Content-Language: am ሰማዕቱ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጴጥሮስ
header image


ሰማዕቱ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጴጥሮስ




ሰማዕቱ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጴጥሮስ ለሀገራቸው
ነፃነት መከበር ያደረጉት ተጋድሎና የተቀበሉት ሰማዕትነት

በእያንዳንዱ አርዕስት ሥር የሚገኘውን የድምጽ
ማጫወቻ በመጠቀም ትረካውን ማዳመጥ ይችላሉ

ክፍል አንድ

ትውልድ፣ የወጣትነት ዘመን፣ የጵጵስና ማዕረግ
ሰለመቀበልና ለሀገራቸው ነፃነት ያደረጉት ተጋድሎ

ክፍል ሁለት

በአቡነ ጴጥሮስ ላይ የተፈጸመ
የጳጳሳትና የቀሳውስት ቅስቀሳ

ክፍል ሶስት

በአቡነ ጴጥሮስ ላይ የጳጳሳትና የቀሳውስት ቅስቀሳና
አቡነ ጴጥሮስ የነበራቸው ፅኑ አቋም ሲፈተሽ

የመጨረሻ ክፍል

የብፅዑ ወቅዱስ አቡነ ጥሮስ መታሰር፣
ለፍርድ መቅረብና ሰማዕትነትን መቀበል


“ሰቆቃዎ ጴጥሮስ”
ተራኪ፤ ክቡር ሎሬት ፀጋዬ ገብረ መድህን
1961 ዓ.ም. “ቀበና”



St. Abune Petros
የሰማዕቱ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ
ሰማዕቱ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ ከአዲስ አበባ በስተሰሜን በሚገኘው በሰላሌ አውረጃ በፍቼ ከተማ በ ፲፰፻፸፭ (1875) ዓ.ም. ከገበሬ ቤተሰብ ተወለዱ፡፡

በታሪክ ተመራማሪው በአቻሜለህ ታምሩ የታሪክ ትንታኔና ዘገባ መሠረት ባጭሩ፤
ሰማዕቱ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ ከዎላይታ ወደ ሸዋ የመጡት የትግሬ ተወላጁን የወላይታውን ንጉሥ ካወ ጦናን ለማስገበር የዘመተው የማዕከላዊ መንግሥት ጦር አንድ ክፍል የሆነው የሰላሌ ገዢ የነበሩት የልዑል ራስ ካሣ ኃይሉ ዳርጌ ጦር ማርኮ ወደ ሰላሌ እንዳመጣቸውና በወቅቱም አቡኑ ሰላሌ ውስጥ ያደጉትና የተማሩት ፍቼ በሚገኘው ልዑል ራስ ካሣ ኃይሉ ግቢ ውስጥ ነበር።
በዚህም መሰረት፤ ልዑል ራስ ካሣ ያሳደጓቸውን አቡነ ጴጥሮስን ይወዷቸው ስለነበር ሊድሯቸው ቢፈልጉም አቡኑ ግን ወደ ሃይማኖት በጣም ያዘነበሉ ሰው በመሆናቸው ፍቃደኛ ሊሆኑ እንዳልቻሉ ተገልጿል።

የክርስትና ስማቸው ኃይለማሪያም ስለነበረ በዚሁ ስማቸው መጠራት ጀመሩ፡፡
በወጣትነት ዘመናቸው መልካም ሥነምግባር ያላቸውና ትህትናን የተላበሱ ስለነበሩ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ውስጥ ሐይማኖታቸውን ለማገልገል ፍላጎት አደረባቸው፡፡
በመሆኑም ደረጃ በደረጃ የድቁናና የቅስና ትምህርታቸውን ተከታትለው አጠናቀዋል፡፡
አባ ኃይለማሪያም የሐይማኖት ትምሕርታቸውን ካጠናቀቁ በኋላ እድሜያቸው 24 አመት ሲሆን በኢትዮጵያ ኦርቶዶከስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ሥርዓት መሠረት ምንኩስና ከተቀበሉ በኋላ በየገዳማቱና በየአድባራቱ እየተዘዋወሩ የየገዳማቱ አስተዳዳሪና መምህር በመሆን አገልግሎታቸውን ቀጠሉ፡፡
ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ፤ በግብፅ አሌክሳንድሪያ በሚገኘው በቅዱስ ጴጥሮስ ቤተክርስቲያን ጵጵስና ከተቀበሉት አራት አባቶች መካከል አንዱ በመሆን በ ፲፱፻፳ (1920) ዓ.ም. ማለትም በተወለዱ በ36 አመታቸው ጳጳስ በመሆን ተሹመዋል፡፡
የፋሽስት ኢጣሊያ ጦር በኢትዮጵያ ላይ የግፍ ወረራ በፈፀመበት ወቀት አቡነ ጴጥሮስ ከ ከቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ጋር ተገናኝተው በሰሜን ግንባር ካለው የኢትዮጵያ ጦር ጋር በመሆን ፋሽስት ኢጣሊያ በአይሮፕላን የሙስታርድ ጋስ ቦምብ በሠላማዊው ሕዝብ ላይ በማርከፍከፍ እንስሳቱን፤ የመኖሪያ መንደሮችንና ጫካውን ሳይቀር ፋታ በሌለው ጥቃት ሲያቃጥልና ሲያወድም የነበረውን አሰቃቂ ውርጅብኝ በአይናቸው ተመልክተዋል፡፡
በዚህ አስከፊ የመከራ ወቀት አቡነ ጴጥሮስ ሕዝቡን ሲያስተምሩ ይጠይቁ የነበረው ጥያቄ፤
“ እንዴት እነደኢጣሊያ ያለ የክርስቲያን እምነት የሚከተል ሀገር ኢትዮጵያን በመሰለ ሰላማዊ የክርስቲያን ሀገር ላይ እንደዚህ አይነት አስከፊና አሰቃቂ ሽብር ይፈጽማል? ”
የሚል ነበር፡፡
በዚህም የተነሳ ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ ፋሽስት ኢጣሊያ በንፁህ ሕዝባቸው ላይ ይፈጽመው የነበረው ኢሰብአዊ የሆነ የጭካኔ ድርጊት በጣም ስላስቆጣቸው በቆራጥነት ተነሳስተው ድርጊቱን በገሀድ በማውገዝ ሕዝቡ እንዳይገዛና በኢጣሊያ ላይ እንዲያምጽ ቅስቀሳ ጀመሩ፡፡
Abune Petros
ሰማዕቱ ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ
ከ ሐምሌ 22 ቀን 1928 ዓ.ም.
በፊት የተነሱት ፎቶግራፍ
እኝህ ተአማኒነትን፣ ከበሬታንና ተወዳጅነትን በኢትዮጵያ ህዝብ ያተረፉ ታላቅ አባትና የሐይማኖት መሪ ፋሽስት ኢጣሊያን ከመቃዎም ተቆጥበው እርሳቸውም ሆነ ሕዝቡ የወራሪውን ፋሽስት አገዛዝ አምነው እንዲቀበሉ የተለያዩ ጥረቶችን ማድረግ ተጀመረ፡፡
በወቅቱ ጥቂት ጻጻሳትና ቀሳውስት ለሀገራቸው ነጻነት ከመታገል ይልቅ ሥጋዊ ሕይዎታቸው በልጦባቸው በድሎት ለመኖር ሲሉ ለፋሽስት ኢጣሊያ አገዛዝ በመንበርከካቸው በአዲስ አበባ የሚገኘውን የፋሽስት ጦር መንግሥትነቱን አምነውና ተቀበለው በሰላም ይኖሩ ነበር፡፡
በነዚህ ጥቂት ራስ ወዳድ በሆኑ ሀገር ከሀዲ ባንዳዎች አማካኝነት ንጉሥ ቪቶሪዮ ኢማኑኤል የኢጣሊያ ንጉሥ ብቻ ሳይሆን የኢትዮጵያም ንጉሥ መሆኑን እንዲያምኑ፤ በአዲስ አበባ የሚገኘውንም የኢጣሊያን መንግሥትነት እንዲቀበሉና ሕዝቡንም በፋሽስት ኢጣሊያ አገዛዝ ላይ ማሳመጻቸውን እንዲያቆሙ ለማሳመን ለአቡነ ጴጥሮስ ድበዳቤ ጻፉላቸው፡፡
የተጻፈውም ደብዳቤ እንደሚለው፤ አቡነ ጴጥሮስ የታዘዙትን የሚቀበሉ ከሆነ በአዲስ አበባ ውስጥ እጅግ ዘመናዊ መኖሪያ ቤት ተሰጥቷቸው በሰላምና በድሎት መኖር እነደሚችሉ ይገልጻል፡፡
ይሁን እንጅ ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ ደብዳቤውን ካነበቡ በኋላ፤ ይህን ጥያቄ መቀበል ክርስቲያናዊ እምነታቸውን የሚጻረር፣ የእግዚአብሔርን ቃል የሚቃረን፣ ኃጢያት ውስጥ የሚያስገባና በአጠቃላይ ህሊናቸው የማይፈቅድላቸው በመሆኑ የቀረበላቸውን ጥያቄ እንደማይቀበሉና የኢትዮጵያ መንግሥትም ብቸኛው ንጉሥ አፄ ኃይለ ስላሴ መሆናቸውን አስረዱ፡፡
በመጽሐፍ ቅዱስ እንደተጠቀሰው፤
ለጊዜው በኃጥያት ከሚገኝ ደስታ ይልቅ ከእግዚአብሔር ሕዝብ ጋር መከራን መቀበልን መረጠ:: (ወደ ዕብራውያ 11፡25)
በተባለው መሠረት በአቋማቸው ጸንተው ወደ ደበረሊባኖስ በመሄድ በጾምና በጸሎት ቆዩ፡፡
የኢትዮጵያ ሕዝብም በእምነቱ ጸንቶ የፋሽስት ኢጣሊያን የግፍ ወረራ እንዲቋቋምና እንዳይተባበረው፣ ያለምንም ፍርሀት እረፍት ሳይሰጠው እንዲፋለመው፣ ይልቁንም እግዚአብሔር አንድ ቀን ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ከዚህ የግፍ ወረራ እንደሚታደጋት የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅስ እየጠቀሱ በየቦታው እየተዘዋወሩ ሕዝቡ በትግሉ እነዲበረታ ያለማሰለስ ማስተማር ቀጠሉ፡፡
ለናንተም ለወዳጆቸ እላችኋለሁ፤ስጋን የሚገድሉትን በኋላም አንድስ እንኳ የሚበልጥ ሊያደርጉ የማይችሉትን አትፍሩ፡፡
(የሉቃስ ወንጌል 12፡4)
Abune Petros
ሰማዕቱ ብፅዑ ወቅዱስ አቡነ ጴጥሮስ በኢየሩሳሌም

ምስጋና፤ ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን 1996 ዓ.ም.

አቡነ ጴጥሮስ በአንድ ወቀት ብድግ ብለው የጵጵስና ማዕረግ ልብሳቸውን ለብሰውና ሰማያዊ ቀለም ባለው ከለሜዳ የተጠቀለለ መስቀላቸውን ይዘው ወደ አዲስ አበባ አቀኑ፡፡
በዚያን ወቅት የአዲስ አበባ ሕዝብ የኢጣሊያ ፋሽስት ጦር በፈጠረው ስጋትና ጭንቀት ውስጥ ወድቆ ነበረ፡፡
አቡነ ጴጥሮስም ብዙም ሳይቆዩ በፋሽስት ወታደሮች ተይዘው እንዲታሰሩና ፍርድ ቤት እንዲቀርቡ ተደረገ፡፡
እንደተያዙም ማታውኑ በገነተ ልዑል ቤተ መንግሥት (ቀድሞ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ የነበረውና የአሀኑ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ) በሚገኘው ጉድጓድ ቤት ውስጥ እንዲታሠሩ ከተደረገ በኋላ ሲመረመሩ፣ ሲገረፉና ሲሰቃዩ አደሩ፡፡

አቡነ ጴጥሮስ በእስር ቤት እያሉ እንዲፈጽሙት የተሰጣቸው የመጨረሻ የማስጠንቀቂያ ጽሁፍ እንዲህ የሚል ነበር፤
የኢጣሊያን ወታደሮች በሕዝቡ ላይ የግፍ ወረራና ሽብር እየፈጠሩ ነው የሚለውን የማነሳሳት ስብከትዎን እንዲያቆሙ፤ የኢጣሊያንን ገዥነት አምነው እንዲቀበሉ፤ በተጨማሪም የኢጣሊያን ጦር ፋታ ሳይሰጡ በየሥፍራው የሚዋጉትን የነፃነት አርበኞች፤ ለኢትዮጵያ ነፃነት የሚዋጉ አርበኞች ሳይሆኑ ‘ሽፍቶች’ መሆናቸውን ለህዝቡ እንዲያሳምኑ፤ይህን የማይፈጽሙ ከሆነ ግን በሞት ይቀጣሉ፡፡

አቡነ ጴጥሮስም የተሰጣቸውን ይህን የማስጠንቀቂያ ጽሁፍ አልቀበለም በማለት ጥያቄ ላቀረቡላቸው የኢጣሊያን የጦር መኮንኖች በአሰተርጓሚ አማካይነት መልስ ሲሰጡ፤
እናንተ ባመጣችሁት የጦር መሣሪያና በነርቭ ጋዝ ህዝቤን በጭካኔ ያለርሕራሔ እየገደላችሁና እያሰቃያችሁ እያየሁ የናንተን ጥያቄ ህሊናዬ እንዴት ሊቀበለው የሚችል ይመስላችኋል?
እንደዚህ አይነት ወንጀል እየፈፀማችሁስ እያየሁ፤ አላየሁም ብል እግዚአብሔር ፊት እንዴት መቅረብ እችላለሁ?
በማለት ከተናገሩ በኋላ፤ የሚከተለውን የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅስ ተናገሩ፡፡

ጽድቅን የምታውቁ ሕጌም በልባችሁ ያለ ሕዝብ ሆይ፤ስሙኝ፤ የሰውን ተግዳሮት አትፍሩ፤ በስድባቸውም አትደንግጡ፡፡ እንደልብስም ብል ይበላቸዋል፤ እነደበግ ጠጉርም ትል ይበላቸዋል፤ ጽድቄ ግን ለዘላለም ማዳኔም ለትውልድ ሁሉ ይሆናል፡፡ (ትንቢተ ኢሳይያስ 51፡7-8)
ስለጽድቅ የሚሰደዱ ብፁአን ናቸው፤መንግሥተ ሰማያት የእነርሱ ናትና፡፡
(የማቴዎስ ወንጌል 5፡10)

ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስም ፋሽስቶችና ግብረ አበሮቻቸው ያቀረቡላቸውን ጥያቄ ውድቅ ስላደረጉባቸውና ሊያሳምኗቸው ስላልቻሉ በበነጋው ጧት የኢጣሊያ ፋሽስት ባስቸኳይ ባቋቋመው ፍርድ ቤት እንዲቀርቡ ተደረገ፡፡
ፋሽስቶች ያቋቋሙት ፍርድ ቤትም ወዲያውኑ በሞት እንዲቀጡ ወሰነ፡፡
ይህም ፋሽስቶች የወሰኑት የሞት ፍርድ ዜና በሀገሪቱ በሙሉ ተሰማ፡፡
Abune-Petros-Statute
ለሰማዕቱ ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ መታሰቢያ ይሆን ዘንድ በ1938 ዓ.ም.
የመጀመሪያውን ሃውልት ግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ
ሲያቆሙላቸው የበዓሉ አከባበር ይህን ይመስል ነበር
ሐምሌ 22 ቀን 1928 ዓ.ም. አቡነ ጴጥሮስ የሞት ቅጣት ወደሚፈፀምበት ሥፍራ ከተወሰዱ በኋላ የመጨረሻ እስትነፋሳቸው የሆነውን ንግግር እንዲያደርጉ ዕድል ተሰጣቸው፡፡
በሚረሸኑበትም ሥፍራ እንዲቆሙ ከተደረገ በኋላ ከያዙት መስቀል ላይ የተጠቀለለውን ከለሜዳ ካነሱ በኋላ በመስቀላቸው አራቱንም የዓለም ማዕዘናት ባርከው የሚከተለውን ተናገሩ፡፡

የሀገሬ ሕዝቦች ሆይ! ፋሽስቶች አርበኞችን 'ሽፍቶች ናቸው' ቢሏችሁ አትመኗቸው፡፡
አርበኞች ሀገራቸውን ከግፈኛው ፋሽስት ነፃ ለማውጣት በጽናት የሚታገሉ ሰዎች ናቸው፡፡
ሽፍቶችስ ከሩቅ ሀገር መጥተው ሰላማዊና አቅም በሌለው ኢትዮጵያ ሀገሬ ላይ የግፍ ወረራና ጭፍጨፋ የፈፀሙ እነዚህ በእናንተና በእኔ ፊት ቆመው የምታይዋቸው የፋሽስት ወታደሮች ናቸው፡፡
የኢትዮጵያ ሕዝብ የፋሽስት ጦር ለሚፈጽመው የግፍ ወረራ እንዳይንበረከክ እግዚአብሔር ፅናቱንና ብርታቱን ይስጠው፡፡
የኢትዮጵያ ምድርም በፋሽስት ወራሪ ጦር እንዳይገዛ አውግዣለሁ!
በማለት ንግግራቸውን ጨረሱ፡፡
Abune-Petros-Statue
ተሻሽሎ የተሠራው የብፁዕ ወቅዱስ
አቡነ ጴጥሮስ ሐውልት
ስምንት ወታደሮች በስተጀርባቸው ሃያ እርምጃ ርቀው ተንበርክከው በተንጠቀቅ ቆሙ። ወዲያው የፋሽስት ገዳይ ቡድኑ አዛዥ «ተኩስ» በማለት ትእዛዝ ሲሰጥ ስምንቱም የፋሽስት ወታደሮች በአንድላይ በአቡኑ ላይ የጥይት እሩምታ አዘነቡባቸው፡፡
መሞታቸውንና አለመሞታቸውን ለማረጋገጥ ዶክተር ተጠራ። ዶክተሩም እንዳልሞቱ አረጋገጠ።
ወዲያውኑ አቡነ ጴጥሮስን በጥይት ደብድቦ ለመግደል የተመደቡት ፋሽስት ያሰለጠናቸው የሰሜን ባንዳዎች ወንድሞቻችን በድጋሚ ተኩስ ከፍተው ብዙ ጥይቶችን በሰማዕቱ ላይ በማርከፍከፍ ሐምሌ 22 ቀን 1928 ዓ.ም.በተወለዱ በ 53 ዓመት ዕድሜያቸው የግፍ ግድያ ተፈጽሞባቸው በሰማዕትነት ሕይወታቸው ሊያልፍ ችሏል፡፡


Abune-Petros-Statue
ለብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጴጥሮስ
በሰላሌ ፍቼ የታነፀው
መታሰቢያ ሐውልት
ይህ በሰማዕቱ ላይ የተፈጸመው የግፍ ግድያ የኢትዮጵያን ሕዝብ ለሀገሩ ነፃነት በቁጭትና በቆራጥነት ይበልጥ እንዲታገልና ለፋሽስት ጦር በፍጹም እንዳይንበረከክ ጉልበትና ብርታት ስለሰጠው ፀረ ፋሽስት ትግሉ እየተጋጋለ ሄደ እንጅ ፈጽሞ አልበረደም፡፡
ቅዱስ አቡነ ጴጥሮስ ለሀገራቸው ነፃነት ሲሉ ያሳዩትን ፅናት፣ ቆራጥነት፣ ተጋድሎና የከፈሉትን ቅዱስ መስዋዕትነት ለመዘከርና እነዲሁም መጭው የኢትዮጵያ ትውልድ ፈለጋቸውን በመከተል፤ የሀገሩን ነፃነትና አንድነት ለድርድር ሳያቀርብ እንዲጠብቃት ለማስተማር ግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ቅዱስ ሰማዕቱ በተሰዉበት ሥፍራ ላይ የመታሰቢያ ሐውልት አቁመውላቸዋል፡፡

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስም፤ “አቡነ ጴጥሮስ ሰማዕት ጻድቅ ዘኢትዮጵያ” በማለት አጽድቆ ሠይሟቸል፡፡






ምንጭ፤
  1. A Martyr Bishop Abune Petros  courtesy: Fesseha Mekuria and Sven Rubenson
  2. ስንክሳር  ምስጋና ለ፤ ለየዲያቆን መልአኩ እዘዘው
  3. sewasew   sewasew.com
  4. የትረካው አጃቢ ሙዚቃ፣ ዋሽንት - በአንሙት ክንዴ   ዩቲውብ