Content-Language: am ደጃዝማች በላይ ዘለቀ ገጽ አንድ
header image


(ድረ ገጽ 1)



ደጃዝማች በላይ ዘለቀ (አባኮስትር)




በአራት ክፍል ተዘጋጅቶ የቀረበውን
የደጃዝማች በላይ ዘለቀን የአርበኝነት ዘመን ትረካ ያዳምጡ

በእያንዳንዱ አርዕስት ሥር የሚገኘውን የድምጽ
ማጫወቻ በመጠቀም ትረካውን ማዳመጥ ይችላሉ

ክፍል አንድ
ትውልድ፣ እድገት፣ የባሻ ዘለቀ መሞት፣
የበላይ ዘለቀ የወጣትነት ትውስታና
የበቀል ስሜት
ክፍል ሁለት
የበላይ ዘለቀ የአርበኝነት ዘመን አጀማመር፣
ቀጣይ ተጋድሎና አባኮስትር ለኢጣሊያ
እንዲገባ የተደረገው ሙከራ
ክፍል ሶስት
በንጉሠ ነገሥቱ ፊት የታየው የበላይ
ዘለቀ ሰልፍና የበላይ ዘለቀ
ንጉሠ ነገሥቱ ፊት መቅረብ
የመጨረሻ ክፍል
እጅ መስጠት፣ በአዲስ አበባ የደረሰበት መጉላላት፣
እስር፣ የሞት ፍርድና የበላይ ዘለቀ
የአመራርና የአስተዳደር ዘይቤ


Dejazmach Belay Zeleke
አባኮስትር በላይ ዘለቀ
በላይ ዘለቀ ከአባቱ ከባሻ ዘለቀ ላቀው እና ከእናቱ ከእመት ጣይቱ ሐሰኔ በወሎ ክፍለ ሐገር በቦረና አውራጃ በጫቀታ ወረዳ በጅሩ ቀበሌ ጎጣ ከተባለው ሠፈር በ1903 ዓ.ም. እንደተወለደ ይገመታል፡፡
የበላይ ዘለቀ አባት ባሻ ዘለቀ የልጅ እያሱ ታማኝ አገልጋይ እና አንጋች ስለነበሩ የባሻነትም ማዕረግ የተሰጣቸው በዚሁ ሳቢያ ነበር፡፡
በእርሳቸው ስርም ብዙ ሠራዊት እንደነበራቸው ይነገራል።
ልጅ እያሱ ከሥልጣን ሲወርዱ፤ ባሻ ዘለቀ ታላቁን ወንድ ልጃቸውን በላይ ዘለቀንና የእርሱ በእድሜ ታናሽ የሆነውን እጅጉ ዘለቀን ይዘው በወሎ ክፍለ ሐገር በቦረና ሳይንት አውራጃ ወደሚገኘው ወደ ሚስታቸው የትውልድ ሥፍራ ወደሆነው ወደ ጫቀታ ሄደው ለጥቂት ዓመታት እዚያው ተቀመጡ፡፡
ከዚያም ሳሉ በእጃቸው የሰው ሕይዎት ስለጠፋ ልጆቻቸውን ይዘው በጠፍ ጨረቃ በሌሊት ወደ ተወለዱበት ሥፍራ ወደ ጎጃም ተሻግረው በብቸና አውራጃ ለምጨን ቀበሌ ገብተው መኖር ጀመሩ፡፡
ለምጨን፤ በብቸና አውራጃ፣ በእነማይ ወረዳ፣ በዓባይ ሸለቆ ውስጥ የሚገኝ፤ ወርካዬ፣ አዲስ አምባ፣ የዱሃ እና ጎይ የተባሉ መንደሮች የሚገኙበት፤ ከላይ ዳገት፣ ከታች ገደል ሆኖ፣ “ቀይት” እና “ጠጋ” ተብለው የሚጠሩ ወንዞች የሚያዋስኑት ቆላማ አካባቢ ነው፡፡
እነማይ ወረዳን፤ በሰሜን እናርጅ እናውጋ፣ በደቡብ ደጀን፣ በምዕራብ ደባይ ጥላትግን፣ በምስራቅ ሸበል በረንታ ያዋስኑታል።

እንደ ቀትር እሳት የሚፋጀው ፊቱ፣
አባ ኮስትር በላይ ለምጨን ላይ ነው ቤቱ፡፡

ባሻ ዘለቀም ለምጨን ሲኖሩ ሳለ ሰው ገድለሃል ተብለው በ1916 ዓ.ም. ቀንጦ ማሪያም በተባለው ሥፍራ ላይ በራስ ኃይሉ ተክለ ሐይማኖት ሌባ አዳኝ የሚል ሹመት በተሰጣቸው በፊታውራሪ እምቢያለ አማካኝነት በድንገት ተከበው ባሻ ዘለቀን እጃቸውን እንዲሰጡ ጠየቋቸው፡፡
ባሻ ዘለቀም እጀን አልሰጥም በማለታቸው ተኩስ ሲከፈት፤ ከባሻ ዘለቀ ጋር አብረዋቸው ከነበሩት ከወንድሞቻቸው ከታደሰ ላቀው እና ከአበጀ ላቀው፣ እንዲሁም ከዘመዳቸው ከአለሙ መርሻ እና ከጓደኛቸው ከመንግሥቱ ፈንታ ጋር በመሆን፤ በአልሞት ባይ ተጋዳይነት ሲታኮሱ ብዙ ሰው ከገደሉ በኋላ የበላይ ዘለቀ አባት ባሻ ዘለቀ በጥይት ተመተው ሕይወታቸው አለፈ፡፡
ለመቀጣጫ እንዲሆን በማለት የባሻን እጅ ለመያዝ የመጡት ሰዎች፤ የባሻ ዘለቀን እና የዘመዳቸውን የአቶ ዓለሙ መርሻን ሬሳ በቤተሰቦቻቸውና በጎረቤቶቻቸው ፊት እቤታቸው በራፍ ላይ ሰቀሏቸው፡፡
ይህ አሰቃቂ ሁኔታ ሲፈጠር የአባቱን አሟሟት እና የሬሳቸውንም መሰቀል በአይኑ የተመለከተው የ14 ዓመት ልጅ የነበረው በላይ ዘለቀ በብስጭት እርር ኩምትር አለ፡፡
ከዚህ በኋላ በበላይ ዘለቀ አዕምሮ የሚመላለሰው እና የሚያልመው መበቀልንና የአባቱ ደም መላሽ መሆንን ብቻ ሆነ፡፡
ሐሳቡ ሁሉ ከከብት ጥበቃና ከእርሻ ይልቅ በዓባይ በረሃ ጥገኝነትን መረጠ፡፡
የዘወትር እንጉርጉሮውም፤
ጥራኝ ዱሩ፣ኧረ ጥራኝ ዱሩ፣
ላንተም ይሻልሃል ብቻን ከማደሩ፤
የሚል ሆነ፡፡
ስለዚህም አባቱ ሲወድቁ ጠመንጃቸውን አንስተው ያመለጡትን አጎቱን አቶ ታደሰ ላቀውን የአባቱን ጠመንጃ እንዲሰጡት ጠየቃቸው፡፡
አጎቱም ልጅነቱን በመመልከት መሣሪያውን ሊሰጡት አልፈቀዱም፡፡
በላይ ዘለቀ የህፃንነት መጥፎ ትዝታው በአዕምሮው እየተመላለሰ ዓላማው ሁሉ በቀል የተሞላበት፣ የሕይዎት ጎዳናውም መንከራተት የበዛበት ሆነ፡፡
በበላይ ዘለቀ አዕምሮ የተጠነሰሰው የበቀል ስሜት በአንድ ስፍራ ሊያስቀምጠው ስላልቻለ፤ በዘመኑ በቤተ ክርስቲያን ይሰጥ የነበረውን መሠረታዊ የፊደል ገበታ እንኳን በአይኑ ለማየት ዕድል ባለማግኘቱ መማር ሳይችል ቀረ፡፡
በዚህም ምክንያት ታናሽ ወንድሙን እጅጉ ዘለቀን ይዞ ከበረሃ ወደ በረሃ መንከራተት እጣ ፋንታው ሆነ፡፡
የመንከራተቱም ምክንያት፤
አንደኛ፡- በአባቱ የትውልድ ሥፍራ በብቸና የአባቱ ገዳዮች ይበቀለናል ብለው ስለሚፈሩ መከታተላቸውን ባለማቆማቸው ሲሆን፤
ሁለተኛው፡- ደግሞ በበላይ ዘለቀ የትውልድ ሥፍራ በቦረና የአባቱ ደመኞች (ባላንጣዎች) የበቀል ተግባር ሊፈጽሙበት በመፈለጋቸው በአንድ ሥፍራ ተወስኖ ለመቆየት አላስቻለውም፡፡
በዚህም ምክንያት ቦረና አለ ሲባል፤ ብቸና ይገኛል፡፡ ብቸና አለ ሲባል፤ ቦረና እየተሻገረ ዱካው የማይገኝ ሰው ሆነ፡፡
በስተመጨረሻም በብዙ ውትወታ የአባቱን ጠመንጃ ከአጎቱ ተቀብሎ ታናሽ ወንድሙን እጅጉ ዘለቀን ይዞ የአባቱን ገዳይ ፊታውራሪ እምቢያለን ለመበቀል ሰውየው ወዳሉበት ሥፍራ ሄደ፡፡
ሆኖም ፊታውራሪ እምቢያለ በስፍራው ስላልነበሩ በምትኩ ፊታውራሪ እምቢያለን እየመራ አምጥቶ አባቱን ያስገደለውን ግራዝማች ደርሰህን በመግደል ደሙን ከመለሰ በኋላ ከታናሽ ወንድሙ ጋር በመሆን ጫካ በመግባት ሽፍትነቱን ተያያዘው፡፡
በአንድ ወቅት የበላይ ዘለቀን የእናቱን ላም ነብር እንደበላባቸው ሲሰማ፤ በላይ ዘለቀ ነብሩን ለመግደል ከታናሽ ወንድሙ ጋር ወደ ጫካው በመሄድ ነብሩን በጠመንጃ ተኩሶ ገደለው፡፡
ላሟን የበላው ነብር እንደተገደለ እናቱ ሰምተው ማን እንደገደለው ሲጠይቁ በላይ እንደሆነ ሲሰሙ፤ እናቱም “አባኮስትር ብየሀለሁ” ብለው ስም እንዳወጡለት የበላይ ዘለቀ የቅርብ ወገኖች ያስረዳሉ፡፡
ከዚያ ጊዜ ጀምሮ በአብዛኛው አባኮስትር ተብሎ መጠራት ጀመረ፡፡
በላይ ዘለቀ ፋሽስት ኢጣሊያ ኢትዮጵያን በወረረበት ወቅት በጎጃም ጠቅላይ ግዛት የአርበኝነት ተግባር ከጀመሩት ከመጀመሪያዎቹ እረድፍ ከሚጠቀሱት ውስጥ በ 25 ዓመት ለጋ ዕድሜው ከወራሪው ፋሽስት ኢጣሊያ ጋር አርበኛ ሆኖ ለመፋለም የቆረጠ ወጣት ነው፡፡
ወራሪው ፋሽስት ኢጣሊያ ወደ ኢትዮጵያ ገብቶ እንደነበረ በላይ ዘለቀ ያውቅ ነበርና ከእለታት አንድ ቀን በብቸና የገበያ ቀን ሳይታሰብ አራት እርሱን መሰል ተከታዮችን አስከትሎ ከገበያው አጠገብ በሚገኝ ጉብታ ሥፍራ ላይ ቆሞ ገበያተኛውን ሲመለከት ሳለ፤ “አስጨናቂ! ሽፍታ! ሽፍታ! በላይ!” የሚል ድምፅ ከገባያተኛው ሲሰማ አስጨናቂ ኮስተር ብሎ፤
“የአገሬ ሰው ስማኝ!!”
“ጣሊያን የሚሉት ነጭ አገራችንን ሊወር፣ ሚስትህን፣ ልጅህን ሊደፍር፤ ሐብትህን ሊወርስ መቷል፡፡
ይኸው ብቸና ገብቶ መሣሪያ አስረክቡ ብሏል፡፡
መሣሪያውን ለጣሊያን የሚያስረክብ ሰው ካላ ቤቱን አቃጥልበታለሁ፡፡”
በማለት ንግግር አድርጎ ሕዝቡ መሣሪያውን ለጠላት እንዳያስረክብ አስጠነቀቀ፡፡
እነአስጨናቂም (በላይ ዘለቀ) የሄዱበት ሳይታወቅ ወዲያውኑ ከሥፍራው ተሰወሩ፡፡
ቀስ በቀስም የኢጣሊያ ጦር ከደብረ ማርቆስ ተነስቶ ወደየአውራጃዎች ለማምራት መንቀሳቀስ መጀመሩን አስጨናቂ እንደሰማ፤ ልክ እንደርሱ በተመሳሳይ ምክንያት ሸፍተው የነበሩትን ባለጦር መሣሪያዎችንና ጀሌዎችን ለምክር ሰብስቦ፤
“ጎበዝ! አገራችን በጠላት ስትደፈር ዝም ብለን ብንመለከት፤ ለአገር ነፃነት፣ ለመንግሥት ክብር እና ለሐይማኖት ጽናት ሲሉ በየጦር ሜዳው ደማቸውን ያፈሰሱትና አጥንታቻውን የከሰከሱት የአባቶቻችን አጥንት ስለሚወቅሰን የተቻለንን ሁሉ ማድረግ አለብን፡፡”
በማለት ወኔ ተናንቆት ሲናገር ተመሳሳይ ሀሳብና ዓላማ ያላቸው ቁጥራቸው ከ 30 እስከ 50 የሚደርሱ የአንድ አያት ልጆች ከተሰባሰቡ በኋላ በአስጨናቂ መሪነት አገር ወራሪውን ጠላት ለመውጋት በአንድነት ተስማሙ፡፡
ከዚያ በኋላ በእርሱ የጎበዝ አለቃነት በምሥራቅ ጎጃም በ25 ዓመት ለጋ ዕድሜው የአርበኝነት ሥራውን ጀመረ፡፡
ግንቦት 12 ቀን 1928 ዓ.ም. በግምት ከቀኑ 8 ሰዓት ላይ 6 የጠላት ኮንቮዮች ከደብረ ማርቆስ ተነስተው የሚሄድበትን አቅጫ የሚያሳዩ በገንዘብ በተደለሉ ባንዳዎች እየተመሩ ወደ ብቸና አቅጣጫ በመጓዝ ላይ ነበሩ፡፡ እነ በላይ ዘለቀም ጥቅጥቅ ያለ ጫካ በሚገኝበት ረባዳ ሥፍራ ላይ አድፍጠው ስፍራ ስፍራቸውን ይዘው ሲጠባባቁ ሳሉ፤ አራቱ የጠላት መኪኖች ተከታትለው አልፈው አምስተኛው መኪና እንደደረሰ በላይ ዘለቀ በሰጠው የተኩስ ትእዛዝ በኮንቮዮቹ ላይ በአንድነት የጥይት እሩምታ አዘነቡባቸው፡፡
በመጀመሪያው መኪና ላይ የነበሩት 4 የኢጣሊያ ወታደሮችና ሁለት ባንዳዎች ሲሞቱ ከወገን በኩል አንድ ሰው ሲሞት አንዱ ቁስለኛ ሆኗል፡፡
ከዚህ ፈጣን ከሆነ የደፈጣ ውጊያ በኋላ እነበላይ ዘለቀ የማረኩትን ቦምብና መሣሪያ ይዘው በጫካው ውስጥ ከደበቁት በኋላ ከስፍራው በፍጥነት ተሰወሩ፡፡
በብልህነቱ፣ በአዳማጭነቱና በአስተያየት ጥልቀቱ በላይ ዘለቀ የሚተማመንበት የልጅነት ጓደኛው ቢሰውር፤ ከከተማ ወደ ገጠር፣ ከገጠር ወደ ከተማ በመመላለስ ጠቃሚ መረጃ ያቀርብለት ስለነበር፤ አባኮስትር በላይ ድል በድል ላይ ይቀዳጅ ስለነበር በልጅነት ጓደኛው ይመካበት ነበር፡፡
አባኮስትር በላይ ታማኝ የሆኑ የውስጥ አርበኞችም ነበሩት፡፡
ባንዳ መስለው የጠላትን መሣሪያ ዓይነትና ብዛት፣ የወታደሩን ቁጥርና የጦሩን መሪ፣ የሚዘምቱበትን ቀንና ቦታ የሚሰልሉለት ታማኝ የውስጥ አርበኞች ነበሩት፡፡
በአንድ ወቅት ታናሽ ወንዱሙን እጅጉ ዘለቀን ደጃዝማች ብሎ ሲሾም፣ እጅጉ ዘለቀም በበኩሉ፤
“ጋሸ፣ ስሙን ሁሉ ጨረስከው፤ አንተ ማን ልትባል ነው?” ብሎ ሲጠይቅ፤ በላይም፤ “ለእኔ ሌላ ስም ምን ያስፈልጋል፤ እናቴ በላይ ብላኝ የለም እንዴ?”
በማለት እንደመለሰ ተነግሯል፡፡
በአካባበቢው የነበረው ሕዝብም በላይን፤ ልዑል በላይ የሚል የማዕረግ ስም አውጥቶለት እንደነበር ይነገራል፡፡
አባኮስትር በለምጨን በረሃ መሽጎ ለኢጣሊያ መንግሥት አልንበረከክም በማለቱ፣ ሕዝቡም ለኢጣሊያ ባለሥልጣኖች እንዳይገዛ በማድረጉና ጠላትን መግቢያ መውጫ በማሳጣት ፋታ ስለነሳው “አፄ በጉልበቱ” የሚል የሙገሣም ስም ሕዝቡ አውጥቶለት ነበር፡፡
የፋሽስትን ጦር በየስፍራው ወጥሮ አላንቀሳቅስ ያለውን የጀግናውን የበላይ ዘለቀን እጅ ይዞ ለመቅረብ እና ሹመት ለማግኘት በብቸና ከተማ የተሰማሩት የጠላት ወታደሮችና ባንዶች መራወጥ ይዘዋል፡፡
የኢጣሊያ ጦርም ተዋጊ ጦሩንና ፈረሰኛውን እያግተለተለ በላይ ዘለቀ ይገኘበታል ወደተባለው ለምጨን ቀበሌ አመራ፡፡
እነ አባኮስትር በላይ የመሸጉበት ሥፍራ ለምጨን በሚባለው ቀበሌ በዓባይ ሸለቆ ውስጥ የሚገኝ በረሀ ሲሆን ጠላት በቀላሉ ሊደርስበት የማይችል፤ ነገር ግን በረሃ ያደገ ጀግና ብቻ ሊኖርበት የሚችል አካባቢ ነው፡፡
የኢጣሊያ ጦር እነ አባኮስትር በላይ የመሸጉበት ወርካየ ወደተባለው ምሽግ ደረሰ፡፡
የመሸጉት የበላይ ዘለቀ አርበኞችም በአካባቢው ለመኖራቸው ምንም አይነት ምልክት ሳያሳዩ መሣሪያቸውን ወድረውና አድፍጠው ጠላት ወደ ዒላማቸው እስኪገባ ድረስ ይጠባበቁ ነበር፡፡
የኢጣሊያ ወታደሮችም አርበኞች በአካባቢው ስለመኖራቸው ምንም ምልክት ባለማግኘታቸው ተዝናንተው ይጓዙ ነበር፡፡
ከጠላት ጦር ግማሽ ያህሉ ወደ አርበኞች ዒላማ እንደገባ፤ እነበላይ ዘለቀ ከምሽጋቸው ሆነው በአንድነት የጥይት እሩምታ በጠላት ላይ አዘነቡበት፡፡
የጠላት ጦርም ያልጠበቀው ሁኔታ ስለተከሰተ ተደናግጦ የኋላውም ፈርጥጦ ተመለሰ፣ ከፊት የቀደመውም ጦር በበላይ ዘለቀ ጦር ተመቶ ድል ተደረገ፡፡
ወደ በረንታ የዘመተውም የጠላት ጦር በእጅጉ ዘለቀ ጦር ተመቶ ብትንትኑ ወጣ፡፡
አባ ኮስትርን ማርኮ ለማምጣት የተሰማራውም የኢጣሊያ ጦር ሳይሳካለት ቀረ፡፡
አባኮስትርም ጠላት እንደገና ተጠናክሮ ሊመጣ እንደሚችል ስለተረዳና የተዋጊ ወታደሮችም ቁጥር እየቀነሰ በመምጣቱ ወደ ሌላ አካባቢ ሄዶ ለመመሸግ ተገደደ፡፡
የጠላትም ኃይል ከብቸና ምድር ለቆ ወደ ደብረ ማርቆስ ተመለሰ፡፡

በአንድ ምሽት ወቀት፤ አብሮ አደጉ ተመስገን ፋንታና ታናሽ ወንድሙ እጅጉ ዘለቀ አባኮስትር ወደሚገኝበት ምሽግ ገቡ፡፡
ተመስገን ፋንታና ታናሽ ወንድሙ እጅጉ ዘለቀ ትካዜ ገብቷቸው አቀርቅረዋል፡፡
አባኮስትር ግን ድልን ተቀዳጅተው ሳለ ለምን እንደተከዙ አልገባውም፡፡
አባ ኮስትርም፤ ልጄና ባለቤቴ ሸክሚቱ ዓለማየሁስ የት ሄዱ? ብሎ ጠየቀ፡፡
የእጅጉ ዘለቀ እንባ ኩልል ብሎ ሲወርድ ያየው አባኮስትር ደንገጥ ብሎ “ምነው ሞቱ እንዴ?” ብሎ እጅጉን ሲጠይቅ፤
“የሸክሚቱን እናትና ልጅህን ሻሸወርቅ በላይን ጠላት ማርኮ እንደወሰዳቸው እንደሰማሁ ለማስለቀቅ ብዙ ለፍቼ ነበር፡፡ ግን ሳይሳካልኝ ቀረ፡፡ ባለቤትህን ሸክሚቱ ዓለማየሁን ግን ጠላት ያለችበት አካባቢ እንደደረሰ እንደ ወንድ ለብሳ ከእህቷ ከዘውዲቱ ዓለማየሁ ጋር ሆና ከጠላት ጋር ሲዋጉ በመትረየስ ጥይት ተመተው ሁለቱም ሞቱ፡፡”
የሚል መልስ ተነገረው፡፡
አባኮስትር ይህን መርዶ ሲሰማ አላለቀሰም፡፡ ግን ከባድ ሀዘን ተሰማው፡፡ ቀኝ እጁ የተቆረጠ ያህል ተሰማው፡፡
አባኮስትር ባለቤቱን፣ የባለቤቱን አህትና አጎቱን ብቻ ሳይሆን ያጣው፤ በርካታ ተከታዮችንም በሞት ተነጥቋል፡፡








ምንጭ፤
  1. "አባኮስትር - ታሪካዊ ልብወለድ"  ደራሲ፡- አበራ ጀምበሬ 1983 ዓ.ም.
  2. "የታሪክ ማስታዎሻ"  ደራሲ፡- ደጃዝማች ከበደ ተሰማ 1962 ዓ.ም.
  3. "የኢትዮጵያ ታሪክ ከ 1847 እሰከ 1983"  ደራሲ፡- ፕሮፌሰር ባሕሩ ዘውዴ
  4. የትረካው አጃቢ ሙዚቃ፣ ዋሽንት - በአንሙት ክንዴ   ዩቲውብ
  5. Courtesy of: Rare WW2 Footage - German Infantry - No Music, Pure Sound  ዩቲውብ