Content-Language: am ራስ ደስታ ዳምጠው
header image


ክቡር ራስ ደስታ ዳምጠው




የክቡር ራስ ደስታ ዳምጠውን
የአርበኝነትና የሕይወት ታሪክ ያዳምጡ













1. ትውልድና ዕድገት

Ras Mulugeta Yigezu
ራስ ደስታ ዳምጠው
ልጅ ደስታ ዳምጠው በሸዋ ጠቅላይ ግዛት በጉራጌ አውራጃ መስቃ በተባለው ቀበሌ በ1884 ዓ.ም. ተወለዱ፡፡
አባታቸው ፊታውራሪ ዳምጠው ከተማ በዐድዋ ጦርነት ዘምተው በጦርነቱ የተሰው የዓድዋ ጀግና ነበሩ፡፡
ልጅ ደስታ ዳምጠው አና ወንድማቸው ልጅ አበበ ዳምጠው በልጅነታቸው ዘመን ከዳግማዊ አፄ ምኒልክ እና ከእቴጌ ጣይቱ ጋር በቤተ መንግሥት ውስጥ እያገለገሉ አድገዋል፡፡
ዳግማዊ አፄ ምኒልክ ከሞቱ በኋላም ልጅ ደስታ ዳምጠው በእንጦጦ ቤተ መንግስት ከእቴጌ ጣይቱ ጋር ኖረዋል፡፡
ራስ ደስታ ዳምጠው በወጣትነታቸው ዘመን ልጅ ደስታ ዳምጠው እየተባሉ በቤተ መንግሥት ባለሟል ሆነው ከቆዩ በኋላ በ1916 ዓ.ም. የፊታውራሪነት ማዕረግ ተሰቷቸው የፈረሶች ሀላፊ ሆነው ተሸሙ፡፡

2. የጋብቻ ሁኔታ

የጀግናው የራስ ደስታ ዳምጠው ባለቤት
ልዕልት ተናኘ ወርቅ ኃይለ ሥላሴ
ልጅ ደስታ ዳምጠው በ1917 ዓ.ም. በ33 ዓመት እድሜያቸው የዚያን ጊዜውን ልዑል አልጋወራሽ ተፈሪ መኮንን ተብለው ይጠሩ የነበሩትንና በኋላ የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ የመጀመሪያ ልጅ የሆኑትን ልእልት ተናኘወርቅ ኃይለ ሥላሴን በተክሊል አግብተው ሁለት ወንዶችን ማለትም፤
  1. አምሀ ደስታንና
  2. እስክንድር ደስታን
    ሲወልዱ እንዲሁም አራት ሴት ልጆችን በቅደም ተከተል ማለትም፤
  1. አይዳ ደስታን፣
  2. ሂሩት ደስታን፣
  3. ሰብለ ደስታን እና
  4. ሶፊያ ደስታን
ወልደዋል፡፡

ልዕልት ተናኘ ወርቅ ኃይለ ሥላሴ ከክቡር ራስ ደስታ ዳምጠው ከወለዷቸው ልጆች በኋላ፤
- እመቤት ጽጌ ማሪያምን፤ ከአባቷ ከአቶ አበበ ረታ፣
- እመቤት ምንትዋብን፤ ከአባቷ ከራስ አንዳርጋቸው መሣይ ወልደወል፡፡

Princess Tenagne Work Haile Selassie
ልዕልት ተናኘወርቅ ኃይለ ሥላሴ
በእንግሊዝ አገር በ1930 ዓ.ም.

Photo link
ልጅ ደስታ ዳምጠው ቁመታቸው ረዘም ያለ መልከ መልካምና ብዙ መናገር የማይወዱ ጭምትና የተረጋጋ ስብእና የነበራቸው ሰው እንደነበሩ ይነገራል፡፡
ልጅ ደስታ ዳምጠው፤ በነጮች ላይ ምንም አይነት እምነት የማይጥሉ ስለነበሩ ወደ ኢትዮጵያ የሚመጡት የውጭ ሰዎች ቁጥራቸው እንዳይበዛ እንደሚፈልጉ በግልጽ ይናገሩ እንደበር ተጽፏል፡፡
በ1923 ዓ.ም. ልዑል ራስ ተፈሪ መኮንን ከነገሡ በኋላ ልጅ ደስታ ዳምጠው የራስነት ማዕረግ ከተሰጣቸው በኋላ ራስ ብሩ ወልደ ገብሬልን ተክተው የሲዳሞና የቦረና ገዥ ሆነው ተሹመዋል፡፡
በቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ የንግሥ ሥነ ሥርዓት ላይ ለመታደም ከተለያዩ ሀገራት ከመጡት የውጭ ሀገር እንግዶች መካከል ከአሜሪካ ከመጡት እንግዶች ጋር ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ አሜሪካ ተጉዘው ኒውዮርክ እንደደረሱ የክብር አቀባበል ከተደረገላቸው በኋላ በወቅቱ የአሜሪካ ፕሬዚደንት የነበሩት ሩዝቬልት የምሳ ግብዣ አድረገውላቸዋል፡፡

3. የአርበኝነት ዘመን ተጋድሎና መስዋዕትነት

በፋሽስት ኢጣሊያ ወረራ ወቅት የደቡብ ጦር ግንባር የሚመራው በሲዳሞ ገዥ በራስ ደስታ ዳምጠው አማካኝነት ነበር፡፡
የደቡብ ጦር ግንባር ከሰሜኑ ጦር ግንባር ጋር ሲነጻጸር፤ በጦር መሣሪያ አቅርቦትም ሆነ በጦር አመራር ደረጃ የደቡቡ ጦር ግንባር የተሻለ ብቃት እንደነበረው ተነግሯል፡፡
የደቡብ ጦር ግንባር መሪው ራስ ደስታ ዳምጠው በጣሊያን ጦር ላይ እጅግ ድፍረት የተሞላበት ጥቃት አድርሰዋል፡፡
ግራዚያኒ ለደቡብ ጦር ግንባር ያሰለፋቸው ቦንብ ጣይ የጦር አውሮፕላኖች ብዛት 100 ይደርሳል፡፡
የግራዚያኒ ጦር በደቡብ ኢትዮጵያ አቅጣጫ ያለውን ሐረርጌን ለመያዝ በማቀድ፤ የኢጣሊያ ቅኝ ግዛት ከሆነችው ከሶማሊያ ከሦስት አቅጣጫ በመነሳት በኢትዮጵያ የኦጋዴን ድንበር በሆኑት ቦታዎች በቆራሄና በዶሎ ላይ ጦርነት ከፍቶ እየተዋጋ ወደፊት በመግፋት ደጋሀቡርን አልፎ ጉዞውን ጀመረ፡፡
ራስ ደስታ ዳምጠው፤ ጥሩ ትጥቅ የነበረውን፣ የሰለጠነ፣ ለአገሩና ለንጉሠ ነገሥቱ ታማኝና ተራማጅ አስተሳሰብ ያለውን ቁጥሩ 40 ሺህ የሚደርስ ጥሩ ተዋጊ ወታደሮቻቸውን እየመሩ ከነገሌ ቦረና በመነሳት፤ በደቡብ ኢትዮጵያ ግንባር የተሰለፈውን በግራዚያኒ በሚመራው የፋሽስት ጦር ላይ ውጊያ ከፍተው የኦጋዴን ድንበር የሀነችውን ዶሎን ከተቆጣጠሩ በኋላ ግራዚያኒን ለመውጋት ወደ ኢጣሊያ ሶማሌላንድ አመሩ፡፡
Ras Mulugeta Yigezu
ራስ ደስታ ዳምጠው ባንዳ እጃቸውን ይዞ
ለጠላት ጦር አሳልፎ ሲሰጣቸው

ራስ ደስታ ዳምጠው፤ ዋና ዋና አሽከሮቻቸው የሆኑትን ፊታውራሪ አደመ አንበሶንና ፊታወራሪ ታደመ ዘለቃን እፊት በማስቀደም፤ እርሳቸው የኋላ ደጀን ሆነው፤ ጦራቸው ግን ከፊት እየተዋጋ የኢጣሊያ ግዛት የሆነችው ሶማሊያ ሲደርሱ፤ በኢጣሊያ ሶማሌ ግዛት ውስጥ ታላቅ ሽብርና ፍርሀት ነገሠ፡፡
በዚህ ስጋት የገባው ግራዚያኒ፤ በሶማሌ ያለው መቶ ሺህ ጦር አይበቃኝምና ተጨማሪ ጦር ይላክልኝ እያለ ለአለቆቹ መልዕት ያስተላልፍ ነበር፡፡
ግራዚያኒ ይህም አልበቃው ብሎ፤ ሶማሌዎችን ሰብስቦ ስለኢትዮጵያውያን ጦር ያስነገረው አዋጅ፤
“…ኢትዮጵያውያን ሶማሌን ለመውረር ተሰልፈዋል፡፡
…አኛ ተዋግተን ከተሸነፈን፤ በመርከባችን ተሳፍረን ወደ አገራችን እንመለሳለን፡፡
…እናንተ ግን የምትሄዱበት ስለሌላችሁ፤ ኢትዮጵያውያን፤ የእናንተን ወንዶች እየሰለቡ፤ ሴቶችን ጡታቸውን እየቆረጡ ይበሉታል፡፡
...ምግባቸውም የሰው ሥጋ ነው፡፡
…ስለዚህ፤ ነጋዴ ነኝ፤ ገበሬ ነኝ ሳትሉ በአንድነት እንዋጋ፡፡”

የሚል መልዕክት የያዘ ነበር፡፡
በዚህም የግራዚያኒ የውሸት ስብከት የተታለሉ የሶማሌ ሰዎች፤ መሣሪያ እየተቀበሉ በሐይማኖት ከሚመሳሰሏቸው ከሊቢያ ከመጡ ወታደሮች ጋር ለውጊያ ተሰለፉ፡፡
Ras Desta Damtew
ጀግናው የደቡብ ጦር ግንባር መሪው
ራስ ደስታ ዳምጠው
እጃቸው በጠላት ወታደር ሲያዝ
ምንም እንኳን የጠላት ጦር ቆራሄ ላይ በራስ ደስታ ሠራዊት ላይ መዋከብ ፈጥሮ እንደነበር ቢታወቅም፤ ራስ ደስታ ግን ይህን ወከባ እንደአጋጣሚ በመጠቀም ሠራዊታቸውን ድንበር ላይ በምትገኘው የጠላት ይዞታ ሥር በነበረችው ዶሎ ላይ አዘመቱ፡፡
ሆኖም የጉዞው መርዘም የፈጠረው ድካም፣ የስንቅ እጥረትና የበሽታ መዛመት ጦርነቱን ውጤታማ ሊያደርገው አልቻለም፡፡
ነገር ግን ለጠላት ተሰልፈው እንዲዋጉ ከኤርትራ የመጡት ኤርትራውያን ጠላትን ከድተው ከራስ ደስታ ዳምጠው ጦር ጋር በመቀላቀላቸው የራስ ደስታ ጦር እንደገና አገግሞ ጠላትን እረፍት ማሳጣቱን ቀጠለ፡፡
ግራዚያኒም ቆራሄ የሚገኘውን የኢትዮጵያን ምሽግ በአይሮፕላን በሙስታርድ ጋስ ቦንብ በተከታታይ በመደብደብ የኢትዮጵያን ሠራዊት መጨፍጨፍ ጀመረ፡፡
በመጨረሻም የአዲስ አበባው የየካቲት 12ቱ እልቂት በሚካሄድበት ዕለት፤ በጣሊያኖች አይን እንደ አደገኛ ጠላት የሚታዩት ራስ ደስታ ዳምጠው፤ ከረዳታቸው ከደጃዝማች ገብረ ማሪያም ጋሪ ጋር በመሆን፤ ከጠላት ጋር ብርቱ ውጊያ ካደረጉ በኋላ፤ ደጃዝማች ገብረ ማሪያም በጦር ሜዳ ሲሞቱ፤ ራስ ደስታ ዳምጠው ደግሞ በጎጌቲ ጦርነት ሻላ ሀይቅ አጠገብ ቆስለው በነበረበት ሰዓት ሳይቀር ጠላትን ይዋጉ ነበር፡፡
በኋላም ሕመሙ ሲጠናባቸው ከጦር ሜዳ በማፈግፈግ በተወለዱበት መስቃ ቀበሌ ከተባለው ሥፍራ ደርሰው ህክምና ሳያገኙ በስቃይ ላይ ተኝተው ሳሉ በጠላት እጅ ተያዙ፡፡
Ras Desta Damtew Hospital
አዲስ አበባ የሚገኘው የራስ
ደስታ ዳምጠው መታሰቢያ ሆስፒታል
በኋላም ሳይውሉ ሳያድሩ በ 45 ዓመት እድሜያቸው በዕለተ ማክሰኞ የካቲት 16 ቀን 1929 ዓ.ም. በጠላት እጅ ተገደሉ፡፡
በ1933 ዓ.ም ኢትዮጵያ ከጣሊያን ወረራ ነፃ መውጣቷን ተከትሎ የራስ ደስታ ዳምጠው አጽም ጣሊያኖች ከቀበሩበት ስፍራ ወጥቶ አዲስ አበባ ወደሚገኘው ወደ መንበረ ፀባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ቤተ ክርስቲያን ተወስዶ ከንጉሠ ነገሥቱ ቤተሰቦች መካነ መቃብር ጋር ሥርዓተ ቀብሩ በክብር ተፈጽሟል፡፡

ለውድ አገራቸው ነፃነት መጠበቅ ለከፈሉት አኩሪ መስዋዕትነትና ለፈፀሙት የአርበኝነት ተግባራቸው ሲባል ለክቡር ራስ ደስታ ዳምጠው፤ አዲስ አበባ ውስጥ አንድ መታሰቢያ ሆስፒታል እና መንገድ እንዲሁም በይርጋለም አንድ 2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት በስማቸው ተሰይሞላቸዋል፡፡

4. የክቡር ራስ ደስታ ዳምጠው የቤተሰብ ሁኔታ

ደርግ መፈንቅለ መንግሥት ካካሄደ በኋላ የንጉሠ ነገሥቱን ቤተሰቦች፤ በተለይ ዘጠኝ ልዕልቶች ከያሉበት ተለቅመው ቀዝቃዛና እርጥበታማ የሲሚንቶ ወለል ባላት ጠባብና አስቸጋሪ እስር ቤት ውስጥ ከሁለት ፍራሽ ጋር ፀጉራቸውን ተላጭተው ከተወረወሩ በኋላ ለ14 ዓመታት ያህል ማንም ሰው እንዳይጎበኛቸው ተደርጎ በእስር ቤት ተሰቃይተዋል፡፡

የራስ ደሰታ ዳምጠው ልጆች ታሪክ ባጭሩ


1. ልዕልት አይዳ ደስታ

Princess Aida Desta
ልዕልት አይዳ ደስታ
Leul Ras Mengesha Seyoum
ልዑል ራስ መንገሻ ስዩም
የክቡር ራስ ደስታ ዳምጠው የመጀመሪ ልጅ የሆኑት ልዕልት አይዳ ደስታ መጋቢት 30 ቀን 1919 ዓ.ም. አዲስ አበባ ተወለዱ፡፡
ፋሽስት ኢጣሊያ ወረራ በፈፀመበት ወቅት ንጉሠ ነገሥቱ ወደ እንግሊዝ አገር ሲጓዙ ልዕልት አይዳም አብረው ተጉዘዋል፡፡
ልዕልት አይዳ እና ሶስት እህቶቿም በሰሜን ዌልስ በሚገኘው ክላሬንደን የሴቶች ልጆች ትምህርት ቤት ገብተው ተምረዋል።
በ1937 ዓ.ም. የማትሪክ ትምህርታቸውን ካጠናቀቁ በኋላ በካምብሪጅ ዩኒቨርሲቲ ገብተው ትምህርታቸውን ተከታትለዋል፡፡
በኋላም ወደ ኢትዮጵያ በመመለስ የትግራይ ልዑል ከሆኑት እና የአፄ ዮሐንስ የልጅ፤ ልጅ፤ ልጅ ከሆኑት ከልዑል ራስ መንገሻ ሥዩም ጋር በጥር ወር 1941 ዓ.ም. በአዲስ አበባ ጋብቻ በመፈፀም አምስት ወንድና አንዲት ሴት ልጅ አፍርተዋል።
ልዕልት አይዳ በአያታቸው በበግርማዊ ቀዳማዊ አፄ ኃይለ ሥላሴ ዘመነ መንግሥት በበጎ አድራጎት እና በባህላዊ ጉዳዮች ላይ ንቁ ተሳትፎ አድርገዋል።
በ1966 ዓ.ም. ደርግ ባለቤታቸውን ለማሰር በተላኩ አብዮታዊ ወታደሮች አማካይነት በመቀሌ ቤተ መንግስት ተይዘው ታስረዋል።
ልዕልት አይዳ በደርግ ጊዜ ለ14 ዓመታት ከታሰሩት የንጉሠ ነገሥቱ የሴት ቤተሰቦች መካከል አንዷ ነበሩ፡፡
ልዕልት አይዳ ከእስር ከተፌ በኋላ የተቋረጠውን የቤተሰብ ህይወታቸውን ከባለቤታቸው እና ከልጆቻቸው ጋር በስደት ቀጠሉ፡፡
ከደርግ ውድቀት በኋላ ወደ ኢትዮጵያ ከተመለሱ በኋላ ወደ ዋሽንግተን ዲሲ እና ወደ አዲስ አበባ በመመላለስ ጊዜያቸውን አሳለፉ።
በመጨረሻም ጥር 7 ቀን 2005 ዓ.ም. በተወለዱ በ86 ዓመታቸው በአሌክሳንድሪያ ቨርጂኒያ ሕይወታቸው አልፏል።

2. ልዕልት ሂሩት ደስታ

ልዕልት ሂሩት ደስታ
ልዕልት ሂሩት ደስታ ሚያዝያ 12 ቀን 1922 ዓ.ም. አዲስ አበባ ተወለዱ፡፡
ናትናኤል ቲ ኬኒ የተባለው ጋዜጠኛ በሚያዝያ ወር 1957 የናሽናል ጂኦግራፊክ እትም ላይ፤ “እሷ፤ ሰራተኛ ሲሰራ ስታይ፤ የሚሰራበትን መሳሪያ ወስዳ እንዴት እንደሚጠቀምበት ሰርታ የምታሳይ በጣም ዲሞክራሲያዊ የሆነች፤ የልዕልቶች ልዕልት ነች፡፡” በማለት ገልጿታል።
ልዕልት ሂሩት ደስታ በለንደን ለረጅም ጊዜ በሕክምና ከቆዩ በኋላ በተወለዱ በ84 ዓመታቸው ለንደን በ2006 ዓ.ም. ከዚህ አለም በሞት ተለይተዋል፡፡
የቀብር ስነ ሥርዓታቸውም በአዲስ አበባ በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ተፈጽሟል።

3. ልዕልት ሰብለ ደስታ

Princess Seble Desta
ልዕልት ሰብለ ደስታ

(photo edited by the webmaster)

Dejazmach Kasa Wolde Mariam
ደጃ/ ካሣ ወልደ ማሪያም

photo courtesy of:  SPU
ልዕልት ሰብለ ደስታ ነሐሴ 26 ቀን 1923 ዓ.ም. አዲስ አበባ ተወለዱ፡፡
ልዕልት ሰብለ ደስታም ልዕልት ሶፊያ ደስታ በተሰረጉበት በተመሳሳይ ቀንና ቦታ የወለጋ ጠቅላይ ግዛት የሌቃ ቄለም ሥርዎ መንግስት አልጋ ወራሽ ከሆኑት ከጆቴ ከሚወለዱት ከደጃዝማች ካሣ ወልደ ማሪያም ጋር ተጋብተው አምስት ልጆችን እና 6 የልጅ ልጆችን አፍርተዋል፡፡
የልጆቻቸው ስምም፤
  1. አምሃ ካሣ
  2. እመቤት ካሣ
  3. የሽመቤት ካሣ
  4. ደብሪቱ ካሣ
  5. ኮከብ ካሣ
ይባላሉ፡፡

ልዕልት ሰብለ ደስታ ትምህርታቸውን እንግሊዝ አገር በሚገኘው በኦክስፎርድ ዩኒቨርሲቲ አጠናቀዋል፡፡
እንደ እናቷ ሁሉ ልዕልት ሰብለም የኢትዮጵያ ሴቶች የበጎ አድራጎት ማህበር ፕሬዝዳንት ነበሩ፡፡
በእርሳቸው ጊዜ አዲስ አበባ ላይ ወጣት ሴቶች በሰላም ሠርተው እንዲኖሩ ለማስቻል ለማህበሩ ገቢ የሚያስገኝ እጅግ ዘመናዊ ህንፃ ገንብተው ነበር።
የልዕልት ሰብለ ደስታ ባለቤት ደጃዝማች ካሣ ወልደ ማሪያም በአሜሪካ በፖለቲካል ሳይንስ የማስተርስ ዲግሪ ተቀብለዋል፡፡
ልዕልት ሰብለ ደስታ ልጃቸው አምሀ ካሣ ተወልዶ አንድ ዓመት ሳይሞላው በደርግ በቄጥጥር ስር ውሎ ለ 13 ዓመታት በእስር ላይ ከቆየ በኋላ በ1980 ዓ.ም. ከእስር ተለቋል፡፡
ካሣ ወልደ ማሪያም በጣም አስተወይ፤ በአስተሳሰብ የበሰሉ፣ አገራቸውን መወከል የሚችሉ፣ መጽሐፍ ቅዱስን ጠንቅቀው የተረዱና ጠንካራ እምነት የነበራቸው መሆኑን የተማሩበት የተምህርት ቤት ጓደኞቻቸው ይናገራሉ፡፡
ደጃዝማች ካሣ ወልደ ማሪያም በ1952 ዓ.ም. የንጉሠ ነገሥቱ ልዩ ፀሓፊና የጽሕፈት ሚኒስቴር ምክትል ምኒስትር በመሆን ከተሾሙ በኋላ በሚቀጥለው ዓመት የቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ የመጀመሪያው ፕሬዝደንት ሆነው ተሸሙ፡፡
ካሣ ወልደ ማሪያም የዩኒቨርስቲው ፕሬዚደንት በነበሩበት ጊዜ በቁርጠኝነት እና በትጋት ለስኬት የሚሰሩ ምሁር እንደነበሩ አሜሪካ የተማሩበት የሲያትል ፓሲፊክ ኮሌጅ ፕሬዘደንት አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ለጉብኝት መጥተው መስክረዋል፡፡
ካሳ ወልደ ማሪያም በፕሬዘዳንትነት በቆዩባቸው ሰባት አመታት ውስጥ፣ ዩኒቨርሲቲው ሰፊ እድገት አሳይቷል።
የትምህርት፣ የህክምና እና የህግ ፋከልቲዎችን አቋቁሟል። በኢትዮጵያ ኮሌጅ የገባ ተማሪ ሁሉ ከሞላ ጎደል ያውቋቸዋል።
በአሜሪካም ሆነው በሌላወም የዓልም ክፍል ተቀባይነትን አግኝተዋል፡፡
በ 1961 ዓ.ም. ካሣ ወልደ ማሪያም የወለጋ ጠቅላይ ግዛት አስተዳዳሪ ሆነው ተሹመዋል፡፡
ደርግ በ1966 ዓ.ም. ሥልጣን ላይ ከወጣ በኋላ ክቡር ደጃዝማ ካሣ ወልደ ማሪያም በቁጥጥር ስር ውለው በምኒልክ ቤተ መንግሥት ከታሠሩ በኋላ ሐምሌ 7 ቀን 1971 ዓ.ም. ከታሰሩበት ክፍል ተጠርተው በእስር ላይ ከሚገኙት ፓትርያርክ አቡነ ቴዎፍሎስ ዘንድ ተንበርክከው ይፍቱኝ ብለው ፍታትን ከተቀበሉ በኋላ ተወስደው በደርግ ተገለዋል፡፡
አማሟታቸውም እርሳቸው እና ፓትርያርክ አቡነ ቴዎፍሎስ ታንቀው እንደተገደሉ ይታመናል፡፡

4. ልዕልት ሶፊያ ደስታ

Princess Sofia Desta
ልዕልት ሶፊያ ደስታ
Captain Dereje Haile Mariam
ልዑል ደረጀ ኃይለ ማሪያም
ልዕልት ሶፊያ ደስታ ጥር 17 ቀን 1926 ዓ.ም. በጅማ ተወለዱ፡፡
ልዕልት ሶፊያ ጥር 23 ቀን 1951 ዓ.ም. የዕውቁ አርበኛና የጦር መሪ የኃይለ ማሪም ማሞ ልጅ ከሆነው ከካፒቴን ደረጀ ኃይለ ማሪያም ጋር አዲስ አበባ ተጋብተው ትዳር መስርተዋል፡፡
ካፒቴን ደረጀ የተወለዱት በ1929 ዓ.ም. ነው፡፡
ካፒቴን ደረጀ እንግሊዝ አገር ከሚገኘው ከሳንደርስት ሮያል አካዳሚ በ1947 ዓ.ም. ተመርቀዋል፡፡
ካፒቴን ደረጀ ከልዕልት ሶፊያ ደስታ ጋር በ1951 ዓ.ም. ከተጋቡ በኋላ ልዑል ደረጀ ኃይለ ማሪያም ተብለው መጠራት ጀመሩ፡፡
ልዑል ደረጀ ኃይለ ማሪያም በ1953 ዓ.ም. በመንግስቱ ነዋይ ተጠንስሶ የነበረውን የመንግሥት ግልበጣ ሙከራ ለማክሸፍ በተደረገው ውጊያ ውስጥ ሕይዎታቸው ሊያልፍ ችሏል፡፡

ልዕልት ሶፊያ ደስታ ከሰሯቸው ሥራዎች ውስጥ፤
  1. ልዕልት ሶፊያ ደስታ እንጦጦ ዓለም አቀፍ ትምህርት ቤት የተሰኘውን የግል ትምህርት ቤት በማቋቋም ራሳቸው በመምራት የደሀ ቤተሰብ የሆኑት ልጆች ጥራት ያለው ትምህርት አግኝተው እንዲማሩ የስኮላርሽፕ ዕድል እንዲሰጥ አድርገዋል፡፡
  2. ቸሻየር ኢትዮጵያን እና የወጣት ሴቶች ክርስቲያናዊ ማህበር ያሉትን YWCA (Young Womens' Christian Association) የበጎ አድራጎት ድርጅቶችን በማቋቋም አስተዋፅኦ አድርገዋል፡፡ በአጠቃላይ ልዕልት ሶፊያ፤ ከራስ ወዳድነት ነፃ የሆኑ፣ ለጋስ፣ ደከመኝ ሰለቸኝ ሳይሉ በበጎ አድራጎት ስራ በመሰማራት ለኢትዮጵያ ልጆች ብቻ ሳይሆን ለመላው ህጻናት ሳይቀር ትምህርት እንዲያገኙ እና ደህንነታቸው እንዲጠበቅ ከፍተኛ ፍላጎት የነበራቸው ሴት ነበሩ፡፡

ልዕልት ሶፊያ ደስታ በደርግ ቁጥጥር ስር ውለው ከታሰሩበት ጊዜ ጀምሮ ለ14 ዓመታት በእስር ቤት ከቆዩ በኋላ በ 1980 ዓ.ም. ከእስር ቤት ሲፈቱ ወደ ጄኔቫ ሄደው ከቆዩ በኋላ ከዚያም ወደ ስዊትዘርላንድ፣ በመጨረሻም ወደ ለንደን ሄደው እዛው መኖር ጀመሩ፡፡
ከጥቂት ጊዚያት ቆይታ በኋላ ህዳር 2 ቀን 1914 ዓ.ም. በተወለዱ በ88 ዓመታቸው ከዚህ ዓለም በሞት ተለይተዋል፡፡ ሥርዓተ ቀብራቸውም በለንደን ተፈጽሟል፡፡
Captain Dereje Haile Mariam
እመቤት ሆይ ሃና ማርያም
ምህረተ ሥላሴ ደረጄ
ልዕልት ሶፊያ ደስታ እና ልዑል ደረጀ ኃይለ ማሪያም፤ እመቤት ሆይ ሃና ማርያም ምህረተ ሥላሴ ደረጄ የምትባል አንድ ሴት ልጅ ብቻ ሲያፈሩ፤ ደስታ አስፋው የሚባል የልጅ ልጅም አላቸው፡፡
እመቤት ሆይ ሃና ማርያም በ1953 ዓ.ም. በአዲስ አበባ ተወለደች፡፡
እመቤት ሆይ ሃና ማርያም እንግሊዝ አገር በሚገኘው ክላርንደን በሚባለው የልጃገረዶች ትምህርት ቤት ተምራለች፡፡
እመቤት ሆይ ሃና ማርያም፤ የኮሎኔል አስፋው እና የወይዘሮ ዳርምየለሽ ልጅ ከሆነው ከልጅ አክሎግ አስፋው ጋር ተጋብተው ልጅ ደስታ አክሎግ የሚባል ወንድ ልጅ አፍርተዋል፡፡
እመቤት ሆይ ሃና ማርያም ምህረተ ሥላሴ ደረጄ፤ በአስተዳደጓ ወቅት በአዲስ መልክ ያጋጠማትን ችግር፤ ለውጥ እና ጥርጣሬን እንዴት በብቃት ሕይወቷን እንደመራች ልዩ ግንዛቤዎችን የሚያስጨብጥ "ትናንት ብቻ ነበር" በሚል ርዕስ መፅሃፍ ጽፋ አሳትማለች፡፡

5. ሪር አድሚራል እስክንድር ደስታ

ሪር አድሚራል እስክንድር ደስታ
ሪር አድሚራል እስክንድር ደስታ ሐምሌ 30 ቀን 1926 ዓ.ም. በአዲስ አበባ ተወለዱ፡፡ ፋሽስት ኢጣሊያ ወረራ በፈፀመበት ወቅት ንጉሠ ነገሥቱ ወደ እንግሊዝ አገር ሲጓዙ እስክንድር ደስታ የአንደ ዓመት ህፃን ሆኖ አብረው ተጉዘዋል፡፡
እስክንድር ደስታ በእንግሊዝ አገር ሳለ መሰረታዊ ትምህርታቸውን ከተከታተሉ በኋላ በ1944 ዓ.ም. በ18 ዓመቱ በብሪታንያ የሮያል የባህር ኃይል ኮሌጅን በመቀላቀል ትምህርታቸውን ካጠናቀቁ በኋላ በባህር ኃይል ኦፊሰርነት ተመርቀዋል፡፡
በኋላም በ1947 ዓ.ም. አዲስ በተቋቋመው በኢትዮጵያ የባህር ኃይል ውስጥ በምክትል መቶ አለቅነት ከተመደቡ ከ3 ዓመት በኋላ በ1950 ዓ.ም. በ24 ዓመታቸው የኢትዮጵያ የባህር ኃይል ምክትል አዛዥ በመሆን ተመደቡ፡፡
በ1966 ዓ.ም. ደርግ መፈንቅለ መንግሥት እንዳካሄደ እስክንድር ደስታ ከምጽዋ ጠፍተው ወደ ጅቡቲ በመጓዝ እዛው ቆዩ፡፡
ንጉሠ ነገሥቱ ከሥልጣናቸው ሲወርዱ እስክንድር ደስታም በደርግ ቁጥጥር ስር ውለው ከታሰሩ በኋላ በተወለዱ በ40 ዓመት ዕድሜያቸው በደርግ ከተረሸኑት 60ወቹ ባለስልጣናት ጋር አብረው ተረሽነዋል፡፡








ምንጭ፤
  1. "የታሪክ ማስታወሻ"  ደራሲ፡- ደጃዝማች ከበደ ተሰማ 1962 ዓ.ም.
  2. "የኢትዮጵያ ታሪክ ከአፄ ቴዎድሮስ እስከ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ" ደራሲ፡- ተክለ ጻድቅ መኩሪያ 1961 ዓ.ም.
  3. የኢትዮጵያ ዘውድ ምክር ቤት ድረ ገጽ   ethiopiancrown
  4. የትረካው አጃቢ ሙዚቃ፣ ዋሽንት - በአንሙት ክንዴ   ዩቲውብ