Content-Language: am ግርማዊ ቀዳማዊ አፄ ኃይለ ሥላሴ ገጽ አንድ
header image


ግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ምንም እንኳን በአገዛዝ ዘመናቸው ወቅት የታሪክ ተወቃሽ የሚያደርጓቸው ህፀፆች ባይጠፉም፤ በዘመናዊው የኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ አገራቸውን ለማዘመን የጣሩ፣ የበለፀገ የዲፕሎማሲ ዕውቀታቸውን በመጠቀም ሀገራችን ኢትዮጵያን በዓለም አቀፍ ደረጃ እንድትታወቅ ታላቅ አስተዋጽዖ ያበረከቱ፣ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት እዲመሠረት ግምባር ቀደም ሚና የተጫወቱ፣ የመጀመሪያው የድርጅቱ ሊቀመንበርም በመሆን ታላቅ የመሪነት ችሎታቸውን ያሳዩና በአጠቃላይ ለሀገራቸውና ለአፍሪካ ትርጉም ያለው ለውጥ በማምጣት ረገድ አኩሪ ታሪክ ሠርተው ያለፉ ታላቅ መሪ ነበሩ፡፡


(ድረ ገጽ 1)

ግርማዊ ቀዳማዊ አፄ ኃይለ ሥላሴ



Emperor-Haile-Selassie
The image is digitally edited by the webmaster









የግርማዊ ቀዳማዊ አፄ ኃይለሥላሴ የአስተዳደር፣
የአመራር ጥበብና የሕይዎት ዘመን ትረካ
በአስር ክፍል ተዘጋጅቶና በየአርዕሰቱ የሚገኘውን የድምጽ
ማጫወቻ በመጠቀም ትረካውን ማዳመጥ ይችላሉ

ክፍል አንድ

ትውልድ እድገትና ሹመት፣ የሥልጣን ሽኩቻ፣ ሥርዓተ ንግሥ፣ ከኢጣሊያ ወረራ በፊት ያከናወኗቸው ዐበይት ተግባራትና የኢጣሊያና የኢትዮጵያ የጦር መሣሪያ ትጥቅ

ክፍል ሁለት

ኢጣሊያ በኢትዮጵያ ላይ ያወጀው የጦርነት አዋጅ፣ በሰሜን ኢትዮጵያ የተከፈተው የኢጣሊያ ወረራ፣ አዲግራት፣ ዐድዋና መቀሌ በጠላት እጅ መውደቅ፣ በሰሜን ጦር ግንባር የኢትዮጵያ ጦር ተጋድሎና ውጤቱ

ክፍል ሶስት

የማይጨው ጦር ግንባርና የመጨረሻው ውጤት፣ ንጉሠ ነገሥቱ
በማይጨው ጦርነት የነበራቸው ተሳትፎ፣ በደቡብ ኢትዮጵያ ከጠላት ጋር የተዋጋው የሐረርጌ ጦር ግንባር

ክፍል አራት

የኢትዮጵያ የደቡብ ጦር ግንባር የማጥቃት እርምጃ፣ የዐድዋ ድል ለምን ሳይደገም ቀረ?፣ በጦርነቱ የኢትዮጵያ ሠራዊት የፈፀመው ተጋድሎ፣ የንጉሠ ነገሥቱ ስደትና አዲስ አበባ በጠላት እጅ መውደቅ

ክፍል አምስት

ዶክተር መላኩ በያን የፈፀመው የአርበኝነት ተግባር፣ የአብርሃም ደቦጭና የሞገስ አስገዶም ተጋድሎ፣ ፋሽስት ኢጣሊያ በአዲስ አበባ ንፁሃን ላይ የወሰደ የበቀል እርምጃ

ክፍል ስድስት

የፋሽስት ኢጣሊያ ከፋፋይ ተግባራት ሲዳሰሱ፣ ኢትዮጵያውያን የውስጥ አርበኞች ያበረከቷቸው ጉልህ ተግባራት፣ የንጉሠ ነገሥቱ ከስደት ወደ አገራቸው መመለስ

ክፍል ሰባት

እንግሊዞች በኢትዮጵያ ላይ ያደረሱት አሉታዊ ተጽዕኖ፣ እንግሊዞች ወደ ኢትዮጵያ ከገቡ በኋላ ድብቅ ፖለቲካዊ ዕቅዳቸው ምን ነበር?፣
የኤርትራና የኦጋዴን የይገባኛል ጥያቄ እና ውጤቱ

ክፍል ስምንት

የኢትዮጵያና የአሜሪካ ዲፕሎማሲያዊ
ግንኙነት አጀማመር፣ በንጉሠ ነገሥቱ
ላይ የተካሄዱ አድማዎች

ክፍል ዘጠኝ

የ1953ቱ የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራ፣
በንጉሠ ነገሥቱ ላይ የተቀጣጠለው አመፅ ሲዳሰስ፣ የንጉሠ ነገሥቱ መታሰርና በባልስልጣናቱ ላይ የተፈፀመው ግድያ

የመጨረሻ ክፍል

በደርግ ኢፍትሀዊ ውሳኔ መሠረት ያለፍርድ የተገደሉት ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናት፣ ጀነራል አማን ሚካኤል አንዶም ለምን ተገደሉ?፣ የንጉሠ ነገሥቱ አሟሟትና የቀብር ሥነ ሥርዓት



Teferi-Mekonnen-at-child-age
ልዑል ራስ ተፈሪ መኮንን
በ7 ዓመት የህፃንነት እድሜያቸው

ለፎቶው ምስጋና፤ Getish Ras Teferi
ልጅ ተፈሪ መኮንን፤ ሐምሌ 16 ቀን 1884 ዓ.ም. ሐረር ጠቅላይ ግዛት ውስጥ በሚገኘው ኤጀርሳ ጐሮ በሚባል ሥፍራ ተወለዱ፡፡
አባታቸው፤ ልዑል ራስ መኮንን ወልደ ሚካኤል ይባላሉ፡፡
31 ዓመት በንግሥና የቆዩትና የዳግማዊ አፄ ምንይልክ አባት የሆኑት የሸዋው ንጉሥ ኃይለ መለኮት ሳህለ ሥላሴ፤ የራስ መኮንን ወልደ ሚካኤል አጎታቸው (የእናታቸው ወንድም) ናቸው፡፡
የራስ መኮንን ወልደ ሚካኤል እናት ልዕልት ተናኘ ወርቅ ደግሞ፤ የንጉሥ ኃይለ መለኮት እህት ሲሆኑ፤ የዳግማዊ አፄ ምኒልክም አክስት ናቸው፡፡
በሌላ በኩል ልጅ ተፈሪ መኮንን ደግሞ፤ የዳግማዊ አፄ ምኒልክ የአክስታቸው የልጅ ልጅ ናቸው፡፡
የልጅ ተፈሪ መኮንን እናት፤ ወይዘሮ የሽእመቤት ይባላሉ፡፡
ልጅ ተፈሪ መኮንን በተወለዱ በአራተኛው ወር፤ የአባታቸው የእህት ልጅ ከሆኑት ከራስ ዕምሩ ጋር በአንድነት አደጉ፡፡ ሁለቱም እድሜአቸው 7 ዓመት ሲሞላቸው፤ አስተማሪ እቤታቸው ድረስ እየመጣላቸው መማር ጀመሩ፡፡
ልጅ ተፈሪ መኮንን፤ በተወለዱ በ10 ዓመታቸው በአማርኛና በግዝ ማንበብና መፃፍ ቻሉ፡፡
የልጅ ተፈሪ መኮንን እናት ወይዘሮ የሽእመቤት፤ ገና የ30 ዓመት እድሜ ሳሉ በህመም ምክንያት ከዚህ ዓለም በሞት ተለዩ፡፡
ልጅ ተፈሪ መኮንን፤ ከአባታቸው ጋር የነበራቸው ፍቅር ጠንካራና ለአባታቸውም ታዛዥ ስለነበሩ ዘወትር ይመርቋቸው ነበር፡፡

Teferi Mekonnen at the age of ten
ልጅ ተፈሪ መኮንን
በ10 ዓመት እድሜያቸው
Photo Credit to: image link
ፊታውራሪ ተክለ ሐዋርያት ተክለ ማርያም ስለ ህጻኑ ተፈሪ ሲጽፉ፤
“ተፈሪ በባሕሪው ገና ከሕፃንነቱ ጀምሮ እንደ ዐዋቂ ሰው ነው:: እንደ ልጅ አይደለም። ጭምት፣ አስተዋይና ዝምተኛ ነው። ሁል ጊዜ ከንፈሮቹን ፈልቀቅ ያደርጋል እንጅ ከትከት ብሎ አይስቅም፡፡ መቅበጥ፣ መጮህ አይፈቅድም።” በማለት ገልፀዋቸዋል፡፡...(የበለጠ ለማንበብ➝ Getish Ras Teferi) ልጅ ተፈሪ መኮንን፤ በተወለዱ በ13 ዓመታቸው ለማዕረጉ ሲባል ብቻ የደጃዝማችነት ሹመት ተሰጣቸው፡፡
ደጃዝማች ተፈሪ መኮንን የፈረንሣይኛ ቋንቋ ተከታትለዋል፡፡
ደጃዝማች ተፈሪ መኮንን፤ የአባታቸውን ንግግርና ምክር ስለሚሰሙና በእድሜያቸው ትንሽነት የተነሳ የሚያስከትለውን ማናቸውንም ሥራ በጥንቃቄ በመሥራታቸው፤ አባታቸውም ሆኑ ሌሎች ሹማምንቶችና መኳንንቶች ይወዷቸው ነበር፡፡
ደጃዝማች ተፈሪ መኮንን የ14 ዓመት ልጅ ሳሉ፤ አባታቸው ልዑል ራስ መኮንን ወልደ ሚካኤል፤ ባደረባቸው ሕመም ምክንያት ከዚህ ዓለም በሞት ተለዩ፡፡
ቀብራቸውም እርሳቸው ባሰሩት በቁልቢ ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ተፈፀሟል፡፡

ዳግማዊ ምኒልክ ለኢትዮጵያ ልጆች የውጭ አገር ቋንቋ የሚማሩበት ትምህርት ቤት ከፍተው ስለነበር፤ ደጃዝማች ተፈሪ መኮንንም እንዲማሩ ጥያቄ አቅርበው ስለተፈቀደላቸው ትምህርታቸውን ጀመሩ፡፡
የደጃዝማች ተፈሪ መኮንን አባት ራስ መኮንን ሲሞቱ፤ የልጅ ተፈሪ መኮንን የአባታቸው ልጅ የሆኑት ወንድማቸው ደጃዝማች ይልማ፤ የሐረር አስተዳዳሪ ሆነው ተሾሙ፡፡ ደጃዝማች ተፈሪ መኮንን ደግሞ የሰላሌ ገዥነትን ተሾሙ።
ነገር ግን በቤተ መንግሥት ፖለቲካ ምክንያት፣ አዲስ አበባ በሚገኘው የአፄ ምኒልክ ቤተ መንግሥት ውስጥ ተወስነው በመቅረታቸው፣ የቤተ መንግሥቱን ፖለቲካዊ እንቅስቃሴንና ጥበብን መማር ቻሉ፡፡
ከደጃዝማች ተፈሪ ደጋፊዎች መካከል አንዱ የሆኑት ዳግማዊ አፄ ምኒልክ ሲታመሙ፤ (ተፈሪን ከቤተ መንግሥት ለማራቅ ይመስላል) "በግዞት" ደቡብ ኢትዮጵያ ወደሚገኘው ወደ ሲዳሞ ጠቅላይ ግዛት ተዛውረው አስተዳዳሪ ሆነው እንዲሠሩ ወደሥፍራው ተላኩ። ሲዳሞ በነበሩበትም ወቅት ቁጥሩ 3 ሺህ የሚደርስ ሠራዊት ነበራቸው።
የሐረር አስተዳዳሪ ሆነው የተሾሙት ደጃዝማች ይልማም ሥልጣን እንደያዙ ብዙም ሳይቆዩ ከዚህ ዓለም በሞት ተለዩ። በኋላም ደጃዝማች ተፈሪ የአባታቸውን ግዛት ሐረርን እንዲያሰተዳድሩ በአቴጌ ጣይቱ ሹመት ተሰጣቸው፡፡

Leul Ras Teferi Mekonnen
ንግሥት ዘውዲቱ የአልጋ ወራሽነት ሥልጣን የተሰጣቸው ልዑል ራስ ተፈሪ መኮንን፤ በጀመሩት ተራማጅ አስተሳሰብ የተነሣ ከንግሥት ዘውዲቱ ጋር የአመለካከት ልዩነት እንደነበራቸው ይነገራል፡፡
ንግሥት ዘውዲቱ፤ ሲሰራበት የቆየው አሮጌው የአሠራር ሥርዓትና ልማድ ሳይበረዝ ተጠብቆ እንዲቆይ የሚፈልጉ ስለነበሩ፤ በኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን እና የቀድሞው አስተዳደራዊ ሥርዓት ሳይፋለስ እንዲቀጥል በሚፈልጉ መሳፍንትና መኳንንት ዘንድ ሙሉ ድጋፍ አግኝተው ነበር፡፡
በሌላ በኩል ድግሞ፤ ተፈሪ መኮንን ከውጭው ዓለም ጋር ግንኙነት በመፍጠር፤ ኢትዮጵያ፤ አስተዳደሯ ዘመናዊ እንዲሆንና ከሌሎች ታዳጊ አገራት ጋር እንድትስተካከል የሚፈልጉ በመሆኑ፤ በወጣት መኳንንቶችና ተከታዮቻቸው ዘንድ ተቀባይነት እያገኙ መጡ፡፡
በመካከሉም፤ ተፈሪ መኮንን ንጉሥ ሆነው ይሾሙልን የሚል የአድማ ጥያቄ ለንግሥቲቱ በመቅረቡ፤ ንግሥቲቱ በጥያቄው ደስተኛ ባይሆኑም ቅሉ ተፈሪ መኮንንን ጠርተው ካነጋገሩ በኋላ፤ የጐንደር ንጉሥና ባለሙሉ ሥልጣን እንደራሴ ብለው ሾሟቸው፡፡
ቀስ በቀስም ሁለት ተቃራኒ አስተሳሰብ የሚያራምዱ አካላት፤ ውስጥ ውስጡን በሚያካሂዱት የሥልጣን ትግል ምክንያት በንግሥተ ነገሥታት ዘውዲቱና በተፈሪ መኮንን መካከል የነበረው ጥሩ ግንኙነት፤ እየላላ መምጣት ጀመረ፡፡
መስከረም 17 ቀን 1909 ዓ.ም. መኳንንቱ ከነሠራዊቱ፣ ጳጳሱና እጨጌው ከነካህናቱ በአንድነት ሆነው፤
አንደኛ:- ልጅ እያሱ ከሥልጣናቸው እንዲሻሩ፣
ሁለተኛ:- ንግሥተ ነገሥታት ዘውዲቱ፤ የዘውዱንና የዙፋኑን ክብር ብቻ ይዘው እንዲቀመጡ፤
ሦስተኛ:- ደጃዝማች ተፈሪ ደግሞ፤
የኢትዮጵያ አልጋወራሽና ባለሙሉ ሥልጣን እንደራሴነቱን ይዘው፤ የመንግሥቱን ሥራ ሁሉ እንዲያከናውኑ፣
የጦር አለቆችን እንዲሾሙና እንዲሽሩ፣
በችሎት አደባባይ እየተቀመጡ ዳኞች የፈረዱትን የሲቪልና የወንጀል ይጋባኙን ሁሉ እንዲፈርዱ፣
እንዲሁም ከውጭ አገር መንግሥታት ጋር የሚያገናኘውን ማንኛውንም ጉዳይ ሁሉ እንዲያስፈጽሙ፣
በደንብ መልክ ተዘጋጅቶና ተወስኖ ተሰጣቸው፡፡
በዚህም መሠረት አልጋ ወራሽ ተፈሪ መኮንን፤
  • አንደኛ:- በኢትዮጵያ ያለው ማዕድን ተቀብሮ ከሚቀር እየወጣ እንዲሰራበት በማሰብ ‘ባዬር’ ለሚባል የፈረንሳይ ኩባንያ ውል በመስጠታቸው፣
  • ሁለተኛ:- አይሮፕላን ከፈረንሳይ አገር ገዝተው በማስመጣት ሰዎችንና የፖስታ መልዕክቶችን እዲያመላልስ በማድረጋቸው የተነሣ፣
አልጋ ወራሽ ተፈሪ መኮንንን የሚቃወሙት ወገኖች፤ በአገራችን ላይ ጉዳት የሚያደርስ ሥራ እየሠሩ እንደሆነና አይሮፕላኑም የተገዛው፤ የንግሥትን ወገን ሁሉ በአይሮፕላን ፈጅቶ ዘውዳቸውንና ዙፋናቸውን በኃይል ሊወስድባቸው ነው የሚል ወሬ በማሶራት ከፍተኛ ችግር ፈጥረውባቸው ነበር፡፡
ይህም መከፋፈል የተፈጠረው፤ በዕለት እንጀራ ፈላጊ በሆኑና ነገር ከወዲያ ወዲህ በሚያመላልሱ ነገረኞች ምክንያት መሆኑ ይታወቅ ነበር፡፡
በዚህም የተነሳ፤ እነገሌ የላይኛው ቤተ መንግሥት ወገኖች ናቸው፤ እነገሌ ደግሞ የታችኛው ቤተ መንግሥት (የአልጋ ወራሽና የፊታውራሪ ሐብተ ጊዮርጊስ) ወገኖች ናቸው በመባባል ከፍ ያለ መለያየትና ብጥብጥ ይፈጠር ነበር፡፡
ይሁን እንጅ ንግሥቲቱ፤ ሠላምና ፀጥታን ፈላጊ በመሆናቸው ሁሉኑም ነገር በብልሀት በመያዝ፣ በየጊዜው የሚቀጣጠለውን ነገርና ሽብር ሁሉ ወደ ከፋ ደረጃ ሳይደርስ በታላቅ ትዕግሥት ያበርዱት እነደነበረ ይነገራል፡፡
ልዑል ራስ ካሣ ኃይሉም፤ በአንዳነድ ሰዎች የተንኮል ምክር ምክንያት ሥራ ሳይሠራ በመሰናከሉ፤ አገሪቱ ከዘመናዊ ሥልጣኔ ወደ ኋላ በመቅረቷ ያዝኑ ስለነበረ፤ አልጋ ወራሽ ተፈሪ መኮንን ቀደም ሲል በተሠጣቸው የስራ ደንብ መሠረት ቢሰሩ ለአገር የሚጠቅም መሆኑን ለንግሥቲቱ ያስረዷቸው ስለነበረ፤ ንግሥቲቱ የሌሎችን ሀሳብ ችላ እያሉ መጡ፡፡
አልጋ ወራሽ ተፈሪ መኮንንም፤ ተራማጅ የፖለቲካ አስተሳሰብ በነበራቸው የፖለቲካ ባለሥልጣናትና ደጋፊዎቻቸው ዘንድ የሚያከናውኗቸው ሥራዎች ይበልጥ ተቀባይነት እያገኙና የአገር መሪነት ሥልጣኑንም እያጠናከሩ መምጣት ጀመሩ፡፡

Ras Gugsa Araya
የንግሥት ዘውዲቱ ባለቤት የነበሩት
ራስ ጉግሣ አርዓያ
የ32 ዓመት ዕድሜ ባላቸው በንጉሥ ተፈሪ እና በንግሥት ዘውዲቱ ባል በሆኑት በ 53 ዓመቱ በራስ ጉግሳ ወሌ መካከል፤ የማዕከላዊ መንግሥቱን ሥልጣን ለመጨበጥና አገሪቱን ለመምራት የከረረ የሥልጣን ፉክክር ተፈጠረ፡፡
ራስ ጉግሣ ወሌ ብጡል የንግሥት ጣይቱ የወንድማቸው ልጅ ናቸው፡፡
ራስ ጉግሳ ወሌና መሰሎቻቸው በልዑል አልጋ ወራሽ ተፈሪ መኮንን መንገሥ ፍጹም ደስተኛ አልነበሩም፡፡
በዚህም ምክንያት ራስ ጉግሳ ወሌ የንግሥት ዘውዲቱን ፍላጐት ማለትም፤ ነባሩ የአስተዳደር ሥርዓት ሳይፋለስ ማቆየት የሚለውን አስተሳሰብ በማራመድ ሚስታቸውን ለመደገፍ ማሳደሙን ቀጠሉበት፡፡
ራስ ጉግሳ አልጋ ወራሽ ተፈሪ መኮንንን በጦርነት አሸንፈው፤ ንጉሥ ሆነው አገሪቱን ከንግሥቲቱ ጋር መምራት እንደሚችሉ ራሳቸውን ስላሳመኑ የአመጽ እንቅስቃሴአቸውን ተያያዙት፡፡
ራስ ጉግሳ፤ ንግሥቲቱን የሚደግፉትን ወገኖች ለራሳቸው እንዲወግኑ በማስተባበርና ንጉሥ ተፈሪም አገር ለመምራት የማይበቃ፤ ገና በዕድሜ ያልበሰለና ዘመናዊነትን ያለቅጥ የሚያራምድና ራሱንም ወደ ሮማን ካቶሊክ የለወጠ ነው ብሎ በማሶራት ቅስቀሳቸውን ተያያዙት፡፡
ለትግራይ ገዥዎች፤ ለራስ ስዩም መንገሻና ለራስ ጉግሳ አረአያ ሥለሴ፤ እነዲሁም ለጐጃሙ ገዥ ለራስ ኃይሉ ተክለሐይማኖት አመፃቸውን እንዲደግፉላቸው ደብዳቤ ሲጽፉላቸው ሦስቱም ገዥዎች ሀሳባቸውን የደገፉላቸው መስለው ታይተው ነበር፡፡
በኋላ ግን ሦስቱም ገዥዎች ለድባዳቤው መልስ ባለመስጠት ራስ ጉግሳን ሳይተባበሯቸው ቀሩ፡፡
ንግሥት ዘውዲቱ በበኩላቸው፤ በሁለቱ ወገኖች መካከል ጦርነት እንዲቀሰቀስ ስለማይፈልጉ፤ ከራስ ጉግሳ በተቃራኒ በመቆም፤ ጦርነት እንዳይጀመር ራስ ጉግሳን ቢማጸኑም ተቀባይነት ሳያገኙ ቀሩ፡፡
በዚህም የተነሣ፤ ንግሥቲቱ ባላቸውን ትተው አልጋ ወራሽ ተፈሪ መኮንንን መደገፍ ጀመሩ፡፡
ከዚህ በኋላ ንግሥት ዘውዲቱ እና አልጋ ወራሽ ተፈሪ መኮንን በአንድነት ሆነው፤ ራስ ጉግሳ ወሌ በመንግሥት ላይ ያመጹ ከሀዲ መሆናቸውን የሚገለጽ አዋጅ አሳወጁ፡፡
በተጨማሪም የራስ ጉግሳን የአመፃ ተግባር ቤተክርስቲያን የማትደግፈው መሆኑን የኮፕቲኩ አቡነ ቄርሎስና ሌሎች አምስት ጳጳሳት በአንድነት ሆነው፤ ራስ ጉግሳን የሚደግፍና የእርሱን ሀሳብ የተከተለ ሁሉ የተረገመ፣ ቤተክርስቲያን የማትቀበለውና የተወገዘ መሆኑን በጽሁፍ ከተዘጋጀ በኋላ ቤገምድር ለሚገኙ ገዳማት ሁሉ እንዲደርስ ተደረገ፡፡
ቀደም ሲል ንግሥት ዘውዲቱና አልጋ ወራሽ ያወጡት አዋጅና ቤተክርስቲያን ያወጣችው ውግዘት በአንድ ላይ ሕዝቡ እንዲያውቅ በአይሮፕላን ተበተነ፡፡
ራስ ጉግሳም፤ ጦራቸውን ይዘው ለውጊያ ቤገምድርን አቋርጠው ወደ ሸዋ ግዛት ገሠገሡ፡፡
በመጨረሻም የንጉሥ ተፈሪ ጦርና የራስ ጉግሳ ጦር፤ በሰሜን ወሎ በሚገኘው ደብረ ዘቢጥ ተብሎ በሚጠራው ሥፍራ አንችም በተባለው ሜዳ ላይ፤ መጋቢት 22 ቀን 1922 ዓ.ም. በማእካለዊው መንግሥት በኩል 20,000 ጦር፤ በራስ ጉግሳ ወገን፤ 10,000 ጦር ተሰልፎ ከጧቱ በ 3 ሰዓት ጦርነቱ ተጀመረ፡፡
በማዕከላዊው መንግሥት በኩል የተሰለፉት የጦር አዛዦች፤
 ፊታወራሪ (በኋላ ደጃዝማች) ወንድወሰን ካሣ (የልዑል ራስ ካሣ ኃይሉ ልጅ)፣
 ቀኛዝማች (በኋላ ደጃዝማች) አያሌው ብሩ የሰሜን ጦር አዛዥ፣
 ፊታውራሪ ፍቅረማሪያም የወሎ ጦር አዛዥ፤
ነበሩ፡፡
በ1921 ዓ.ም. ንጉሥ ተፈሪ የመጀመሪያውን አየር ኃይል በማቋቋም ላይ ስለነበሩ በዚህ ጦርነት በታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ ማእካለዊው መንግሥት ቦምብ ጣይ አይሮፕላኖችን ተጠቅሟል፡፡
ከአራት ሰዓት ውጊያ በኋላ የራስ ጉግሳ ወሌ ጦር ተሸንፎ መበታተን ጀመረ፡፡
ራስ ጉግሳ እጃቸውን እንዲሰጡ ቢጠየቁም አሻፈረኝ ብለው ውጊያውን ቀጠሉ፡፡
በመጨረሻም ራስ ጉግሳ ብዙ ቦታ ላይ በጥይት ተደብድበው ተገደሉ፡፡

The Royal Corronation of His Emperial Majesty Haile Selassie
ልዑል ራስ ተፈሪ መኮንን
ከባለቤታቸው ከወይዘሮ መነን ጋር
ሥርዓተ ንግሣቸውን በመናገሻ ገነተ ጽጌ
ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ሲፈጽሙ
ንግሥተ ነገሥታት ዘውዲቱ ምኒልክ የአባታቸውን ዙፋን ወርሰው ለ 13 ዓመት ከ 6 ወር አገሪቱን ሲገዙ ከቆዩ በኋላ በህመም ምክንያት በማረፋቸው፤ በእርሳቸው ምትክ አልጋ ወራሽ ተፈሪ መኮንን እንዲነግሡ ተደረገ፡፡
የዘውድ በዓል አከባበሩም ፕሮግራም ንግሥት ዘውዲቱ ካረፉ በኋላ በ7ኛው ወር ጥቅምት 23 ቀን 1923 ዓ.ም. እንዲሆን ተወሰነ፡፡
የዘውድ በዓሉ ከሚከበርበት ቀን በፊት በኢትዮጵያ አውራጃዎች ሁሉ የሚገኙ አገረ ገዥዎችና ሹሞች ተከታዮቻቸውን ይዘው የአዲስ አበባን ከተማ በሰው ሞልተውት ነበር፡፡
የዘውድ በዓሉ በሚከበርበት የዋዜማው ቀን ምሽት ንጉሠ ነገሥቱ ከግራማዊት እቴጌ መነን ጋር በመሆን ልዑላን ልጆቻቸውን አስከትለው በመናገሻ ገነተ ጽጌ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ከሄዱ በኋላ ሌሊቱን ጳጳሳቱና ቀሳውስቱ ሥርዓተ ንግሥ ሲያደርሱ አደሩ፡፡
በዘውድ በዓሉ አከባበር ተሳታፊ እንዲሆኑ ከተጋበዙትና በሥነሥርዓቱ ላይ ከታደሙት የአለም መንግሥታት እነደራሴዎችና ተወካዮች መካከል፤
የእንግሊዝ፣ የአሜሪካ፣ የፈረንሣይ፣ የጃፓን፣ የጀርመን፣ የኢጣሊያ፣ የግሪክ፣ የስዊድን፣ የሆላንድ፣ የቤልጅየም እና የግብጽ፣ ይገኙበታል፡፡

The Royal Corronation of His Emperial Majesty Haile Selassie
በንጉሠ ነገሥቱ በስተቀኝ የቆሙት
ፊታውራሪ ኃብተ ጊዮርጊስ ሲሆኑ
ጉሠ ነገሥቱ በሥነ ስርዓቱ ወቀት
የውጭ እንግዶችን ሲተዋወቁ
በማግሥቱም ጥቅምት 23 ቀን 1923 ዓ.ም.፤
በቅድሚያ ሊቀ ጳጳሱ በወርቅና በአልማዝ ያጌጠውን ሠይፍ አንስተው፤ “በዚህ ሠይፍ አመፀኞችን ቅጣበት፤ ፈቃደኞችን ሹምበት፣ እውነተኛ ፍርድ ፍረድበት” ብለው ለንጉሠ ነገሥቱ ሲሰጧቸው በቀኝ ጎናቸው ታጠቁት፡፡
ቀጥሎም ሊቀ ጳጳሱ ከባረኩት በኋላ በትረ መንግሥቱን ለንጉሠ ነገሥቱ ሲሰጧቸው በቀኝ እጃቸው ያዙት፡፡
አከታትለውም ንጉሠ ነገሠቱ ባለ አልማዝ ቀለበት፣ ሁለት ባለወርቅ ጦሮችና በወርቅ ያጌጠ መጽሐፍ ቅዱስ ይዘው፤ ልብሰ መንግሥቱን ለብሰው ቅብዓ ሜሮን ከተቀቡ በኋላ፤ ሊቀ ጳጳሱ ጸልየው ሲጨርሱ ወደ ንጉሠ ነገሥቱ ቀርበው፤
“ይህን ዘውድ የጽድቅና የምስጋና ዘውድ ያድርግልዎ” ብለው የወርቁን ዘውድ በንጉሠ ነገሥቱ ራስ ላይ ከደፉላቸው በኋላ፤
“ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ሥዩመ እግዚአብሔር ንጉሠ ነገሥት ዘ ኢትዮጵያ” ተብለው የሰሎሞናዊው ሥርዎ መንግስት 225ኛው ትውልድ በመሆን ነገሡ፡፡
ቀጥሎም ለግርማዊት እቴጌ መነን የሚገባው ሥርዓት ከተደረገ በኋላ የአልማዝ ቀለበት አጥልቀውና ልብሰ መንግሥት አልብሰው፤ መዘምራኑ የሚገባውን መዝሙር ዘምረው ሲጨርሱ ሊቀ ጳጳሱ ዘውዱን በእቴጌይቱ ራስ ላይ ጫኑላቸው፡፡
እቴጌይቱም ዘውዱን ከጫኑ በኋላ ወደ ንጉሠ ነገሥቱ ቀርበው አጅ ነስተው በንጉሠ ነገሥቱ ቀኝ በኩል በተዘጋጀው የወርቅ ወንበር ላይ ተቀመጡ፡፡
በዚሁም ዕለት ልዑል አልጋ ወራሽ አስፋ ወሰን ለአልጋ ወራሽነት የሚገባውን የወርቅ አከሊል ደፉ፡፡
ከዚህ በኋላ መሳፍንቱና መኳንንቱ ሁሉ ሺህ ዓመት ያንግስዎ እያሉ እጅ ከነሡ በኋላ ሥነ ሥርዓቱ ተጠናቆ ንጉሠ ነገሥቱና እቴጌይቱ በወርቅ ሠረገላ ተቀምጠው በተሰለፈው ሕዝብ መሀል ወደ ታላቁ ቤተ መንግሥት አመሩ፡፡
ታላቁ ቤተ መንግሥትም እንደደረሱ 101 ጊዜ መድፍ ከተተኮሰ በኋላ ከውጭ አገር ለመጡ እንግዶች፣ ለመሳፍንቱ፣ ለመኳንንቱና ለዘውዱ በዓል ታዳሚ ሹማምንቶች ታላቅ ግብዣ ተደረገ፡፡
በዕለቱም የአዲስ አበባ ከተማ በንጉሠ ነገሥቱና በእቴጌይቱ ፎቶ በልዩ ልዩ ቀለማት አሸብርቃና በመብራት ደምቃ ትታይ ነበር፡፡

አልጋ ወራሽ ተፈሪ መኮንን ያከናወኗቸው አበይት ተግባራት


  1. ከ 1913 ዓ.ም. ጀምሮ የምኒስቴር መሥሪያ ቤቶችን በአዲስ መልክ በማደራጀት፣ የሥራ ደንብና መመረያ ማዘጋጀትና ለሚኒስትሮች የውጭ አገር የሥራ አማካሪዎችን መቅጠር፣
  2. ቀደም ሲል በፍትሐ ነገሥት ተጽፎ የኖረውን፤ እጅና እግርን የመቁረጡን የጭካኔ ቅጣት በማስቀረት ለፍርድ ቤቶች የተሻሻለ የአሠራር ደንብ ማውጣት፣
  3. ቀደም ሲል ወንጀል የፈፀሙ ሰዎችን በገንዘብም ሆነ በእሥር ለመቅጣት የነበረው ልማድ፤ ምንም ደንብ ስላልነበረው፤ ዳኛው በመሰለው መንገድ ለመፍረድ የሚያስችለውን ገደብ የሌለው ሥልጣኑን በማስቀረት፤ የፍርድ ሂደቱ በ 1923 ዓ.ም. በወጣው የወንጀለኛ መቅጫ ደንብ መሠረት እንዲሠራ ማድረግ፣
  4. የአገር ውስጥና የውጭ አገር ሰዎች ሲጣሉ ጉዳዩን የሚያይ የዳኝነት ቤት ማቋቋም፣
  5. ቀደም ብሎ በአፄ ምኒልክ ጊዜ የነበረው የመጽሐፍ ማተሚያ መሣሪያ በቂ ስላልነበረና አብዛኛው መጽሐፍ በእጅ ይጻፍ ስለነበረ በ 1914 ዓ.ም. ተጨማሪ ሁለት ማተሚያ መሣሪያዎችን በግል ገንዘባቸው ገዝተው ብርሃንና ሰላም እና ከሳቴ ብርሃን የተሰኙ ጋዜጦችን ማሳተም፣
  6. በተጨማሪም ከላይ በተጠቀሰው ዓ.ም. ሌላ የማተሚያ መሣሪያ በመንግሥት ገንዘብ ተገዝቶ ለመርሐ ጥበብ ማተሚያ ቤት ተሰጥቶ ለመንግሥት መሥሪያ ቤቶች የሚያስፈልጉት ሰነዶች እንዲታተሙና በተጨማሪም አእምሮ ተብሎ የተሰየመውን ጋዜጣ ማሳተማቸው፣
  7. በአዲስ አበባና በሌሎቹም በዋና ዋና ከተሞች ኤሌክትሪክ ባለመኖሩ ሕዝቡ ይጠቀም የነበረው በጋዝና በጧፍ መብራት ብቻ ስለነበረ፤ በ 1909 ዓ.ም. ተጀምሮ የነበረው የኤልክትሪክ መብራት፤ በ 1915 ዓ.ም. ተስፋፍቶ፤ በቤተ መንግስት፣ በምኒስትሮች መሥሪያ ቤቶች፣ በትላልቅ አብያተ ክርስቲያናት፣ በየመኳንንቱ ቤት፣ በሐረር፣ በድሬዳዋና በደሴ በሚገኙ መሥሪያ ቤቶች እንዲስፋፋ መደረጉ፣
  8. ከ 1915 ዓ.ም. በፊት የነበረው አንድ አውቶሞቢል ብቻ ስለነበር፤ ከ 1915 ዓ.ም. በኋላ ግን በርካታ ተሽከርካሪዎች እና ብስክሌቶች እንዲገቡ መደረጉ፤
  9. በአዲስ አበባና በሌሎችም ከተሞች የነበረው አንድ የዳግማዊ ምኒልክ ትምህርት ቤት ብቻ ስለነበረ፤ ከ 1917 ዓ.ም. ጀምሮ ግን በርካታ የውጭ አገር ቋንቋ መማሪያ ትምህርት ቤቶች በየአውራጃው እንዲከፈቱና እንዲሁም ወደ ውጭ አገር ብዙ ልጆች እየተላኩ እንዲማሩና ተምረው ሲመለሱም በየምኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ተመድበው እንዲሠሩ መደረጉ፣
  10. በአዲስ አበባና በሌሎችም ከተሞች የነበረው አንድ የዳግማዊ ምኒልክ ሆስፒታል ብቻ ስለነበረ ከ 1915 ዓ.ም. ጀምሮ ግን በአዲስ አበባና በሌሎችም ዋና ዋና ከተሞች ብዙ ሆስፒታሎች መሠራታቸውና እንዲሁም በግል ገንዘባቸው ቤተ ሳይዳ ተብሎ የተሰየመው ሆስፒታል (በአሁኑ ወቅት የካቲት 12 ሆስፒታል ተብሎ የሚጠራው) ተቋቁሞና አንድ የስዊድን ተወላጅ ሐኪም ተቀጥሮ እንዲሠራ መደረጉ፣
  11. አዲስ አበባ ላይ በራሳቸው ስም የሚጠራ ተፈሪ መኮንን የተሰኘ ዘመናዊ ት/ቤት አሠርተው ሚያዝያ 17 ቀን 1917 ዓ.ም መመረቁ፣
  12. በቀድሞ ዘመን ውትድርና በልማድ ብቻ መሆኑ ቀርቶ የውትድርና ማሠልጠኛ ትምህርት ቤት ተቋቁሞ የውትድርና ትምህርት እንዲሰጥ መደረጉ፣
  13. ቀደም ሲል ጥቅም ላይ ይውል የነበረው ሰንደቅ ዓላማ፤ የመሐል መደቡ የአንበሳ አርማ ያለበት ሆኖ ባለሦስት ቀለማት፤ ማለትም አረንጓዴ፣ ቢጫ፤ ቀይ ሲሆን፤ ከ 1920 ዓ.ም. ጀምሮ ግን ይኸው ሰንደቅ ዓላማ ሳይለወጥ በቤተ መንግሥቱ ቅጥር ግቢ ለዘወትር እንዲውለበለብ መደረጉ፡፡
    በተጨማሪም ለበዓል ቀናት ብቻ ሦስቱ ቀለማት ሳይለወጡ የአንበሳው ዓርማና የወርቅ መርገፍ ያለበት እንዲሆን መደረጉ፡፡
    ለጦር ሠራዊት፣ ለፖሊስ ሠራዊትና ለመርከበኞች ደግሞ ሦስቱ ቀለማት ሳይለወጡ በጌጡና በቅጹ እየተለየ ሰንደቅ ዓላማ እንዲሠራ መደረጉ፡፡
  14. ከ 1920 ዓ.ም. ጀምሮ የኢትዮጵያ ብሔራዊ መዝሙር ተዘጋጅቶ፤ የውጭ አገር እንግዶች ሲመጡ በክብር አቀባበልና በግብዣ ጊዜ እንዲዘመር መደረጉ፣
  15. ከ 1900 ዓ.ም. ጀምሮ ከናሽናል ባንክ ኦፍ ኢጅብት እና በአዲስ አበባ ባንክ ኦፍ አቢሲኒያ በስተቀር ሌላ ባንክ ስላልነበረ፤ በ 1920 ዓ.ም. በራሳቸው፣ በመኳንንቱና በሕዝቡም አማካኝነት አክሲዮን በመግዛት፤ የባንክ ኦፍ አቢሲኒያን ኪሳራ ከፍሎ ባንኩን የባለአክሲዮኖች ሐብት በማድረግ ትልቅ ጥቅም እንዲገኝበት መደረጉ፤
  16. ከ 1920 ዓ.ም. ጀምሮ አይሮፕላኖች እየተገዙ እንዲመጡ መደረጉ፣
  17. ከ 1921 ዓ.ም. ጀምሮ በጐረቤቶቻችን ላሉ መንግሥታት የዲፕሎማቲክ ሚሲዮንና ቆንስላ እንዲቋቋሙ መደረጉ፣
  18. ሐምሌ 29 ቀን 1923 ዓ.ም. የመጀመሪያው ሕገ መንግሥት መጻፉ፣
  19. ስልክና የፖስታ አገልግሎት በየአውራጃው እንዲገባ መደረጉ፣
  20. በየሥፍራው የነበሩትን የባላባት ገዥወችን በማስቀረት መንግሥት በሚሾማቸው መተካቱ፣
  21. ኢትዮጵያ በዓለም መንግሥታት እንድትታወቅ በማሰብ፤ ግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ጥቅምት 23 ቀን 1923 ዓ.ም. የንጉሠ ነገሥት ዘውድ ሲጭኑ፤ የ 12 መንግሥታት እንደራሴዎችና መሳፍንት ወደ አዲስ አበባ መጥተው የዘውድ በዓሉን ማክበራቸው፣



Mussolini visiting his troops
ፋሽስት ሙሶሎኒ ወደ ኢትዮጵያ
የሚያዘምተውን ጦር ሲጎበኝ
Photo credit to: greengoldgardens.com
የኢጣሊያ ወራሪ ጦር በ1888 ዓ.ም. አድዋ ላይ ሽንፈቱን ከተከናነበ ከ40 ዓመት በኋላ በቁጭት ተመልሸ እመጣለሁ እነዳለው ኢትዮጵያን በቅኝ ግዛት ለመያዝ እንደገና ተነሳሳ፡፡
ኢጣሊያ ኢትዮጵያን ለማያዝ የነበራት ዕቅድ እንዲሰምርላት በዲፕሎማሲው መስክ ጥረት በማድረግ፤ በኢትዮጵያ የኢጣሊያ ለጋሲዮን (ዲፕሎማቲክ ሚሽን) ለማቋቋም ሌላ አገር የቀደማት የለም፡፡
ኢጣሊያ ከሌሎች አጐራባች ከሆኑ ከእንግሊዝና ከፈረንሳይ ቅኝ ገዥዎች ጋር በተፈራረመችው ውል መሠረት ከኤርትራና ከኢጣሊያ ሶማሌላንድ አዋሳኝ ያሉት የኢትዮጵያ ግዛቶች እንዳሉ ወደ ኢጣሊያ ግዛት እንዲካለሉ ወሰኑ፡፡
በሙሶሎኒ የሚመሩት ፋሽስቶች በ1915 ዓ.ም. በኢጣሊያ ሥልጣን ሲይዙ፤ የኢጣሊያ የቅኝ ግዛት ፍላጐት ይበልጥ እየበረታ መጣ፡፡
የጥንቱ የሮማን መንግሥት የነበረውን ኃይልና ዝና እንደገና ለማደስ ታጥቆ የተነሳው የፋሽስት ቡድን የመጀመሪያ ዓላማው የሆነው፤
  1. የዐድዋን ሀፍረት ለመሻርና፤
  2. እጅግ ለምና በከርሰ ምድር ሀብት የበለፀገችውን የኢትዮጵያን ሐብት ለመቆጣጠር ነበር፡፡
ፋሽቱ ሙሶሎኒ ግን የወረራ ዓላመውን ሸፍኖ የሚፈልገውን በዲፕሎማሲያዊ መንገድ ለማግኘት ጥረት ማድረግ ጀመረ፡፡
ሌላው ቀርቶ ራስ ተፈሪ መኮንን በ1916 ዓ.ም. አውሮፓን ለጉብኘት በሄዱበት ወቅት ኢጣሊያ አገር ሲገቡ፤ ቪቫ ኢትዮጵያ! ቪቫ ተፈሪ! እያሉ ሞቅ ያለ አቀባበል ማድረጋቸው ኢትዮጵያን የማዘናጊያ ስልት እንደነበረ መገንዘቡ አያዳግትም፡፡
በኢጣሊያና በኢትዮጵያ መካከል የነበረው የመቀራረብና የመቻቻል ስሜት ከፍተኛ ደረጃ ላይ ደረሰ የሚያሰኘው፤ ልክ እንደውጫሌው ውል ሁሉ፤ “የሰላምና የወዳጅነት ውል” በሚል መጠሪያ ሐምሌ 8 ቀን 1920 ዓ.ም. ለ20 ዓመት የሚቆይ ውል ሲፈራረሙ ነበር፡፡
ይሁን እንጅ የተገለፀው የሰላምና የወዳጅነት ውሉ በኢጣሊያ በኩል የማስመሰል እንጅ ከልብ ሰላልነበረ፤ የኤርትራው የኢጣሊያ አገረ ገዥ፤ በትግሬ፣ በቤገምድር፣ በጐጃምና በወሎ የማዕከላዊውን መንግሥት ሥልጣን ይቦረቡር ነበር፡፡
ኢጣሊያ፤ በጦር ኃይላቸው ብቻ ኢትዮጵያን ድል ለማድረግ እንደማይችሉ በመገንዘባቸው፤ በየምክንያቱ በላኳቸው የዲፕሎማቲክ ሠራተኞቻቸውና በየሀገሩ ገብተው በነበሩት የሐይማኖት ሚሲዮኖች አማካይነት አስመሳይ የሆነ የውሸት ስብከትና ድለላ ረዘም ላለ ጊዜ በማስፋፋታቸው፤ እርስ በርሳችን ፍቅር አጥተን እንዳንስማማ ምክንያት በመሆኑ፤ አንድነታችንን አሳጥተው ኃይላችንን አዳክመውት ነበር፡፡

በተለያዬ ወቀት፤ በዐድዋ፣ በጐንደር፣ በደብረ ማርቆስና በደሴ ተከፍተው የነበሩት የኢጣሊያ ቆንስላወችም፤ የማዕከላዊውን መንግሥት ሥልጣን በመቦርቦር የሸፍጥ ትግባር ላይ በመሰማራት፤ የኢትዮጵያን ፖለቲካዊና ወታደራዊ መረጃዎችን ሰብስቦ ለአገራቸው ለኢጣሊያ በማስተላለፍ ሥራ ላይ በመሰማራት ያቀዱትን ወረራ ለማሳካት ያለማቋረጥ ሠርተዋል፡፡
የአሁኑ የኢጣሊያ ወረራ ከቅድመ ዐድዋ ጋር የሚያመሳስለው ሌላው መንገድ፤ እንግሊዝ ለኢጣሊያ ቅኝ ግዛት የመስፋፋት ዓላማ ሙሉ ድጋፈፍ መስጠቷ ነው፡፡
ግብፅን በቅኝ ግዛትነት የያዘችው እንግሊዝ፤ ሰዊስ ካናልን የኢጣሊያ ጦር መሣሪያና ሎጅስቲክስ መተላለፊያ እንዲሆን ክፍት አደረገቸው፡፡ ስዊስ ካናል ባይከፈት ኖሮ ኢጣሊያ በቅኝ ግዛቶቿ ለሚገኙት ወታደሮቻቸው መሣሪያና ሎጅስቲክስ ማቅረብ አይችሉም ነበር፡፡
የዓለም መንግሥታት ማህበር (League of Nations) በኢጣሊያ ላይ ማዕቀብ ለመጣል ቢሞክርም አባል አገራት ስላልተስማሙበት ሳይሳካ ቀርተዋል፡፡
ሌላው ቀርቶ የማህበሩ አባል አገራት፤ የማህበሩን ውሳኔ ጣሊያኖች እንዳይቀበሉት ይገፋፉ እንደነበረ ተዘግቧል፡፡
በ1918 ዓ.ም. እንግሊዝና ኢጣሊያ በኢትዮጵያ ላይ ያደረጉት ሰምምነት፤ በ1883 ዓ.ም. እና በ1886 ዓ.ም. ሁለቱም አገራት ካደረጓቸው የፕሮቶኮል ስምምነቶች ጋር ይመሳሰላል፡፡
እንግሊዝ ምእራብ ኢትዮጵያን፤ የኢጣሊያ ብቸኛ የኢኮኖሚ ክልል ነው ብላ አውቅና ስትሰጥ፤ ኢጣሊያም በበኩላ፤ እንግሊዝ (ግብፅን በቅኝ ግዛትነት በተቆጣጠረችበት ወቅት መሆኑ ነው)፤ ጣና ሐይቅ ላይ ግድብ ሠርታ የዓባይን ውሀ ለመቆጣጠር ለነበራት የብዙ ዓመታት ጥረት ዲፕሎማሲያዊ ድጋፍ ለመስጠት ቃል ገባች፡፡

ይህን ሁሉ ስምምነት ሁለቱ አገሮች የሚፈጽሙት፤ ኢትዮጵያ የዓለም መንግሥታት ማህበር አባል መሆኗ እየታወቀና “ሁሉም የመንግሥታቱ ማህበር አባላት እኩል መብት አላቸው” የሚለውን የማህበሩን ቻርተር አውቀው እንዳላወቁ በእብሪት መነሳሳታቸው እጅግ የሚያስገርም ነበር፡፡
ይህም የሁለቱ አገሮች ድርጊት የሚያመለክተው፤ የዓለም መንግሥታት ማህበሩ የታቀደውን የኢጣሊያ ወረራ ማስቆም እንደማይችል ጠቋሚ ነበር፡፡
ቆይታም ኢጣሊያ፤ ቀደም ብላ ለአቀደችው ጦርነት እንደመነሻ የሆነውንና በኢትዮጵያ ላይ ወረራ ለመጀመር የሚያስችላትን የወልወል ግጭትን አስነሳች፡፡

የኢጣሊያ ጦር የታጠቀው መሣሪያ ዓይነትና ብዛት፤

  1. የተዋጊ እግረኛ ሠራዊት ብዛት 500 ሺህ
  2. 795 ታንኮች
  3. 2 ሺህ መድፎች
  4. 600 ቦምብ ጣይ አይሮፕላኖች

የኢትዮጵያ ጦር የታጠቀው መሣሪያ ዓይነትና ብዛት

  1. 300 ሺህ እግረኛ ሠራዊት
  2. 4 ታንኮች
  3. 200 መድፎች
  4. 7 መትረየስ የጫኑ መኪኖች


ምንጭ፤
  1. "የኢትዮጵያ ታሪክ - ከአፄ ልብነ ድንግል እስከ ዳግማዊ አፄ ቴዎድሮስ"  ደራሲ፡- ተክለ ጻድቅ መኩሪያ 1961 ዓ.ም.
  2. "የኢትዮጵያ ታሪክ ከ 1847 እሰከ 1983"  ደራሲ፡- ፕሮፌሰር ባሕሩ ዘውዴ
  3. "የታሪክ ማስታወሻ"  ደራሲ፡- ደጃዝማች ከበደ ተሰማ 1962 ዓ.ም.
  4. "ሕይወቴና የኢትዮጵያ እርምጃ - ፩ኛ መጽሐፍ"  ደራሲ፡- ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ንጉሠ ነገሥት 1928 ዓ.ም.
  5. የትረካው አጃቢ ሙዚቃ፣ ዋሽንት - በአንሙት ክንዴ   ዩቲውብ
  6. Courtesy of: Rare WW2 Footage - German Infantry - No Music, Pure Sound  ዩቲውብ