Content-Language: am ንግሥተ ነገሥታት ዘውዲቱ ምኒልክ
header image



ንግሥተ ነገሥታት ዘውዲቱ ምኒልክ




የንግሥተ ነገሥታት ዘውዲቱ ምኒልክ የሕይወትና የአስተዳደር ዘመን ታሪክ

በእያንዳንዱ አርዕስት ሥር የሚገኘውን የድምጽ ማጫወቻ በመጠቀም
ትረካውን ማዳመጥ ይችላሉ

ትውልድ፣ ዕድገት፣ የጋብቻ ሁኔታና
የአባታቸውን ዙፋን ስለመውረስ
ንግሥት ዘውዲቱ፤ በንግሥና ዘመናቸው
ያከናወኗቸው ዐበይት ሀገራዊ ተግባራት
በወቅቱ በነበረው የፖለቲካ
እንቅስቃሴና ሽኩቻ የነበራቸው ቆይታ
በንግሥቲቱና በልዑል ተፈሪ መኮንን መካከል
የተፈጠረው አለመግባባትና የንግሥቲቱ ሕልፈተ ሕይወት




Empress Zewuditu
ወይዘሮ ዘውዲቱ ምኒልክ
ከመንገሣቸው በፊት
ዘውዲቱ፤ ከአባታቸው ከ ዳግማዊ አፄ ምኒልክ እና ከወረይሉ የባላባት ልጅ ከሆኑት ከናታቸው ከወይዘሮ አብቺው ሚያዝያ 22 ቀን 1866 ዓ.ም እነዋሪ ከተማ ተወለዱ፡፡
ዳግማዊ አፄ ምኒልክ ቀደም ሲል ወይዘሮ ሸዋረጋንና ልጅ አስፋወሰንን ወልደው ነበር፡፡
ነገር ግን ልጅ አስፋወሰን ገና በፊት በጨቅላነቱ ሲሞት፤ በኋላ ወይዘሮ ሸዋረጋም (የልጅ እያሱ እናት) በሞት ስለተለዩ በሕይዎት የቀሩት ብቸኛ ልጃቸው ዘውዲቱ ናቸው፡፡
ዘውዲቱ ገና ልጅ እያሉ እናታቸውና አባታቸው ስለተፋቱ፤ ያደጉት በአባታቸው ቤት ሲሆን፤ ምኒልክ ከ እቴጌ ጣይቱ ጋር ከተጋቡ በኋላ፤ ዘውዲቱና እቴጌ ጣይቱ ተጋብበተውና ተስማምተው ስለኖሩ፤ ምኒሊክም ዘውዲቱን የበለጠ እያቀረቧቸውና እየወደዷቸው መጡ፡፡
ምኒልክ የአፄ ዮሐንስን ንጉሠ ነገሥትነት ከተቀበሉ በኋላ፤ ከ አፄ ዮሐንስ ጋር የነበራቸውን ፖለቲካዊ ግንኙነት ለማጠናከር በማሰብ የ10 ዓመት ልጅ የሆኑትን ዘውዲቱን ለአፄ ዮሐንስ ልጅ ለራስ አርአያ ሥላሴ ዮሐንስ ዳሩላቸው፡፡
ከሁለት ዓመት በኋላ ራስ አርአያ ስላሴ ሲሞቱ፤ ዘውዲቱ ከመቀሌ ወደ አባታቸው ጋ ተመለሱ፡፡
በምኒልክና በአፄ ዮሐንስ መካከል መቃቃርና ግጭት ቢኖርም፤ ዘውዲቱ በትእግሥት እና በዘዴ ሁለቱንም ወገን ሳያስቀይሙ በማቻቻል ስለያዟቸው፤ ዘውዲቱ ወደ አባታቸ ወደ ሸዋ ሲመለሱ፤ አፄ ዮሐንስ ለዘውዲቱ በነበራቸው ፍቅር የተነሣ በርካታ ቁጥር ያላቸውና ምርጥ የሆኑ ከብቶችን አሲዘው ልከዋቸዋል፡፡
Ras Gugsa Wolle Spouse of Empress Zewuditu
የእቴጌ ጣይቱ የወንድም ልጅ እና
የንግሥተ ነገሥታት ዘውዲቱ
ባለቤት ራስ ጉግሣ ወሌ
ከዳግማዊ ምኒልክ መታመም በኋላ፤ እቴጌ ጣይቱ የነበራቸውን የፖለቲካና የሥልጣን መንገድ ለማመቻቸት በመሳብም ይመስላል፤ ዘውዲቱ፤ ንግሥተ ነገሥታት ከመባላቸው ከ 6 ዓመት አስቀድመው የወንድማቸው የራስ ወሌ ብጡል ልጅ ለሆኑት ለንጉሣዊው ቤተሰብና የጦር አዛዥ ለጉግሣ ወሌ ዳሩላቸው፡፡
ክሪስ ፕሩቲ የተባለው ፀሐፊ ስለ ራስ ጉግሣ ወሌ አስተያዬት ሲሰጥ፤
“ ብሩሕ አዕምሮ አላቸው ከሚባሉት ታላላቅ ሰዎች ውስጥ የሚመደብ፣ ታዋቂ ገጣሚ፤ መጽሐፍትን ማንበብ የሚወድና ጠንቃቃና በአስተዋይነት የሚያስተዳደር፤”
በማለት ጽፏል፡፡
ጉግሣ ወሌም ከጋብቻው በኋላ የቤገምድር የራስነት ማእረግ አግኝተው የቤገምድር ጠቅላይ ግዛትን እንዲያስተዳድሩ ሹመት ተሰቷቸው ነበር፡፡
Empress Taitu
እቴጌ ጣይቱ
ዳግማዊ ምኒልክ በ 1900 ዓ.ም. መጨረሻ ላይ ታመው በነበረበት ወቅት ወይዘሮ ዘውዲቱ፤ ንግሥት ከመሆናቸው በፊት ከ እቴጌ ጣይቱ ጋር ሆነው አባታቸውን በማስታመም ላይ ነበሩ፡፡
ሆኖም የመንግሥቱን የወራሽነት ሥልጣን ከተሰጣቸው፤ የእህታቸው የወይዘሮ ሸዋረጋ ምኒልክ ልጅ ከሆኑት ከ ልጅ እያሱ ጋር ባለመስማማታቸውና፤ ልጅ እያሱም ዘውዲቱ የሥልጣን ተቀናቃኛቸው አድርገው ስለወሰዷቸው፤ እቴጌ ጣይቱንና ወይዘሮ ዘውዲቱን ከአዲስ አበባ ቤተ መንግሥት አሶጧቸው፡፡
ዳግማዊ ምኒልክ ካረፉ በኋላ በሕዝቡ ዘንድ ያለመረጋጋት አንዳይፈጠር በማሰብ መሞታቸው ለሕዝብ ሳይገለጽ እንደዲቆይ የካቢኔ ሚኒስትሮቻቸው ወሰኑ፡፡
በዚህም ምክንያት ዳግማዊ ምኒልክ አልጋቸውን እንዲወርስ የተናዘዙላቸው ልጅ እያሱም፤ በሞግዚታቸው በራስ ተሰማና በቤተ ክርስያን ልቃውንት ምክር አማክኝነት፤ እድሜአቸው በሰል እስኪልና ከባለቤታቸው ጋር ያለው ጋብቻ በቤተ ክርስቲያን ሥርዓት መሠረት እስኪፈጸም ድረስ ንግሥናቸው ላልተወሰነ ጊዜ እንዲተላላፍ ተወሰነ፡፡
ይሁን እንጅ ልጅ እያሱ የተላለፈባቸውን ውሳኔ ችላ በማለት በራሳቸው መንገድ መጓዛቸው፤ የሚያሳዩት ያልተረጋጋ ባሕርይና ወደ እስልምናው ሐይማኖት ያደላሉ ተበለውም ይታሙ ስለነበረ፤ በመኳንንቱና በመሳፍንቱ ዘንድ ተግባራቸው ሁሉ አልተወደደላቸውም፡፡
ንግሥተ ነገሥታት ዘውዲቱ
ምኒልክ ከነገሡ በኋላ
ከጥቂት አስቸጋሪ ዓመታት በኋላም፤ የመንግሥት ምክር ቤቱ፤ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን እና ሕዝቡም ተሰብስቦ፤ የዳግማዊ ምኒልክን የልጅ ልጅ የሆኑትን ልጅ እያሱን ከመንግሥት ሥልጣናቸው ሽሮ ካሰናበታቸው በኋላ ወይዘሮ ዘውዲቱ በግዞት ከነበሩበት ቦታ ወደ አዲስ አበባ ተጠሩ፡፡
ከዚህ በኋላ ወይዘሮ ዘውዲቱ፤ ንግሥተ ነገሥታት ዘውዲቱ ተብለው በተወለዱ በ40 ዓመታቸው መስከረም 17 ቀን 1909 ዓ.ም የአባታቸውን ዙፋን እንዲወርሱ ተደረገ፡፡
በኋላም፤ የካቲት 4 ቀን 1909 ዓ.ም. አራዳ በሚገኘው በመናገሻ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ከግብፅ በመጡት የኮፕቲክ ጳጳስ አቡነ ማቴዎስ እጅ ቅብዐ መንግሥት ተቀብለው ዘውድ ጫኑ፡፡
በዚያው እለትም፤ ልዑል ራስ ተፈሪም ታላቁን የሰለሞን ኒሻን ተሸልመው ፀሎት ከተደረገላቸው በኋላ ለአልጋ ወራሽነትና ለእንደራሴነት የሚገባውን ክብር በ24 ዓመታቸው ተቀብለዋል፡፡
Abune Matewos
ከግብፅ የመጡት የኮፕቲክ
ጳጳስ አቡነ ማቴዎስ
በ19ኛው እና በ20ኛው ክፍለ ዘመን በዓለም እውቅና ከተሰጣቸው አገሮች መካከከል ኢትዮጵያ አንዷ ስትሆን፤ ንግሥተ ነገሥታት ዘውዲቱ፤ ይህን ከፍተኛ የአገር መሪነት ሥልጣን መጨበጣቸው፤ በአፍሪካ የሥርዓተ መንግሥት የመሪነት ታሪክ ብቸኛዋ ሴት ያደርጋቸዋል፡፡


ልጅ እያሱ ከሥልጣን ወርደው ንግሥተ ነገሥታት ዘውዲቱ ዘውዱን ከጫኑ በኋላ፤ የራስ ጉግሣ ወሌ ወደ ማዕከላዊ ሥልጣን እየቀረቡ መምጣትና የራስ ተፈሪ መኮንን አልጋ የመውረስ ጽኑ ፍላጎት መካከል የስልጣን ሽኩቻው ተጋግሎ ብዙ ውጣ ውረዶች ተከስተዋል፡፡

ንግሥተ ነገሥታት ዘውዲቱ ምኒልክ በሕይዎት በቆዩባቸው ዘመናት፤ እግዚአብሔርን የሚፈሩ፣ ሕግን አክባሪ፣ ለሐይማኖታቸው እጅግ ቀናኢ የነበሩና በጾም በጸሎት ተወስነው የሚኖሩ ቸርና እርኅርኅት ነበሩ፡፡
Leul Ras Teferi Mekonnen
ልዑል ራስ ተፈሪ መኮንን
ንግሥት ዘውዲቱ፤ በንግሥና ዘመናቸው ካከናወኗቸው ዐበይት ሀገራዊ ተግባራት መካከል፤
  1. በንግሥት ዘውዲቱ ፈቃድ መሠረት፤ ባለሙሉ ሥልጣን እንደራሴ የነበሩት ልዑል ራስ ተፈሪ መኮንን፤ ልዑላን መሳፍንትና መኳንንት ያሉበትን ልዑካን እየመሩ ወደ አውሮፓ ሄደው ኢትዮጵያን ከዓለም መንግሥታት ጋር እንድትተዋወቅ አድርገዋል፡፡
  2. ኢትዮጵያ የዓለም መንግስታት ማሕበር(League of Nations) አባል የሆነችው በንግሥት ዘውዲቱ ዘመነ መንግሥት ነው፡፡
  3. ከግብፅ አሌክዛንድሪያ ተሹሞ ይላክ የነበረው የጵጵስና ማዕረግ የቀረው፤ አቡነ ዮሐንስ የተባሉት ጳጳስ፤ ከአሌክዛንድሪያ ኢትዮጵያ ድረስ እንዲመጡ ተደርጎ በሀገሪቱ በኢትዮጵያ ተወላጅ በሆኑ ጳጳስ ለመጀመሪያ ጊዜ አዲስ አበባ ላይ ሾመውና ባርከው እንዲተካ የተደረገው በሳቸው ዘመነ መንግሥት ነው፡፡
  4. የንግሥት ዘውዲቱ የገንዘብ ሚኒስተራቸው፤ ገንዘብ በንግሥቲቱ ስም እንዲታተም ሲጠይቋቸው፤
    “እኔን የኢትዮጵያ ሕዝብ መርጦ ያነገሠኝ ምንም የዋልኩለት ውለታ ኖሮ ሳይሆን ያባቴን ውለታ አስቦ ስለሆነ፤ የአባቴ ስም ተሰርዞ በእኔ ስም እንዲተካ አልፈቅድምና የታተመው ገንዘብ እንደነበረ ይቀጥል፡፡”
    በማለት መልሰውላቸዋል፡፡
  5. በአሁኑ ወቅት በአገልግሎት ላይ የሚገኘው የንግስተ ነገሥታት ዘውዲቱ ሆስፒታል ለሴቶች ማዋለጃ እንዲሆን የተሠራው በንግሥት ዘውዲቱ ዘመነ መንግሥት ነው፡፡
  6. Zewuditu Menilik
    ንግሥተ ነገሥታት ዘውዲቱ
    በዳግማዊ ምኒልክ መታሰቢያ
    ቤተ ክርስቲያን ክብረ በዓል ላይ
  7. አባታቸው ዳግማዊ አፄ ምኒልክ ከሞቱ በኋላ አጽማቸው ከሥዕል ቤት ኪዳነ ምሕረት ቤተ ክርስቲያን ውስጥ አርፎ ቆይቶ ነበር፡፡ በኋላም የበአታ ለማርያም ገዳም ሕንጻ ሥራ በ1909 ዓ.ም. የግንባታው መሠረት ተጣለ፡፡ የሕንፃው ሥራ አሥር ዓመታትን አስቆጥሮ ታኀሣሥ 3 ቀን 192ዐ ዓ.ም ተጠናቀቀ፡፡
    በኋላም ከጎንደር የመጣችው ታቦተ በአታ ለማርያም ወደታነጸው ቤተክርስቲያን በክብር እንድትገባ ከተደረገ በኋላ በዚያው ዕለት የዳግማዊ ዐጼ ምኒልክ አጽም አርፎበት ከቆየው ከሥዕል ቤት ኪዳነ ምሕረት ቤተ ክርስቲያን ወጥቶ በምድር ቤቱ በተዘጋጀላቸው ማረፊያ በክብር ገብቶ እንዲያርፍ ተደርጓል፡፡
    በመጨረሻም የዚህ ገዳም ስያሜ፤ የዳግማዊ ምኒልክ መታሰቢያ ታዕካ ነገሥት በአታ ለማርያም ገዳም ተብሎ እንዲጠራ ተወሰነ፡፡ (....ስለገዳሙ አመሠራረት የበለጠ ለማንበብ ይህን ይጫኑ )
  8. በዓለም ለታወቁ ታላላቅ ነገሥታት ስለውለታቸው ሐውልት እንደሚቆምላቸው ተገንዝበው ኖሮ፤ አሁን በመናገሻ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ፊት ለፊት በሚገኘው የዳግማዊ ምኒልክ አደባባይ ተብሎ በተሰየመው ሥፍራ ላይ፤ የአባታቸው የዳግማዊ ምኒልክ ሐውልት ከጀርመን ሀገር ተሰርቶ መጥቶ፤ የሚቆምበት ቦታ በመደልደል ላይ ሳለ ንግሥቲቱ በድንገተኛ ህመም በማለፋቸው ሐውልቱ ቆሞ ሲመረቅ ለማየት ሳይታደሉ ቀርተዋል፡፡
  9. በኢየሩሳሌም እስከዛሬ ድረስ የኢትዮጵያ ቤት ተብሎ የሚጠራውን ከ9 በላይ ክፍል ያለውን ትልቅ ፎቅ ቤት አሠርተዋል፡፡

  10. ከዚህ በታች የተዘረዘሩትን ልዩ ልዩ አብያተ ክርስቲያናትን አሳድሰዋል፤ አሠርተዋልም፡፡

    1. በዳግማዊ ምኒልክ ዘመነ መንግሥት በጭቃ ተሠርቶ በእርጅና ምክንያት ሊፍርስ የነበረውን የእንጦጦ ማርያም ቤተ ክርስቲያን፣
    2. ከአኩሱም ፅዮን ቤተ ክርስቲያን ቀጥሎ በታላቅ የአምልኮ ሥፍራነቱ የሚነገርለትን የመንበረ ፀባኦት ቅድስ ሥላሴ ካቴድራል የመሠረት ድንጋይ የተቀመጠው በ1920 ዓ.ም. በንግሥተ ነገሥታት ዘውዲቱ ዘመነ መንግሥት ነው፡፡
      Holy Trinity Cathedral Addis Ababa
      በግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዘመነ መንግሥት
      የተሠራው አዲስ አበባ የሚገኘው የመንበረ ፀባኦት
      ቅድስ ሥላሴ ካቴድራል ቤተ ክርስቲያን
      የቤተ ክርስቲያኑ ሥራ ከተጀመረ በኋላ በኢጣሊያ ወረራ ወቅት ተቋርጦ ከነፃነት በኋላ ለኢትዮጵያ ነፃነት ተጋድሎ ላደረጉ መታሰቢያ እንዲሆን በማሰብ በቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዘመነ መንግሥት ተሠርቶ ተጠናቋል፡፡
    3. በእርጅና ምክንያት ሊፍርስ የነበረውን፤ አዲስ አበባ የሚገኘውን ጽርሃ ማሪያም ቅዱስ ሩፋኤልን ቤተ ክርስቲያን፣
    4. አዲስ አበባ የሚገኘውን የደብረ አሚን ተክለ ሐይማኖት ቤተ ክርስቲያን፣
    5. አዲስ አበባ የሚገኘውን በእርጅና ምክንያት ሊፍርስ የነበረውን የዑራኤል ቤተ ክርስቲያን፣
    6. አዲስ አበባ የሚገኘውን የደብረ ሰላም እስጢፋኖስ ቤተ ክርስቲያን፣
    7. አዲስ አበባ የሚገኘውን ጴጥሮስ ወጳውሎስ ቤተ ክርስቲያን፣
    8. አዲስ አበባ የሚገኘውን የደብረ ነገሥት ቁስቋም ቤተ ክርስቲያን፣
    9. የመናገሻ ማሪያምን ቤተ ክርስቲያን፣
    10. የፉሌ መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን፣
    11. ሜታ አቦ የሚገኘውን የወረብ ማሪያምን ቤተ ክርስቲያን፣
    12. የአወሽ ማሪያምን ቤተ ክርስቲያን፤
    13. የኤጀርሳ ለፎ ቅዱስ ገብርኤልን ቤተ ክርስቲያን፣
    14. የየረር ሥላሴን (አድአ) ቤተ ክርስቲያን፣
    15. አዲስ አበባ የሚገኘውን የቅዱስ ዮሴፍን ቤተ ክርስቲያን፣
    16. የአድአ በርጋ አቡነ ተክለ ሐይማኖትን ቤተ ክርስቲያን፣
    17. በንጉሥ ሣኅለ ሥላሴ ተተክሎ በዳግማዊ አፄ ምኒልክ ተሠርቶ የነበረውን የአቃቂ ቀራንዮ መድኃኒአለም ቤተ ክርስቲያን፣
    18. የአያታቸው የንጉሥ ኃይለ መለኮት አጽም ያረፈበትን ጠራ የደብረ በግዕ አቡነ ሕጻን ሞአን ገዳም ቤተ ክርስቲያን፣
The Uncrowned Lij Eyassu
ዘውድ ሳይደፉ የቀሩት ልጅ እያሱ
ንግሥት ዘውዲቱ፤ አባታቸው ዳግማዊ ምኒልክ ለእህታቸው ልጅ ለሆኑት ለልጅ እያሱ ያወረሱትን ዘውድ በመውሰዳቸው፤ የአባታቸውን ትዕዛዝ እንደጣሱ ስለቆጠሩት ደስተኛ እንዳልነበሩና ይፀፀቱ እንደነበረ ይነገራል፡፡
ንግሥት ዘውዲቱ፤ ልጅ እያሱ ከክርስትና ሐይማኖታቸው መገለልና መራቃቸውን ባሰቡት ቁጥር ስቅስቅ ብለው ያለቅሱ ነበር፡፡
ልጅ እያሱ ከሥልጣን ተሽረው ንግሥተ ነገሥታት ዘውዲቱ የአባታቸውን የዳግማዊ ምኒልክ በትረ ሥልጣን እንዲወርሱ ሲደረግ፤ በዘመኑ ከነበሩ መኳንንቶች ውስጥ ደጃዝማች አብረሃም አርአያ የተባሉ ልጅ እያሱ ግቢ ገብተው የልጅ እያሱን መሻር በመቃወም ለማስቸገር ሞክረው ነበር፡፡
ነገር ግን የማያዋጣቸው መሆኑን ሲያወቁ ወዲያውኑ እጃቸውን ሰጥተዋል፡፡
በሌላ በኩል፤ የልጃቸውን የልጅ እያሱን ከሥልጣን መውረድ የሰሙት የወሎው ንጉሥ ሚካኤል የወሎን ሠራዊት አስከትለው ወደ ሸዋ ተጉዘው፤ ከንጉሠ ነገሥቷ የጦር ሠራዊት ጠቅላይ አዛዥ ከሆኑት ከልዑል ራስ ተፈሪ መኮንን ጋር፤ በደብረ ብርሃን መንገድ በሚገኘው ቶራ ተብሎ በሚጠራው መስክ ላይ ጦርነት ገጥመው፤ እንደገና የመጨረሻ ፍልሚያቸውን በደብረ ብርሃን መንገድ ከአዲስ አበባ 87 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በሚገኘውና ሰገሌ ተብሎ በሚጠራው ቦታ ላይ ተደርጎ ጥቅምት 17 ቀን 1909 ዓ.ም. ንጉሥ ሚካኤል ድል ሆነው ተማርከው ተያዙ፡፡
በኋላም ምርኮኛው ንጉሥ ሚካኤል እጃቸው በሰንሰለት ታስሮ አዲስ አበባ ካመጧቸው በኋላ ድንጋይ በትክሻቸው ተሸክመው ንግሥተ ነገሥታት ዘውዲቱ ፊት ቀርበው ንግሥቲቱ እግር ላይ ወድቀው ይቅርታ እንዲጠይቁ ተደርገዋል፡፡
ይህ ሁሉ ድርጊት ሲፈፀም፤ ራስ ተፈሪ መኮንን በቦታው አልተገኙም፡፡ ያልተገኙበትም ምክንያቱ ንጉሥ ሚካኤል፤ የራስ ተፈሪ መኮንን ባለቤት የወይዘሮ መነን አያት በመሆናቸው የተፈፀመውን ድርጊት በአይናቸው ለማየት ህሊናቸው ሊቀበለው ባለመቻሉ እንደሆነ ይታመናል፡፡
ልጅ እያሱም የአባታቸውን መሸነፍ በሰሙ ጊዜ ተበሳጭተው ወደ አፋር ተጉዘው ከቦታ ቦታ ሲንከራተቱ ከቆዩ በኋላ በመጨረሻ እጃቸው ሊያዝ ችሏል፡፡
ልጅ እያሱ ከተያዙ በኋላ ቤተመንግሥት መጥተው በቤተ መንግሥቱ ምድር ቤት ውስጥ እንዲታሰሩ ሆኖ የሐይማኖት ትምህርት እንዲሰጣቸውና ተገቢው እንክብካቤ እንዲደረግላቸው በማለት ንግሥት ዘውዲቱ፤ ለራስ ተፈሪ መኮንንና ለፊታውራሪ ኃብተ ጊዮርጊስ ዲነግዴ ተማጽኖ ቢያቀርቡም ሊፈቀድላቸው አልቻለም፡፡
ይሁን እንጅ ንግሥት ዘውዲቱ፤ ልጅ እያሱ በታሰሩበት ቦታ በሰላሌ፤ ደረጃውን የጠበቀ ልዩ ምግብና የሚያስፈልጋቸው የልብስ አይነት ሁሉ እንዲቀርብላቸው አስደርገዋል፡፡
በንግሥት ዘውዲቱ የአልጋ ወራሽነት ሥልጣን የተሰጣቸው ራስ ተፈሪ መኮንን፤ በጀመሩት ተራማጅ አስተሳሰብ የተነሣ ከንግሥት ዘውዲቱ ጋር የነበራቸው የአመለካከት ልዩነት ከጊዜ ወደ ጊዜ እየሰፋ መጣ፡፡
ንግሥት ዘውዲቱ፤ የነበረው የቀድሞ ሥርዓትና ባሕል ሳይበረዝ ተጠብቆ እንዲቆይ የሚፈልጉ ወግ አጥባቂ አስተሳሰብ ስለነበራቸው የኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያንን ሙሉ ድጋፍ አግኝተው ነበር፡፡
አልጋ ወራሽ ራስ ተፈሪ መኮንን ድግሞ፤ ከውጭው ዓለም ጋር ግንኙነት በመፍጠር፤ ኢትዮጵያ አስተዳደሯ ዘመናዊ እንዲሆንና ከሌሎች ታዳጊ አገራት ጋር እንድትስተካከል የሚፈልጉ በመሆኑ፤ በወጣት መኳንንቶች ዘንድ ተቀባይነት እያገኙ መጡ፡፡
በመካከሉም፤ አልጋ ወራሽ ተፈሪ መኮንን ንጉሥ ሆነው ይሾሙልን የሚል የአድማ ጥያቄ ለንግስቲቱ በመቅረቡ፤ ንግሥቲቱ በጥያቄው ደስተኛ ባይሆኑም ቅሉ አልጋ ወረሹን ጠርተው ካነጋገሩ በኋላ፤ የጎንደር ንጉሥና ባለሙሉ ሥልጣን እንደራሴ ብለው ሾሟቸው፡፡
እየቆየም በንግሥተ ነገሥታት ዘውዲቱና በአልጋ ወራሽ ተፈሪ መኮንን የነበረው ግንኙነት ቀስ በቀስ እየላላ መምጣት ጀመረ፡፡
ንግሥቲቱ፤ በየጊዜው በሚፈጠረው የፖለቲካ መጠላለፍና ውዠንብር የነበራቸውን አስተያየትና ሀሳብ፤ ክቡር ደጃዝማች ከበደ ተሰማ በመጽሐፋቸው እንደገለጹት፤

“(ሕዝቡ) እኔን ሳያውቀኝና ሳልጠቅመው የአባቴን ውለታ ለመመለስ ሲል፤ የኢትዮጵያ መሳፍንትና መኳንንት፤ ሕዝቡም በፈቃደ እገዚአብሔር ታዞ ለአባቴ ዙፋን ቢያበቃኝ፤ ከእኔ አስተዳደር አለማወቅ የተነሳ ሕዝቡ እርስ በርሱ ተፋጅቶ ከሚያልቅና እራሳቸውን አልቻሉም ተብሎ በዘመነ መንግሥቴ፤ የባዕድ መንግሥትና ገዥ ወደ ኢትዮጵያ ከሚገባ፤ እኔ የተጠየኩትን ስልጣን ለቀቄ ነገሩን ማብረድ ይሻላል፡፡“


በማለት ለጊዜው የሚገጥማቸውን ችግር ሁሉ ከፍ ባለ ትዕግሥት ያሳልፉት እንደነበረ ያስረዳሉ፡፡
ይህም የንግሥቲቱ ተግባር ምቹ ሁኔታን በመፍጠሩ፤ የጎንደር ንጉሥና ባለሙሉ ሥልጣን እንደራሴ የሆኑት አልጋ ወራሽ ተፈሪ መኮንን፤ ተራማጅ የፖለቲካ አስተሳሰብ በነበራቸው የፖለቲካ ባለሥልጣናትና ደጋፊዎቻቸው ዘንድ ይበልጥ ተቀባይነት እያገኙና የመሪነት ሥልጣኑንም እያጠናከሩ ሊመጡ ችለዋል፡፡
ራስ ተፈሪ መኮንንም፤ ኢትዮጵያ የዓለም መንግሥታት ማህበር አባል እንድትሆን ሲያደርጉ፤ እንዲሁም የባሪያ አሳዳሪ ሥርዓትን እንዲወገድ ማድረግ ችለዋል፡፡
ንግሥት ዘውዲቱም በተፈጠረው የሥልጣን ሽኩቻ ምክንያት ቀስ በቀስ ከሥልጣናቸው እነዲገለሉ በመደረጉ፤ ፖለቲካውን ትተው ወደ ሐይማኖታቸው በማዘንበል ቤተ ክርስቲያናትንና ገደማትን ማሠራት ጀመሩ፡፡

የቤገምድር ገዥ የነበሩት፤ የእቴጌ ጣይቱ የወንድም ልጅ የሆኑትና የንግሥተ ነገሥታት ዘውዲቱ ባለቤት ራስ ጉግሳ ወሌ፤ በራስ ተፈሪ መኮንን ላይ የተቃውሞ እንቅስቃሴ አስነስተው ራስ ተፈሪ መኮንንን የእንደራሴነት ሥልጣናቸውን ነጥቆ የንግሥቲቱን ሙሉ ሥልጣን ለማስከበር በማሰብ፤ በሁለቱ ወገን መካከል ጦርነት ተካሂዶ በመጨረሻም ራስ ጉግሣ በጦር ምኒስትሩ በራስ ተፈሪ መኮንን ዘመናዊ ጦር ድል ሆነው ሊገደሉ ችለዋል፡፡

ንግሥተ ነገሥታት ዘውዲቱም፤ የነበረባቸው የስኳር በሽታ በመወሳሰቡ ምክንያት ሕመሙ በርትቶባቸው ስለነበረ፤ ራስ ጉግሣ ድል መሆናቸውን ከሰሙ በኋላ ረቡዕ መጋቢት 24 ቀን 1922 ዓ.ም. ምንም ዘር ሳይተኩ በተወለዱ በ56 ዓመታቸው ሕይወታቸው ሊያልፍ ችሏል፡፡
ሥርዓተ ቀብራቸውም ለአባታቸው ለዳግማዊ ምኒልክ መታሰቢያ ባሠሩት በታዕካ ነገሥት ባዓታ ለማሪያም ገዳም እንዲያርፍ ተደርጓል፡፡
አልጋ ወራሽ ተፈሪ መኮንንም ንግሥቲቱ ካረፉ ከ7 ወራት በኋላ ዕሁድ ጥቅምት 23 ቀን 1923 ዓ.ም.“ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ንጉሠ ነገሥት ዘኢትዮጵያ” ተብለው በንግሥቲቱ ዙፋን ተተክተው በትረ ስልጣኑን ሙሉ ለሙሉ ተረክበው ነገሡ፡፡





ምንጭ፤
  1. "አጤ ቴዎድሮስ" ደራሲ፡- ጳውሎስ ኞኞ ግንቦት ወር 1985 ዓ.ም.
  2. "የኢትዮጵያ ታሪክ ከ 1847 እሰከ 1983" ደራሲ፡- ፕሮፌሰር ባሕሩ ዘውዴ
  3. “የታሪክ ማስታዎሻ” ደራሲ፡- ደጃዝማች ከበደ ተሰማ 2ኛ ዕትም ሐምሌ 2007 ዓ.ም.