆኑትን ደጃዝማች ውቤ ኃይለማሪምን ውጊያ ገጥመው ድል ካደረጉ በኋላ እዚያው ደረስጌ በምትገኘው የማርያም ቤተ ክርስቲያን ውስጥ፤ ደጃዝማች ውቤ ከግብፅ አሌክዛንድርያ ተላልከው ባስመጧቸው አቡነ ሰላማ በሚባሉ ጳጳስ አማካይነት “ዳግማዊ ቴዎድሮስ ንጉሠ ነገሥት ዘኢትዮጵያ” ተብለው በ1845 ዓ.ም. በ34 ዓመት እድሜያቸው ዘውድ ደፍተው ነገሡ፡፡


 ዳግማዊ አፄ ቴዎድሮስ በዘመነ መንግሥታቸው፤
  1. የአውሮፓውያንን የሥልጣኔና የቴክኒክ ዕርዳታ ለማገኘት ያላሰለሰ ጥረት አድርገዋል፡፡
  2. ከተለያዩ የኢትዮጵያ ግዛቶች የመጡትን ወታደሮች በአንድ ሬጅመንት (ዓላማ ያለው የተደራጀ የጦር ኃይል) በማሰለፍ ከአካባቢያዊ ስሜት ተላቆ ሰፋ ያለ ሀገራዊ አመለካከት እንዲኖረው ጥረት አድርገዋል፡፡
  3. እስካለንበት ጊዜ ድረስ የምንጠቀምበትን ወታደራዊ ማዕረግ፤ ማለትም የአሥር አለቃ፣ የሃምሳ አለቃ፣ የሺ አለቃ፣ የመሳሰሉትን ማዕረጎች በሥልጣን ተዋረድ ፈጥረው ተግባራዊ ለማድረግ ጥረዋል፡፡
  4. ሠራዊታቸው በወርሐዊ ደመወዝ እንዲተዳደር ለማድረግ ሙከራ አድርገዋል፡፡
  5. በወታደራዊ ሥነ ሥርዓት የታነጸ፣ ዘመናዊ የጦር መሣሪያ የታጠቀና የተደራጀ ሠራዊት ለመፍጠር ጥረት አድርገው ባይሳካላቸውም ድንቅ ሀሳብ እንደነበራቸውና ፈር ቀዳጅ እንደነበሩ አስመስክረዋል፡፡
  6. አፄ ቴዎድሮስ ያለመታከት የውጭ መንግሥታትን ይጠይቁ የነበረው ዘመናዊ የጦር መሣሪያ እንዲሰጣቸው ሳይሆን ኢትዮጵያውያን መሣሪያውን የመሥራት ጥበብ እንዲኖራቸው የሚያሰለጥኑ ሰዎችን እንዲልኩላቸው ነበር፡፡
  7. አፄ ቴዎድሮስ የባሪያ ንግድን የማይደግፉ ስለነበሩ በባሪያ ገበያ ሊሸጡ የተዛገጁትን አስጠርተው ሴትና ወንድ በማጣመር አጋብተው ሁሉንም በነፃነት እንዲኖሩ ለቀዋቸዋል፡፡ ባሮችም እንዳይሸጡ ትዛዝ ሰተዋል፡፡
  8. የአፄ ቴዎድሮስ ዘመነ መንግሥት የአማርኛ ቋንቋ ያበበበትና የበለፀገበት ስለነበረ ለአማርኛ ሥነ ጽሁፍ በር ከፋች ሆኖ ይቆጠራል፡፡
  9. በግእዝ ቋንቋ ብቻ ተጽፈው የሚገኙ መጻሕፍት ለሕዝቡ ግልጽና ተደራሽ እንዲሆኑ በማሰብ በስፋት የማህረሰቡ መግባቢያ በሆነው የአማርኛ ቋንቋ እንዲተረጎሙ አድርገዋል፡፡
  10. ቀደም ብሎ በቃል ብቻ ይተላለፍ የነበረውን የመልዕክት ልውውጥ አስቀርተው መደበኛ የደብዳቤ ልውውጥ እንዲጀመር አድርገዋል፡፡
  11. በአፄ ፋሲል ዘመነ መንግስት ተጀምሮ በዘመነ መሳፍንት የተቋረጠውን ቤተ መጻህፍት በአዲስ መልክ እንዲያንሰራራ በማድረግ መንፈሳዊና ተጓዳኝ መጻህፍትን በማሰባሰብ ታላቅ ቤተ መጻህፍት አሠርተዋል፡፡
  12. በምስራቅ አፍሪካ የመጀመሪያው ማተሚያ ቤት የተቋቋመው በአፄ ቴዎድሮስ ዘመነ መንግስት ነው፡፡
  13. ገበሬው እንዲያርስ፣ ነጋዴው እንዲነግድ፣ የዕደ ጥበብ ባለሙያው ክሂሉን እንዲያሳድግ፣ ጉሊት የምትቸረችረውም ሥራዋን እነንድትቀጥል ሁሉም በሙያው እንዲተዳደር መመሪያ አስተላልፈዋል፡፡
  14. የእጅ ጥበብ አላቸው የሚባሉትን ኢትዮጵያውያንን ሁሉ ተሰብስበው በውጭ ሀገር ሚሲዮኖች አማካይነት የእደ ጥበብ ሙያ እንዲማሩና እንዲሰሩ አድርገዋል፡፡
  15. ወታደሮቻቸው የያዙት ጦርና ጎራዴ ወደ ማረሻነት ተለውጦ በምትኩ በጠመንጃ ብቻ እንዲሰለፉ ከፍተኛ ምኞትና ፍላጎት ነበራቸው፡፡

  16. ፕሮፌሰር ዶናልድ ክራሚ የአፄ ቴወድሮስን ሕይወት በተመለከተ፤
    “የዘመናዊ ሥልጣኔ ሀሳብ የገባው የመጀመሪያው የኢትዮጵያ ንጉሥ ነበር፡፡” በማለት ጽፏል፡፡









ምንጭ፤
  1. "አጤ ቴዎድሮስ"  ደራሲ፡- ጳውሎስ ኞኞ ግንቦት ወር 1985 ዓ.ም.
  2. "የኢትዮጵያ ታሪክ ከ 1847 እሰከ 1983"  ደራሲ፡- ፕሮፌሰር ባሕሩ ዘውዴ
  3. "መራራ እውነት በኢትዮጵያ ታሪክ "  ደራሲ፡- ታዬ ቦጋለ አረጋ 2011 ዓ.ም.
  4. "የኢትዮጵያ ታሪክ - ከአፄ ልብነ ድንግል እስከ አፄ ቴዎድሮስ"  ደራሲ፡- ተክለ ጻድቅ መኩሪያ 1961 ዓ.ም.
  5. የትረካው አጃቢ ሙዚቃ፣ ዋሽንት - በአንሙት ክንዴ   ዩቲውብ
  6. Courtesy of: Rare WW2 Footage - German Infantry - No Music, Pure Sound  youtube